የአ.አ ከንቲባ ጽ/ቤት ጠባቂ ፖሊሶች ተታኮሱ

ነገረ ኢትዮጵያ / Negere Ethiopia

image

የአዲስ አበባ መስተዳደር ማዘጋጃ ቤት (ከንቲባ ጽ/ቤት) ውስጥ የሚሰሩ ፖሊሶች ዛሬ በግምት ከቀኑ 6 ሰዓት አካባቢ እርስ በእርሳቸው መታኮሳቸውን አስተዳደሩ ውስጥ የሚሰሩ ሰራተኞች ለነገረ ኢትዮጵያ ገለጹ፡፡ 

ፖሊሶቹ የተታኮሱት በከንቲባው ጽ/ቤት ውስጥ የሚሰሩ ፖሊሶች በነበራቸው ግምገማ በተፈጠረ አለመግባባት እንደሆነ ታውቋል፡፡ ፖሊሶቹ የተታኮሱት ከስብሰባው እንደወጡ እንደሆነም ምንጮቹ ገልጸዋል፡፡

በከንቲባ ጽ/ቤት ፖሊሶች በተታኮሱበት ወቅት የአትክልት ተራን ጨምሮ በአካባቢው የሚገኘው ማህበረሰብ በድንጋጤ ውስጥ እንደነበርና አብዛኛው ከተኩሱ በኋላ ወደ አስተዳደሩ ቢሮ በማቅናቱ በከንቲባው ጽ/ቤት አካባቢ በርከት ያለ ህዝብ እንደሚገኝ ምንጮቻችን ጠቅሰዋል፡፡ 

ፖሊሶቹ በተታኮሱበት ወቅት ገላጋዮች መሃላቸው በመግባታቸው በሰው ላይ የደረሰ ጉዳት እንደሌለና ይህም በግምገማው ወቅት ለገላጋይ ያበቃ አጨቃጫቂ ጉዳይ እንደነበራቸው ያሳያል ተብሏል፡፡

ማህበረ ቅዱሳንን በመደገፍ ታላቅ እና ደማቅ የአጋርነት ንቅናቄ ሊደረግ ነው!

By ቀሲስ ሳህለማርያም

ንቅናቄው በጩሐት ሳይሆን ብልሃት እና ብስለት የተሞላበት መሆኑ ታውቋል።

image

የኢሕአዴግ መንግስት እና በቤተክህነት ውስጥ የተሰገሰጉ ካድሬዎች የተዋህዶ እምነትን የፖለቲካ አሽከር ለማድረግ የጀመሩትን ሴራ እና በማህበረ ቅዱሳን ላይ የተሰነዘረውን የስም ማጥፋት ዘመቻ በመቃወም በድምጻችን ይሰማ ዘኦርቶዶክስ እና በእኔም ለእምነቴ በብስለት እና ብልሃት በተሞላበት ሁኔታ በጋራ የተዘጋጀ ታላቅ እና ደማቅ የአጋርነት ንቅናቄ ማህበረ ቅዱሳንን በመደገፍ ሊካሄድ እንደሆነ እና ምእመናን ለዚሁ ንቅናቄ እንዲዘጋጁ ጥሪው ተላልፏል።
===============================
የመጀመሪያው ዙር ዝርዝር መግለጫ እንደሚከተለው ነው።

ለማኅበረ ቅዱሳን እመሰክራለው :: ለቀጣዩ የአደባባይ ምስክርነት በተጠንቀቅ እንዘጋጅ።
ምእመናን ምን ማድረግ እንዳለብን በቀጣይ ቀናት የሚገለፅ ይሆናል፡፡

††† #ድምጻችንይሰማዘኦርቶዶክስ – #እኔም_ለእምነቴ ! ††† የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ የሆነ እና ስለማኅበረቅዱሳን በጎ ሥራ ለመመስከር እንዲቻል ይህ መልዕክት ለሁልም ማዳረስ ሐይማኖታዊ ግዴታችን ነው ፡፡

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን !
እኔም ለእምነቴ የማህበራዊ ድረ ገፅ ተጠቃሚ ምንጮቻችን መሰረት፤ በማኅበረቅዱሳን ላይ አሁን እየተፈፀመ ያለው የስም ማጥፋት እና ውግዘት፤ ገና ከጥንስሱ ከማንም በፊት መረጃው ለሁሉም እንዲደር ጥረት ተደርጓል፡፡

ይሁን እንጂ ያስተላለፍ ነው መልዕክት ከቁምነገር ሳይቆጠር አብዛኛው ሰው ጉዳዩን በቸልታ አልፏታል፡፡ ሆኖም ግን በእኔም ለእምነቴ መረጃው ከተላለፈ ከ1 ቀን በኋላ ሪፖርተር ጋዜጣ በጉዳይ ዙሪያ ሰፊ ዘገባ ይዞ ወጥቷአል፤ ከዚያ ቀን ጀምሮ እስካሁን ስለማኅበረ ቅዱሳን መልካም የሆነ ነገር እየተሳማ አይደለም፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ጉዳይ አሁን ላይ ከጫፍ የደረሰ አሳሳቢ የቤተክርስቲያናችን ጭንቀት ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን በኢትዮጵያ ኦርቶዶክ ተዋሕዶ ቤተ/ክ እጅግ በጣም ለቁጥር የሚታክት መንፈሳዊ አገልግሎት የሰጠ እና እየሰጠ የሚገኝ መኅበር ነው፡፡

ይሁንእንጂ ጥቅምት፯ቀን፳፻፯ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተክህነት የስብሰባ አዳራሽ በተጀመረው ፴፫ኛው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ መደበኛ ስብሰባ ላይ የጉባኤ መክፈቻ ቃለ በረከት እንዲሰጡ የተጋበዙት ፓትርያርክ አባማትያስ፣ ማኅበረቅዱሳንን ‹‹የቤተ ክርስቲያን ቅኝገዥ›› ነው ፣ ‹‹እኔ ብቻዬን የምሠራው ነገር የለም፤ በዚኽ መግለጫ እንድትሠሩበት ነው የምነግራችኹ፤ አባ ማትያስ አላበደም፤ መልእክቴን እያስተላለፍኹ ነው ያለኹት፤መልእክቴን ተቀበሉ ብዬ እማፀናችኋለኹ፡፡››አስከትለውም ‹‹ቤተክርስቲያን ከቅኝ ተገዥነት ትውጣ፤ ካህናቱ ከመከራ ይውጡ›› በማለት በማኅበረ ቅዱሳን ላይ የመጨረሻ አስደንጋጭ እና አሳዛኝ ትዕዛዘቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በመሆኑም የፊታችን እሁድ ጥቅምት 9 ቀን 2007 ዓም በቅድስትሥላሴ ካቴድራል ቤተ/ክ “ዝክረ አቦ ሊቀነጳጳሳት” መንፈሳዊ መራሃ-ግብር ይካሄዳል፡፡ በዕለቱም የአባጳውሎስ የሐውልት ምረቃ ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ነገር ግን የዚህ መረሃ-ግብር ዋንኛ ዓላማ ቀደምት ቅዱስ ጳጳሳት እና ብፁዓንሊቃነጳጳሳትን በሥጋሞት የተለዩትን በማስብ የፀሎት እና የፍትሐት ስነ-ስርዓት ይደረጋል፡፡

ይህም የሚሆነው የቅ/ሲኖዶሱ ዓመታዊ ስብሰባ ከመካሄዱ የመጀመሪያው እሁድ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ መንፈሳዊ መረሃ-ግብር ከ1998 ዓ.ም ጀምሮ እየተካሄድ የሚገኝ ነው፡፡
ስለዚህም የፊታችን እሁድ ጥቅምት 9 ቀን 2007 ዓም በቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ቤተ/ክ ከሥርዓተ ቅዳሴ በኋላ፤ ፓትርያርክ አባ ማትያስ፣ በአገር ውስጥ እና በውጪ የሚገኙ በሙሉ ብፁዓን ሊቃነጳጳት፣ የአዲስ አበባ ሀገረስብከት ገዳማትና አድብራት አስተዳደሪዎች እና ፀሐፊዎች እንዲሁም ጥሪ የተደረገላቸው የውጪሀገር ብፁዓን ሊቃነጳጳሳት በሚገኙበት ታላቅ መንፈሣዊ ፕሮግራም ይካሄዳል፡፡

በዕለቱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ የሆነ ሁሉ በመረሃ-ግብሩ የመሣተፍ ሓይማኖታዊ ምግባር ነው፡፡ በዚህ ታላቅ ሐይማኖታዊ መረሃ-ግብር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ በሙሉ መገኘት አለብን፡፡ በዕለቱም ስለማኅበረ ቅዱሳን ባለፉት 17 ዓመታት ማኅበሩ በቤተክርስቲያናችን የሰጠው መንፈሳዊ አገልግሎት እንጂ ‹‹የቤተክርስቲያን ቅኝ ገዥ›› አለመሆኑ የምንመሰክርበት መልካም አጋጣሚ ነው፡፡

በዕለቱም ምእመናን ምን ማድረግ እንዳለብን በቀጣይ ቀናት የሚገለፅ ይሆናል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ የሆነ እና ስለማኅበረቅዱሳን በጎ ሥራ ለመመስከር እንዲቻል ይህ መልዕክት ለሁልም ማዳረስ ሐይማኖታዊ ግዴታችን ነው ፡፡

ወስብህትለእግዚአብሔር !!!

Al-Shabaab to attack Bole area

OSAC.GOV

The U.S. Embassy advises U.S. citizens in Addis Ababa to avoid large crowds and places where both Ethiopians and westerners frequent. The Embassy has received threat reports of al-Shabaab’s intent to target the Bole area. Restaurants, hotels, bars, places of worship, supermarkets, and shopping malls in the Bole Area should be avoided until further notice because they are possible targets for a potential imminent terrorist attack. While the exact location of this planned terrorist attack is not known, U.S. citizens should continue to maintain heightened personal security awareness.

We strongly recommend that U.S. citizens traveling to or residing in Ethiopia enroll in the Department of State’s Smart Traveler Enrollment Program (STEP). STEP enrollment gives you the latest security updates, and makes it easier for the U.S. embassy or nearest U.S. consulate to contact you in an emergency. If you don’t have Internet access, enroll directly with the nearest U.S. embassy or consulate.

Regularly monitor the State Department’s website, where you can find current Travel Warnings, Travel Alerts, and the Worldwide Caution. Read the Country Specific Information for Ethiopia. For additional information, refer to the “Traveler’s Checklist” on the State Department’s website.

Contact the U.S. embassy or consulate for up-to-date information on travel restrictions. You can also call 1-888-407-4747 toll-free in the United States and Canada or 1-202-501-4444 from other countries. These numbers are available from 8:00 a.m. to 8:00 p.m. Eastern Time, Monday through Friday (except U.S. federal holidays). Follow us onTwitter and Facebook to have travel information at your fingertips.

The U.S. Embassy in Addis Ababa is located at Entoto Street, P.O. Box 1014. The Consular Section of the Embassy may be reached by telephone: +251-111-306-130 or e-mail at consacs@state.gov, and is open Monday-Thursday, 7:30 a.m.-5:00 p.m. For after-hours emergencies, U.S. citizens should call +251-111-306-911 or 011-130-6000 and ask to speak with the duty officer.

አቶ በላይ ፍቃዱ አዲሱ የአንድነት ፓርቲ ፕሬዘዳንት ሆኑ፤ ኢንጂንር ግዛቸው በፍቃዳቸው ለቀቁ

አቡጊዳ

image

አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ብሄራዊ ምክር ቤት አቶ በላይ ፍቃደን የድርጅቱ ፕሬዘዳንት አድርጎ መርጧል።

ከሰባት ወራት በፊት ድርጅቱን እንዲመሩ የተመረጡት ኢንጂነር ግዛቸው ፣ “ወጣቶችን ወደ አመራር አመጣለሁ፣ ወጣቶችን ባካችሁ አቅማችሁን አጎልብቱና ተኩኝ” በማለት ለወጣት አመራሮች ሃላፊነታቸውን ለማስረክብ ፍላጎት እንደነበራቸው መግለጻቸው ይታወቃል። ቃላቸውን በመጠበቅ አዳዲስ አመራሮች ወደ ፊት መምጣታቸው ትግሉን ይረዳል የሚል እምነት ስላደረባቸው ኢንጂነር ግዛቸው፣ በፍቃዳቸው ሃላፊነታቸውን በመልቀቃቸው ነው፣ በድርጅቱ ሕገ ደንብ መሰረት፣ ብሄራዊ ምክር ቤቱ አዲስ አመራር የመርጠው።

አቶ በላይ ፍቃደ የአንድነት ምክትል ሊቀመንበር ሆነው የሰሩ፣ በድርጅቱና አባልትና አገር ዉስጥም ሆነ ከውጭ ባሉ ደጋፊዎች ዘንድ፣ ከመኢአድ፣ ከሰማያዊ ፓርቲ ፣ ከትብብር …እንዲሁም ሌሎች የተቃዋሚ ድርጅት አመራሮች ዘንድ ትልቅ ተቀባይነት እንዳላቸው ይነገርላቸውል።

ማኅበረ ቅዱሳን እንዴት ወዳጆች አፈራ? ጠላቶችስ ለምን ተነሡበት?

Eotcmk.org

“ምንም እንኳ በለስም ባታፈራ፥ በወይንም ሐረግ ፍሬ ባይገኝ…በእግዚአብሔር ደስ ይለኛል ትን.ዕንባ.3፡17-19”

image

በእግዚአብሔር ፈቃድ በቅዱስ ሲኖዶስ ይሁንታ የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለመደገፍና ለማጠናከር የተመሠረተው ማኅበረ ቅዱሳን ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ አያሌ ፈተናዎችን እያሳለፈ 22 ዓመታት ተጉዟል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በዓመታት ጉዞው ባከናወናቸው መልካም ተግባራት ታላላቅ የቤተክርስቲያን አባቶችን ጨምሮ እጅግ በርካታ ወዳጆችን እንዳፈራ ሁሉ ጥቂት በተቃራኒው የቆሙ ስሙን በየጊዜው በክፉ የሚያነሱ ቡድኖችም ተነሥተውበታል፡፡

ወዳጆቹ የቤተ ክርስቲያን ወዳጆች ናቸውና በአገልግሎቱ ተማርከው በሚሠራቸው መልካም ሥራዎች ተስበው ቤተ ክርስቲያን ያለባትን የአገልግሎት ክፍተት ለመሙላት በጋራ ከማኅበሩ ጋር በመሥራት ሲተባበሩ፤ በአንጻሩ ጠላቶቹ ደግሞ የተለያዩ አጋጣሚዎችን እያስታከኩ ማኅበሩን ለመወንጀል እየተጣጣሩ ይገኛሉ፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን እንዴት ወዳጆች አፈራ? ጠላቶችስ ለምን ተነሡበት?

ማኅበረ ቅዱሳን እግዚአብሔር ፈቅዶ ከተመሠረተበት ጊዜ አንሥቶ ወጣቶችን በተለይም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ከመደበኛው ትምህርታቸው ጎን ለጎን በየአካባቢው ወደሚገኙ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ሔደው መሠረታዊውን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት እንዲማሩ በማድረግ ሃይማኖታቸውን ጠንቅቀው እንዲያውቁና ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲጠብቁ እንዲሁም በዕውቀታቸው፣ በገንዘባቸውና በጉልበታቸው እንዲያገለግሉ በማድረግ፤ በተጨማሪም ወጣቱ ሀገሩንና ሕዝቦቿን አክባሪ፣ በሥነ ምግባር የታነጸ እንዲሆን በማስቻሉ ብዙ ወዳጆችን አግኝቷል፡፡

 

ከዚህም ሌላ የመናፍቃኑንና ቤተ ክርስቲያኒቱን እናድሳለን ብለው የተነሡትን የመናፍቃኑ ተላላኪ ቡድኖችን ሴራና የአክራሪ እስልምናውን እንቅስቃሴ በመረጃ አስደግፎ በማጋለጡ፣ ከክፉ ትምህርታቸው መመለስ ያልፈለጉ የተሐድሶ ቡድን አባላት ከቤተ ክርስቲያን እንዲወጡ ስለተወሰነባቸው እና ሌሎችንም የቤተ ክርስቲያኒቱን ችግሮች እየተከታተለ ለዕድገቷና ለብልጽግናዋ በመሥራቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የቤተ ክርስቲያን ወዳጆችን አፍርቷል፡፡

 

ከዚህ በተቃራኒው የተሰለፉት ወገኖች ደግሞ ወጣቱን እንደጠፍ ከብት ወደ ማያውቀው የመናፍቃን አዳራሽ የመንዳት ልምዳቸው በመቋረጡና በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በመግባት የሚያደርጉት ሥርዓቷን የማፋለስ እንቅስቃሴ፤ እንዲሁም አገልጋዮቿንና ምእመናኖቿን የማስኮብለሉ አካሔድ ማኅበሩ በክትትል በተለያዩ መረጃዎች ስለገለጠባቸው ማኅበረ ቅዱሳንን በጠላትነት በማየት ማኅበሩ እንዲፈርስ የማይቧጥጡት ዳገት የማይፈነቅሉት ድንጋይ የለም፡፡

 

እነዚህ የቤተ ክርስቲያን የውስጥ ጠላቶች ለጥቂት ጊዜ ጋብ ብለው የነበሩ ቢሆንም አሁን ባገኙት አጋጣሚ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንጀራዋን እየበሉ የሚኖሩ ወዳጆቻቸውን በማጠናከርና በማስፋፋት በሚሊዮን የሚቆጠር በጀት ከወዳጆቻቸው ተመድቦላቸው የቤተ ክርስቲያኒቱን ሥርዓት ለማዛባትና በጎቿን ለመበታተን ሌት ከቀን እየሠሩ ነው፡፡

 

ይኼ ዕቅዳቸው የሚሳካው እንደ ማኅበረ ቅዱሳን ያሉ ለቤተ ክርስቲያኒቱ እምነትና ሥርዓት መጠበቅ የሚቆረቆሩ ማኅበራትን ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ አጀንዳ በማድረግና እንዲበተኑ ክፉ ሥራ በመሥራት ነው፡፡ እነዚህ የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች ይሔንን ከንቱ ቅዠታቸውን እውን ለማድረግም በቤተ ክርቲያኒቱ የተለያየ ሓላፊነት ላይ የሚገኙትን የዓላማቸው አስፈጻሚዎች ሁሉ እየተጠቀሙ እንደሚገኙም ይታወቃል፡፡

 

ከዚህም ሌላ ድብቅ ዓላማቸው እንዲሳካ ተላላኪዎቻቸው በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥር የሚሆን ነገር ግን ስውር ዓላማ ያለው ማኅበር እንዲመሠርቱና ከዚህ በፊት ከንቱ ተግባራቸው ታውቆ በቤተ ክርስቲያኒቱ ታግደው የነበሩ ማኅበራት ሁሉ ከሞቱበት እንዲቀሰቀሱ እየሠሩም እያደረጉም ይገኛሉ፡፡

 

በቤተ ክርስቲያን ስም ድብቅ ዓላማቸውን ለማስፈጸም ያቋቋሟቸውና የሚያቋቁሟቸው፣ ማኅበራትንም ሕጋዊ ዕውቅና ለማሰጠት እንዲያመቻቸው ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ከኔ ሌላ ሌሎች አያስፈልጉም የሚል አቋም ያለው ማኅበር እንደሆነ ያስወራሉ፡፡

 

በእርግጥ ማኅበረ ቅዱሳን በትክክል የቤተ ክርስቲያኒቱን ሥርዓትና ደንብ ተከትለው በሚቋቋሙት ማኅበራት ላይ የማኅበሩ ጠላቶች ከሚያወሩትና ከሚያስወሩት አሉባልታ የተለየ አቋም አለው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርቲያን የሁለት ሺሕ ዓመታት ታሪክ ያላት ጥንታዊት ቤተ ክርስቲያን ትሁን እንጂ መንበሯ ከሊቀ ጵጵስና ደረጃ ወደ ፕትርክና ለማሳደግ አንድ ሺሕ ስድስት መቶ መራራ ዓመታትን አሳልፋለች፡፡ በዚህ ማለፏ ደግሞ ሌሎች አኀት አብያተ ክርስቲያናት የደረሱበት ዘመናዊ የአደረጃጀት ደረጃ ላይ ለመድረስ አልቻለችም፡፡ ልጆቿንም ጊዜው በሚጠይቀው መንገድ ለመምራት ሳትችል ስለቆየች እነዚህን ክፍተቶች የሚሞሉ አንድ አይደለም በርካታ ማኅበራት እንደሚያስፈልጓት ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ነገር ግን እኩያኑ እንደሚሉት ሳይሆን እነዚህ ማኅበራት ሲቋቋሙ ለአንዲት ቤተ ክርስቲያን ዕድገትና የአገልግሎት ሥምረት የሚንቀሳቀሱ ተልእኮአቸውና ዓላማቸው ተለይቶ የሚታወቅ፣ መንፈሳዊ ተግባርን ብቻ የሚፈጽሙ፣ የሚናበቡና በስልት ለአንድ ውጤት የሚተጉ ሊሆኑ ይገባቸዋል የሚል ጽኑ አቋም አለው፡፡

 

ይሔንን አቋሙን ደግሞ በርካቶች የሚደግፉት እንደሆነ ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ምክንያቱም እነዚህ የመናፍቃኑ ተላላኪዎች በቤተ ክርስቲያን ስም ያቋቋሟቸው ማኅበራት ከዚህ በፊት በቤተ ክርስቲያን ላይ ጥለውት የሔዱት ጠባሳ የሚታወቅ ስለሆነ ማኅበረ ቅዱሳን በማኅበራት ላይ ግልጽ አቋም አለው፡፡ ከዚህም ሌላ እነዚህ የውስጥ ዐርበኞች ይኽ ስውር ዓላማቸው ያልታወቀባቸው ይመስል ማኅበሩን ለመወንጀል የማይለጥፉለት ታፔላ፣ የማይለፍፉት ወሬ የለም፡፡ ነገር ግን እነዚህ የቤተክርስቲያን ጠላቶች ስለማኅበሩ የሚያወሩት ሁሉ ከእውነት የራቀ እና ሁሉም የሚገነዘበው ግልጽ እውነታ መሆኑን ባለማወቃቸው እናዝናለን፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን ምንም ስውር ዓላማ የለውም፤ ከማንኛውም የፖለቲካ አስተሳሰብ የጸዳና በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው መተዳደሪያ ደንብና መመሪያን ሳያዛንፍ እየሠራ ያለ፤ በተሰጠውም መተዳደሪያ ደንብና ሓላፊነት መሠረት ከአባላቱ የሰበሰበውን የገንዘብ መዋጮ ገቢና ወጪ እያሰላ በውስጥ ኦዲተሮችም እያስመረመረ በመሥራት ተጨባጭ ለውጥ ያመጣ ማኅበር እንጂ በወሬ የሚኖር አይደለም፡፡ ይሔንን አሠራሩንም ቀርቦ ማየት ይቻላል፡፡ አባላቱም በገንዘባቸው፣ በዕውቀታቸው በጉልበታቸውና በመላ ሕይወታቸው ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉ እንጂ እንደ መናፍቃኑ ተላላኪዎች ለሆዳቸው ያደሩ፣ ሆዳቸው አምላካቸው የሆነባቸው እዚህም እዚያም ደሞዝ የሚቀበሉ አይደሉም፡፡

 

ማንኛውም አካል እንዲያውቅልን የምንፈልገው ሐቅ ማኅበረ ቅዱሳን ቅዱስ ሲኖዶስ ለሰጠው ሓላፊነትና አባላቱም ለገቡለት ቃል ኪዳን ሃይማኖታቸው የሚፈቅደውን መስዋዕትነት ለቤተ ክርስቲያን ልዕልናና ክብር ለመክፈል የተዘጋጁ እንጂ በተዛባ አመለካከት ወደ ኋላ የሚያፈገፍጉ አለመሆናቸውን ለመግለጽ እንወዳለን፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎቱ የሚታይ አሠራሩም ግልጽ ነው፡፡ ስለዚህም የመናፍቃኑ ተላላኪዎች መሠረተ ቢስ ውንጀላ ከአገልግሎታችን አንዲት ጋት ወደ ኋላ እንደማይመልሰን እንዲታወቅልን እንፈልጋለን፡፡ ርእይና ተልእኮአችንን ለማሳካት ዛሬም ነገም እንሠራለን፤ ትናንትን ያሻገረን እግዚአብሔር ዛሬንም ያሳልፈናልና፡፡

ይህ ጽሑፍ ግንቦት 16 ቀን 2003 ዓ.ም ወጥቶ የነበረና ታርሞ በድጋሚ የቀረበ ነው፡፡

 

የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ እወቁ፡፡ያዕ1፡2

ማኅበረ ቅዱሳን

image

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተዋጀችውና የተመሠረተችው መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ ተቀብሎ፣ ሥጋውን ቆርሶ፣ ደሙን አፍስሶ ነው፡፡ ሐዋ.2ዐ፥28፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ሲገልጽም “በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ።” ብሏል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን በደሙ ሲዋጅ ጥንተ ጠላት ዲያቢሎስን ድል ነስቶ፣ ምርኮውን መልሶ፣ ሞትን ደመስሶ በመሆኑ ዲያቢሎስ የድል ነሺውን ቤተ ክርስቲያንና ወደ ነጻነት የተመለሱትን ክርስቲያኖች ዘወትር ይፈትናቸዋል፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊው እግዚአብሔር ኃላፊያቱንና መጻእያቱን በገለጸለት ራዕይ ስለ ዲያቢሎስ ፈተና ሲጠቁም “ዓለሙንም ሁሉ የሚያስተው ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ተጣለ፤ ወደ ምድር ተጣለ ….ለምድርና ለባሕር ወዮላቸው፤ ዲያብሎስ ጥቂት ዘመን እንዳለው አውቆ በታላቅ ቍጣ ወደ እናንተ ወርዶአልና። ዘንዶውም ወደ ምድር እንደ ተጣለ ባየ ጊዜ ወንድ ልጅ የወለደችውን ሴት አሳደዳት።” ዮሐ. ራዕ. 12፥9-17፡፡

ታሪክና መጻሕፍት እንደሚያስረዱት ቤተ ክርስቲያን ከተመሠረተችበት ጊዜ ጀምሮ ከፈተና ተለይታ አታውቅም፡፡ ጌታን የሰቀሉ አይሁድ ደቀመዛሙርቱን በእርሱ ስም እንዳያስተምሩ ለማድረግ በማስፈራራት ብዙ ጥረዋል፤ አስረዋቸዋል፣ ገርፈዋቸዋል፣ አሳደዋቸዋል፣ ገድለዋቸዋል፡፡ ሐዋ.ሥ 4፥17-21 ነገር ግን ቤተ ክርስቲያን በአለት ላይ የተመሠረተችና በመንፈስ ቅዱስ የምትመራ ስለሆነ ሥራዋ አልተቋረጠም፤ ተከታዮቿም አልጠፉም ዕለት ዕለት ይበዛሉ እንጂ፡፡ ማቴ. 16፥18

ቤተ ክርስቲያን በዘመነ ሐዋርያት፣ በዘመነ ሰማእታትና በዘመነ ሊቃውንት እንደጊዜው የተለያየ መከራና ፈተና አሳልፋለች፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጠላት የሆነው ዲያብሎስ ጥንት በአይሁድ፣ በሮማዊያን ነገሥታት፣ በአህዛብ እያደረ፤ ክርስቲያኖች በሃይማኖታቸው በመጽናታቸውና ቤተ ክርስቲያንን በማገልገላቸው ሰውነታቸው በሰም ተነክሮ በእሳት እንዲቃጠሉ፣ በቁርበት ተጠቅልለው ለአንበሳ እንዲሰጡ፣ በድንጋይ ተወግረው እንዲሞቱ፣ በስለት እንዲቀረደዱ፣ በሰይፍ እንዲቀሉ ያስደርግ ነበር፡፡ ክርስቲያኖችም በእምነታቸው እየጸኑ ከሞት የተረፉት፤ በዋሻ በግበበ ምድር እየሆኑ የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ሲፈጽሙ ኖረዋል፡፡ ጌታ “የሲዖል ደጆች አያናውጧትም” ያላት ቤተ ክርስቲያን እስከ ዓለም ዳርቻ እየሰፋች የመሰረታትን ጌታ እያመሰገነች ትኖራለች፡፡ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን ለማሳካትና የዲያቢሎስን ሽንገላ ለመቋቋም በተለያዩ የአገልግሎት መስኮች ልጆቿን ታሰማራለች፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እውቅና ሰጥታ ልጆቿን ለአገልግሎት ካሰማራችባቸው መንገዶች አንዱ የማኅበራት አገልግሎት ነው፡፡ በዚህ የማኅበራት አገልግሎት የዲያቢሎስን ፈተናና ሽንገላ ተቋቁመው በርካታ መንፈሳዊ ተግባራትን እያበረከቱ ከሚገኙ ማኅበራት መካከል ማኅበረ ቅዱሳን አንዱ ነው፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ ከ22 ዓመታት በፊት ቅርጽ ይዞ የተዋቀረና በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አገልግሎቱን የሚፈጽምበት ደንብና ሥርዓት የተበጀለት ማኅበር ነው፡፡ አባላቱም የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች የሆኑና በየአጥቢያቸው የልጅነት ግዴታቸውን እየተወጡ የሚገኙ ሲሆኑ በቅናተ ቤተ ክርስቲያን ተሰባስበው ለቤተ ክርስቲያን እድገት የሚያግዙ የትሩፋት ሥራዎችን የሚሠሩ ናቸው፡፡

ማኅበሩ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ ተለይቶ በተሰጠው ተግባር መሰረት፤ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚማሩ ተማሪዎችን በየአጥቢያቸው አሰባስቦ፤ ከየሰንበት ትምህርት ቤቶቹ ጋር በመተባበር ትምህርተ ሃይማኖትን የሚያስተምር፣ አባላቱንና በጎ አድራጊ ምእመናንን በማስተባበር ስብከተ ወንጌል በሀገር ውስጥና በውጪው ዓለም እንዲስፋፋ የሚያደርግ፣ አድባራትና ገዳማት በልማት ራሳቸውን እንዲችሉ የሚያደረግ፣ የቤ ተክርስቲያናችን ሀብት የሆነው የአብነት ትምህርት እንዲጠናከርና ሊቃውንቱም ወንበራቸውን እንዳያጥፉ በመርዳት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል፡፡

ይህ መንፈሳዊ ተግባር በቤተ ክርስቲያን በመተግበሩ፤ ቤተ ክርቲያንን የማይወዱና ውድቀቷን እንጂ ጥንካሬዋን የማይሹ አካላት የማኅበሩን አገልግሎት አልወደዱትም፡፡ ስለሆነም ቤተ ክርስቲያንን ለማዳከም ማኅበረ ቅዱሳንን ጠልፎ መጣል እንደ ዋነኛ ስልት አድርገው ቆርጠው መሥራት ከጀመሩ ውለው አድረዋል፡፡ እነዚህ አካላት ለዓላማቸው የሚጠቅም ሆኖ እስካገኙት ድረስ ማንኛውንም ነገር ይጠቀማሉ፡፡ በተለያየ ደረጃ ያሉ ሰዎችን በማሳሳት፣አሉባልታ በመንዛት፣የቤተ ክርስቲያን አባቶችን ጭምር በማሳሳት የሚፈልጉትን ተግባር ለመፈጸምና ለማስፈጸም ይተጋሉ፡፡ ማሩን በማምረር ወተቱን በማጥቆር- ደጋግመው እየወተወቱ ብዙ የዋሐንን የነርሱን የማደናቀፍ ተግባር ተባባሪ ለማድረግ ይጥራሉ፡፡

በጎ ነገር ሲሠራ በጠላት ዲያብሎስ በኩል እንቅፋት እንደሚቀመጥ ሁልጊዜ የታወቀ ነው፡፡ ፈተናውን ማለፍ መሰናክሉን መቋቋም ግን የአንድ ክርስቲያን ግዴታ ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም እንደነዚህ ዓይነት ፈተናዎች ከቀድሞ ጀምሮ ሲያጋጥሙት ቢቆይም በአገልግሎቱ ምክንያት የመጡ መሆናቸውን በመገንዘብ በአባቶች ጸሎት፣ በእግዚአብሔር ኃይል አሸንፎ ላለንበት ዘመን ደርሷል፡፡ ወደፊትም በእግዚአብሔር ፈቃድ ይቀጥላል፡፡

ከላይ በጠቀስናቸው አካላት አማካኝነት አንዳንድ ወገኖቻችን ስለማኅበሩ የተሳሳተ መረጃ ሲደርሳቸው ቤተ ክርስቲያንን የጠበቁ መስሏቸው አገልግሎቱን የሚያደነቅፉና ጥሩ ባልሆነ ሁኔታ የሚፈርጁትን አካላት ወግነው ሲቆሙ ይታያሉ፡፡ እነዚህ አካላት ትክክለኛውን መረጃ ቢያገኙ፣ ቢያውቁና ቢገነዘቡ ከማኅበሩ ጋር የዓላማ ልዩነት ስለሌላቸው፤ አብሮ በፍቅር ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ምንም የሚቸግራቸው ነገር የለም ብለን እናምናለን፡፡ ወደፊትም ከማኅበሩ ጋር አብረው ሊሠሩ የሚችሉ፣ የሚመክሩና የሚያስተካክሉ እንደሆኑ ማኅበሩ ያምናል፡፡ ካሁን ቀደምም እንዲህ ዓይኖቶቹን አካላት ባገኘ ጊዜ ሁሉ ማኅበሩ በማወያየቱና በማስረዳቱ የማኅበሩን አገልግሎት እየደገፉ የሚገኙ በርካታ ናቸው፡፡

ቤተ ከርስቲያንን በዓላማ የሚጠሉ ግን የማኅበሩን አገልግሎት ቢያውቁና ቢረዱትም የዓላማ ልዩነት ስላላቸው መቼም አገልግሎቱን በቀና አያዩትም፡፡ ዕለት ዕለት ለማደናቀፍ ይጥራሉ፡፡ በዚህም የተነሳ በአሁኑ ሰዓት በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ ሆነው ነገር ግን ቤተ ክርስቲያንን ጠልፈው ለመጣል የሚታገሉ፣ እንዲሁም ከቤተ ክርስቲያን በአፍኣ ሆነው እጃቸውን ባስረዘሙ አንዳንድ አካላት ማኅበሩ ፈተናዎች እየገጠሙት ነው፡፡

ለምሳሌም ያህል በአንዳንድ ሀገረ ስብከቶች በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው የመተዳደሪያ ደንብ መሠረት በዋናነት የሚያስተባብረውን የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ሃይማኖታዊ ትምህርት እንዳያስተምር ሲከለክሉና ሲያቋርጡ ይታያሉ፡፡ ማኅበሩ አገልግሎት የሚሰጥባቸውን ማእከላት ቢሮዎች የሚዘጉ አንዳንድ አጥቢያዎችም ይስተዋላሉ፡፡ በተጨማሪም ማኅበሩ የሚያበረክተውን ሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንዲደናቀፍ የሚፈልጉ አካላትም በሕዝብ ጉባኤዎችና ስብሰባዎች ሳይቀር የማኅበሩን ስም እያነሱ ተገቢ ያልሆነና ማኅበሩን በፍጹም የማይገልጹ ቅጽሎችን እየሰጡ ለማስረዳት ሲሞክሩ ይስተዋላሉ፡፡

እነዚህ ለማሳያነት በተጠቀሱት የማኅበሩ ተግዳሮቶች መነሻነት በአንዳንድ ግለሰቦች አማካይነት መዋቅሮችን አላግባብ በመጠቀም የግለሰቦቹን ምኞት ከግብ ለማድረስ የሚሠሩና ጥንቃቄ ያልታከለባቸው እርምጃዎች እንጂ የቤተ ክርስቲያን ወይም የመንግሥት ውሳኔ ነው ብለን አናምንም፡፡ ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን አካል እንደመሆኑ ፈተና ስለማይለየው ስለሚያጋጥሙት ፈተናዎች በጸሎት፣ የሚመለከታቸው አካላት በማስረዳትና በመወያየት፣ እንዲሁም በመታገስ አልፎ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሰረተችውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እግዚአብሔር እስከፈቀደበት ጊዜ ድረስ ያገለግላል፡፡

ማኅበሩ ፈተና ሲያጋጥመው መንፈሳዊ ማኅበር እንደመሆኑ መፍትሔ ለማግኘት የሚሄድባቸው መንገዶች ሁልጊዜም የታወቁ ናቸው፡፡ ችግሮች ሲመጡ ጊዜያዊና በእግዚአብሔር ኃይል በቀላሉ ሊፈቱ የሚችሉ መሆናቸውን በመረዳት በጥበብና በትዕግስት ከሚመለከከታቸው አካላት ሁሉ ጋር እየተወያየ ይፈታል፡፡ የችግር አፈታቱ ሥርዓት መንፈሳዊነትን የተከተለ በመሆኑ ሥጋዊ አስተሳሰብን ሳይጨምር ሃይማኖታዊ ፈተና ሲመጣ ማሸነፊያው ሃይማኖታዊ ኃይል ነው ብሎ ያምናል፡፡ እርሱም እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጎ በጾምና በጸሎት በትዕግስትና በጽናት፤ እግዚአብሔርን በመጠየቅ ነው፡፡

በማርቆስ ወንጌል ላይ እንደምናገኘው፡- (ማር. 4፡37) “ብርቱ ዐውሎ ነፋስም ተነሣና ውኃ በታንኳይቱ እስኪሞላ ድረስ ማዕበሉ በታንኳይቱ ይገባ ነበር። እርሱም በስተኋላዋ ትራስ ተንተርሶ ተኝቶ ነበር፤ አንቅተውም። መምህር ሆይ፥ ስንጠፋ አይገድህምን? አሉት። ነቅቶም ነፋሱን ገሠጸው ባሕሩንም። ዝም በል፥ ፀጥ በል አለው። ነፋሱም ተወ ታላቅ ፀጥታም ሆነ። እንዲህ የምትፈሩ ስለ ምን ነው? እንዴትስ እምነት የላችሁም? አላቸው። እጅግም ፈሩና። እንግዲህ ነፋስም ባሕርም የሚታዘዙለት ይህ ማን ነው? ተባባሉ።” ይላል፡፡ በታንኳይቱ የተመሰለችው ቤተ ክርስቲያን በፈተና ልትናወጥ ትችላለች፡፡ እንዲህ ባለ ጊዜ በውስጧ ያለውን፣ ነገር ግን እኛ የድርሻችንን እስክንወጣ ድረስ የሚጠብቀውንና ዝም ያለ (የተኛ) የሚመስለውን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በጸሎት መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ፈተናን ጸጥ የሚያደርግ አምላክ እንደምናመልክ ልንዘነጋ አይገባምና ፡፡

ማኅበሩ በቤተክርስቲያንም ሆነ በማኅበራችን ዙሪያ ስላሉ ነገሮች ማንኛውንም መረጃ የሚያስተላልፈው በራሱ ሚዲያና በመተዳደሪያ ደንቡ መሠረት ሥርዓት ባለው መልኩ በሚመለከታቸው የማኅበሩ ኃላፊዎች በኩል እንደሆነ የታወቀ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በሆነ መንገድ የሚተላለፍ ልዩ ልዩ መረጃዎችንና ሀሳቦችን በመያዝ ማኅበሩን በተመለከተ የግል ሀሳብንና ተግባርን ማንጸባረቅ አግባብ አለመሆኑን ሁሉም አካላት ሊያውቀው ያስፈልጋል፡፡

ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን ዓላማን ግብ ያለው በመሆኑ በጊዜው በሚታዩ ጥቅመኞችና አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ሁከት ሳንዘናጋ የወንጌል ተልእኳችንን በጥበብና በትዕግስት ከግብ ማድረስ ይገባናል እንላላን፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ያዕቆብ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ እወቁ፡፡ ያዕ.1፡2 እንዳለ ስለ እምነታችንና ስለቤተ ክርስተያናችን የምናደርገውን አገልግሎት ፈታኙ ዲያብሎስ ሊያደናቅፍ ሠራዊቶቹን ቢያሰማራም እግዚአብሔር አምላካችንን ትዕግስትንና ጽናትን እንዲሰጠን ፈተናውንም እንዲያሳልፍልን በጽናት እንለምነው፡፡- እርሱ በሰው ዘንድ የማይቻለውን እንድንችል ማድረግ ያውቅበታልና፡፡ ለዚህም የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔ

አሸባሪ ብዕሮች

By Kinfu Assefa

image

ይህች አጭር ጽሁፍ የተወሰደችው በአውስትራሊያ ከምትታተም “አሻራ” ከተሰኘች መጽሄት ልዩ እትም ላይ ነው።

የፈረንሳዩ አንባገነን ገዥ የነበረው ናፖሊዮን ቦናፓርት በአንድ ወቅት ስለ ነጻ ፕሬስ ሲናገር “ከአንድ ሺህ ሻምላዎች ይልቅ አራት ጋዜጦች የበለጠ መፈራት አለባቸው።” ነበር ያለው።

አንባገነኖች ፕሬስን ይፈራሉ። ይጠላሉም። የህዝብ መሰረት የሌላቸው፤ በራሳቸው የማይተማመኑ ሁሉ ነጻ ሃሳብን ይጠላሉ። ነፍጥን ብቻ ተማምነው በሕዝብ ጫንቃ ላይ የሚቀመጡ፤ እንደምን ነጻ አመለካከትን ሊቀበሉ ይችላሉ? ፍጹም አንባገነናዊነት በሰፈነባቸው እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ሀገሮች፤ ህግ አውጭው ህግ አስፈጻሚውን፣ ህግ አስፈጻሚው ደግሞ ህግ ተርጓሚውን እርስ-በርስ የሚቆጣጠሩበት እና የሚያስተከክሉበት አካሄድ የለም። ይህንን ቁጥጥር በጥቂቱም ቢሆን ተክቶ ይሰራ የነበረው ነጻው ፕሬስ ነው። ከዚህም አልፎ ሕዝቡ መብቱን እንዲያውቅና መብቱንም እንዲያስከብር ብዙ ሰርቷል-ፕሬሱ። ሙስናን አጋልጧል፣ እንደ እንባ ጠባቂም እየሆነ የህዝብን በደልም ይፋ አድርጓል። ይህን የተቀደሰ ተግባር ማከናወን እንደወንጀል፤ ጠንከር ሲል ደግሞ እንደ ሽብርተኝነት የሚቆጠርበት ሃገር ሆናለች የዛሬይቱ ኢትዮጵያ።

መብትን ማወቅ እና ማሳወቅ፤ ‘ህዝብ ለጦርነት እንዲነሳ ማድረግ፤ ወይንም በስራዓቱ ላይ ጥርጣሬ መፍጠር ነው’ ተብሎ ከተተረጎመ ደግሞ ጋዜጠኛን በአሸባሪነት መፈረጁ ብዙ ሊደንቀን አይገባም።

ኢትዮጵያ ላለፉት አስርት-አመታት ጋዜጠኞችን በማሰር ከአፍሪካ በቁጥር አንደኛ ደረጃ ላይ የነበረች ሃገር ናት። አሁን ይህንን ደረጃዋን ለቃለች። እድገትና ትራንስፎርሜሽኑን ተከትሎ ከመጡት ለውጦች አንደኛው መሆኑ ነው። ኢትዮጵያ የአንደኝነት ደረጃዋን ያጣችው ታዲያ ትራንስፎርሜሽኑ ይዞት በመጣው መሻሻል አይደለም። ነጻ ፕሬሱ ከሃገሪቱ እንዲጠፋ በተደረገ ሁለገብ ጦርነት እንጂ። አብዛኛው ጋዜጠኛ ተሰድዷል፣ ጥቂቶቹ ታስረዋል፣ አንዳንዶቹም አቅማቸው ተሟጦ አልቆ፤ ዝም ብለው እንዲቀመጡ ተደርገዋል። ለነጋሪ የተረፉትንም እስከዛሬዋ እለት ድረስ እያሳደዷቸው ይገኛሉ።

ከጅምሩ በፕሬሱ ላይ የተከፈተው የገዥው ፓርቲ ውግያ ቀላል አልነበረም። ፕሬሱ ግን እለት ተዕለት የሚያርፍበትን የአንባገነኖች ጡጫ ሁሉ ችሎ ብዙ ተጉዟል። እየተንገዳገደ፤ እየወደቀና እየተነሳ የህዝቡን የህሊና ንቃት እንዲሰፋ ከማድረጉም ባሻገር በኢትዮጵያ የማንበብ ባህል እንዲዳብር ነጻው ፕሬስ ተግቶ ሰርቷል። የህትመት ዋጋ እስከ 500% እንዲጨምር ቢደረግም ፕሬሱ አልቆመም ነበር። ጋዜጠኞች እንደጥጃ እየታሰሩ፣ እየተደበደቡ፣ እየተሰቃዩም ስራቸውን ላለማቋረጥ መትጋታቸውን አላቆሙም። በካድሬ ዳኞች ፍርደ-ገምድል ፍትህ ሲሰጣቸው፤ ያለ አግባብ በእስርና በገንዘብ ሲቀጡም ሰራቸውን አላቋረጡም…

የአሜሪካው ፍሪደም ሃውስ በተከታታይ ባወጣቸው ዘገባዎች ኢትዮጵያን ፕሬስ (Status: NOT FREE) “ነጻ ያልሆነች” ሃገር ሲል ፈርጇል። የፕሬስ አዋጁንም ፍጹም አፋኝ ሲል ይከሳል። የፈረንሳዩ ሪፖርተርስ ዊዝ አውት ቦርደርስ፣ የኒውዮርኩ ሲ.ፒ.ጄ. እና የብራስልሱ አይ.ኤፍ.ጄ. በሽብር ክስ የተያዙ የጋዜጠኖችን ሰነድ እያከታተሉ አሳፋሪነቱን ቢገልጹም አፍ እንጂ ጆሮ ከሌለው ስርዓት ያገኙት የስድብ ምላሽ ብቻ ነው። አምነስቲ ኢንተርናሽናል እና ሂዩማን ራይትስ ዋችም አፈናውን ይፋ ማድረጉን ተያይዘውታል። ከገዥው ፓርቲ የሚያገኙት ምላሽ “የኒዮ ሊበራል” አቀንቃኞች የሚል ስድብ እና ዛቻ ብቻ ነው።

ከምርጫ 97 ነኋላ ግን የህወሃት እድገት እና ትራንስፎርሜሽን፤ ጫን ያለ ነገር ይዞ ብቅ አለ።

ሽብርተኝነት!

ከዚህ በኋላ ጋዜጠኛ በህገ-መንግስት ሳይሆን፤ ህጉን በሚጻረረው አዋጅ መዳኘት እንዳለበት ተነገረ። ስርዓቱም በባሩድ ሳይሆን ይልቁንም በብእር ጫፍ እንደሚሸበር አረጋገጠ።

ይህ የሽብርተኝነት አዋጅ ቃል በቃል የተቀዳው ከአሜሪካ እና ከእንግሊዝ መንግስታት ሰነድ መሆኑን ሃይለማርያም ደሳለኝ ለቢቢሲ ሲናገሩ ተደምጠዋል። ድንቅ ነው። ሰውየው ግን ምን እየተናገሩ እንደሆን የሚያውቁት አይመስልም። በዚህች በሙት መንፈስ የምትመራ ሃገር ሌላም ብዙ እንግዳ ነገር እንሰማለን። የቡሽ አስተዳደር ከቶኒ ብሌየር ጋር አልቃይዳ የተባለውን አደገኛ ሽብርተኛ ለማጥፋት የነደፉት ይህ ሰነድ ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥ ጋዜጠኞችን ለማጥፋት እየተጠቀሙበት እንደሆነ ነው የሚነግሩን። የፈረንጆቹ ሽብርተኝነት (terrorism) ሲተረጎም፤ “በሃይማኖት ወይንም በርዕዮተአለም ጥላ ስር ተደራጅቶ አመጽን የማድረግ ተግባር” እንደሆነ ይነግረገናል።

በሽብርተኝነት ተወንጅለው በየእስር ቤቱ የተጣሉት የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞች፤ የትኛውን ርዕዮተ-አለም ወይንም ሃይማኖት ተንተርሰው አመጽ እንደፈጠሩ፣ የትኛውን አውሮፕላን እንዳስጠለፉ፣ የትኛውን ህንጻ እንዳፈረሱ፣ የትኛውን ንጹህ ዜጋ እንደገደሉ አልተነገረንም።

እርግጥ ነው። የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞች እየተቹ ይጽፋሉ። ትችቱ ታድያ ለውጡ ላይ አይደለም። የለውጡ አቅጣጫ ላይ እንጂ። አቅጣጫው ትክክለኛ መስመር መያዝ እና አለመያዙን መተቸት “ወንጀል ነው” ሲባል ለቀረው አለም አዲስ ነገር ሊሆን ይችላል። ከዚያ የባሰም አለ። ገዢውን ፓርቲ መተቸት እና ስለ ለውጥ አስፈላጊነት መጻፍ በሽብርተኛነት ያስከሰሰ ወንጀል ሆኖ ሰማን። አስቂኙ ነገር፤ አዋጁ ለኦሳማ ቢን ላደን ሽብር በምእራባውያን ሀገሮች የረቀቀ የጸረ-ሽብር ህግ መሆኑ ነው።

ጋዜጠኞች በሽብርተኝነት ሲፈረጁ ነው ነጻው ፕሬስ በኢትዮጵያ አፈር የለበሰው። ይህ የመጨረሻ ጥይታቸው መሆኑ ነው። አለማቀፍ የጋዜጠኞች ተሟጋች ተቋማት ሳይቀሩ ተስፋ የቆረጡ እስኪመስል ድረድ በዘንድሮ አመታዊ ዘገባቸው የኢትዮጵያን ጉዳይ ችላ ብለውታል። እነዚህ ተቋማት በየአመቱ ስለኢትዮጵያ ፕሬስ ሁኔታ የሚያወጧቸው ዘገባዎች የሚዘገንኑ ነበሩ። ወያኔን የማይማር፣ የደነዘዘ እና የማይለወጥ ስርዓት አድረገው ስላዩት ችላ ያሉት ይመስላል። ሃያ አመት የማይሰማ፣ ያሃ አመት የማይሻሻል፣ ሃያ አመት የማይማር ስርዓት… ውሃ ቢወቅጡት እንቦጭ ሆነባቸው።

በምርጫ 97 ሰሞን በርካታ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞች ቃሊቲ ተወርውረው ነበር። በጉዳዩ ላይ የአምነስቲ ኢንተርናሽናል ዲያሬክተር ከነበሩት ዶ/ር ማርቲን ሂል ጋር ስናወራ አንድ ጥያቄ አነሱልኝ።

“ለመሆኑ ሰርካለም ፋሲል ላይ ለምን እንዲህ ጨከኑባት? ” የሚል ነበር የማርቲን ጥያቄ። እኝህ ታላቅ ሰው ይህን ጥያቄ ለምን እንዳነሱልኝ አሁን ነው የተገለጠልኝ።

የሰርካለም ፋሲልን ጉዳይ ማንሳቱ የኢትዮጵያን ፕሬስ የሰቆቃ ጉዞ በከፊልም ቢሆን ይገልጸዋል።

ሰርካለምን ከባለቤትዋ እስክንድር ነጋ ጋር አፍነው ወደ ቃሊቲ ሲወስዷት ነብሰ-ጡር ነበረች። የመውለጃዋ ቀን ሲደርስም ከእስር አልለቀቅዋትም። በምጥ ስቃይ፣ ነብስ ውጭ፤ነብስ ግቢ ሁኔታ ውስጥ ሆና እንኳን አሳሪዎችዋ ርህራሄ አላሳዩዋትም ነበር። በመጨረሻ እዚያው ቃሊቲ እስር ቤጥ ናፍቆትን ተገላገለች። በዚያ የጭንቅ ወቅት የሚይዘውን እና የሚጨብጠውን ያጣ ስርዓት ምን እያደረገ እንደነበር እንኳን በውል አየውቀውም። “የመንግስት ጠላት” የሚል ታፔላ ተለጥፎለት የሚንቀሳቀስ ጋዜጠኛ፤ ሊወድቅ ከሚንገዳገድ ስርዓት ከዚህም በላይ ሊደረግበት እንደሚችል ለማስረዳት ሞከርኩ።

ነብሰ-ጡርዋ ሰርካለም የተከሰሰችው ህገ-መንግስታዊ ስርዓቱን በሃይል ለመናድ እና ለማፍረስ፣ ጥላቻን የምታስፋፋ፣ ጥርጣሬን የምትነዛ… ተብላ ነበር። በ “ምህረት” ከእስር እንደተፈታች ወደ ኬንያ ተሰደደች። በኋላም ሀገር ሰላም የሆነ ሲመስላት ከስደት ተመለሰች። ይህች ወጣት እትብትዋ ወደተቀበረባት ሃገርዋ ብትመለስም እንደዜጋ የመኖር ዋስትናዋ ግን በአንባገነኖች መዳፍ ስር ሆነ። በኑሮዋ እና በትዳርዋ ዙርያ ካለፈው የባሰ ችግር መጣባት። ባለቤትዋ እስክንድር ነጋ በሽብርተኝነት ተከሶ በፍርደ-ገምድል ዳኛ ለአመታት ተፈረደበት። ቤት ንብረታቸውም በግፍ ተቀማ። ከዚህ በኋላ በመኖር እና ባለመኖር የሚደረግ ምርጫ ውስጥ መግባት ግድ ሆነባት። እናም ባለቤትዋን ወህኒ ቤት ጥላ ዳግም ተሰደደች። እስዋም ሆነች በሰቆቃ የተወለደ ልጅዋ በመንገድ ከመወርወራቸው በፊት ያላቸው አማራጭ ይህ ብቻ ነበር። የሚወዷት ሃገራቸውን ጥለው ከሁለት መቶ በላይ የሚሆኑ ስደተኛ ጋዜጠኞችን ተቀላቀሉ። እንደቀልድ የሚነገር ሌላም እውነታ አለ። ከ”ሽብርተኛ” ጋር በስልክም ሆነ በአካል ያወራ፣ አብሮ የታየ፣ አብሮ ሻይ የጠጣ፣ የተነካካ ሰው ሁሉ ሽብርተኛ እንደሆነ አዋጁ ይደነግጋል። ሰርካለም እና ናፍቆት በእስር ያለው እስክንድር ጋር በሚያደርጉት ግንኙነት ሽብርተኛ ተብለው ሊወነጀሉም ይችሉ ነበር።

በስልጣን ላይ ያሉት ሰዎች ፍርሃት ውስጥ እንዳሉ ግልጽ ነው። በጋዜጠኛ የሚናድ ሀገ-መንግስት ይዘው ስንት አመት ሊዘልቁ እንደሚችሉ ባናውቅም፤ አሁንም ጋዜጠኞችን ሲያስሩ ይህንንኑ ዘፈን ይደጋግሙታል። 99.7 በመቶ በህዝብ የተመረጠ መንግስት መራጩን ሕዝብ ከቶውንም መፍራት አልነበረበትም። ነገሩ ስላቅ ነው። ይህ ቀልዳቸው ግን የህዝቡን ንቃተ-ህሊና ዝቅ አድርጎ ከመመልከት የሚመጣ ይሁን እንጂ ጉዳዪ ሌላ ነው። አንባገነኑ ናፖሊዮን ቦናፓርት ብሎታል። ከሺ ሳንጃ አንድ ጋዜጠኛ ያስፈራል። የጭቆና እና የአፈና ስርዓት ገንብቶ ለረጅም አመት የቆየ አንባገነን በታሪክ አልታየም።

የፈቀደውን መምረጥ የሚችልን ህዝብ አዲስ ዘመንን ብቻ እንዲያነብ መምከራቸው ብቻ አይደለም በሕዝብ ላይ ያላቸው ንቀት፤ የፍትህ ስርዓቱን ለበቀል የሚዘረጋ እጃቸው አድርገው ነጻውን ፕሬስ ለማጥፋት ሲጠቀሙበትም እጅግ ያንገበግባል። የህግ የበላይነትን እንዲህ እያደረጉ ናዱት።

ኢሕአዴግ የፕሬስ ነጻነትን ለህዝቡ እንዳጎናጸፈ ይመጻደቃል። ይህ ስህተት ነው። መናገር፣ ሃሳብን በነጻነት መግለጽ፣ መጻፍ፣ … ወዘተ መብት የሰው ልጅ የተፈጥሮ ጸጋ እንጂ አንድ ስርዓት የሚያጎናጽፈን ጉዳይ አይደለም። በሌላ በኩል ደግሞ ይሀው ስርዓት እነዚሁኑ መብቶች እየጨፈለቀ እነሆ ሃያ ሶስት አመታትን ዘልቋል።

ነጻ ፕሬሱን ለምእራባውያን የዲሞክራሲ ማሳያ አድርጎ እንደተጠቀመበት እርግጥ ነው። የአለም ባንክ እና ለጋሽ ሃገሮች በኢትዮጵያ የሳንሱር አዋጅ እንደጠፋ ነው የሚነገራቸው። የእርዳታና ብድር እጃቸውን የሚዘረጉልንም ከቀድሞው የተሻለ የመጻፍና የመናገር ነጻነት አለ ብለው ስለሚያምኑ ይመስላል። ግና ይህ የሳንሱር አዋጅ በአእምሮ ሳንሱር መተካቱን የምናውቀው እኛ ብቻ ነን። ሳንሱር ቢኖር ይህ ሁሉ ጋዜጠኛ ባልታሰረ፣ ባልተንከራተተ እና ባልተሰደደ ነበር።

ምርጫ መጣ! ጋዜጠኛ ይውጣ! እንዲሉ… በቅርቡ በስድስት ነጻ ፕሬስ ህትመቶች ላይ ከተመሰረተው ክስ ጋር በተያያዘ አስራ ሁለት ጋዜጠኞች ለስደት መብቃታቸው ተዘግቧል። በጭላንጭል የነጻነት ድባብ ይንቀሳቀሱ የነበሩት፤ አዲስ ጉዳይ፣ ሎሚ፣ ጃኖ፣ አፍሮ ታይምስ እና እንቁ ጋዜጦች እንዲቋረጡ ተደርጓል። ጋዜጠኞቹም በአሸባሪነት ሽፋን ተከስሰው እስከ አስራ ስድስት አመት የሚደርስ ጽኑ እስራት ተበይኖባቸው የነእስክንድር ነጋ፣ ውብሸት ታዬ እና ርእዮት አለሙ እጣ ይደርሳቸዋል። እነዚህ ጋዜጠኞች የነበራቸው አማራጭ የሽብር አዋጁ ሰለባ መሆን አልያም አገር ለቀው መሰደድ ነው። ተሰደዱ። የስደተኛ ጋዜጠኛውን ቁጥር ወደ 210 አሳደጉት።

ውንጀላው ግን በተያዘለት መርሃ-ግብር ቀጥሏል። ሰሞኑን “ያልተገሩ ብዕሮች” በሚል ርእስ በኢቲቪ የቀረበውን “ዘጋቢ ፊልም” ያስተውሏል? በአንድ በኩል የጋዜጠኖቹ ጉዳይ በህግ የተያዘ እንደሆነ ይነግሩናል። በሌላ በኩል ደግሞ “ልማታዊ” ተዋንያን እና የስርዓቱ አጎብዳጆችን በመገናኛ ብዙሃን አቅርበው ፍርድ እንዲሰጡ ያደርጓቸዋል። በእርግጥ በመገናኛ ብዙሃን እየቀረቡ አንድ ተጠርጣሪን በወንጀለኝነት መፈረጅ አዲስ ነገር አይደለም። የፍትህ አካሉ ውሳኔ ከመስጠቱ በፊት ተጠርጣሪው በኢቲቪ የፖለቲካ ፍርድ ይበየንበታል። ከዚያም እንደ “ዳኛ” ልዑል አይነት የሲቪል ሰርቪስ ምርቶች ውሳኔውን ያጸኑታል።

በዚያ የኢቲቪ ቅንብር ሃይሌ ገብረስላሴም ተዋንያን ነበር። የሚናገረውም የትዬለሌ። “ትልቁ የጦር መሳርያቸው ፕሬስ ነው።… ጦር ከፈታው ወሬ የፈታው ይባላል… ” ይለናል ሃይሌ ገብረስላሴ። “ዘጋቢ” ፊልሙም የእነ እስክንድር ነጋን ፎቶ፣ የእነ ተመስገን ጽሁፎች ያሳየናል። የዚህ ድራማ ሌሎቹ ተዋንያን ከሙያው ጋር የተያያዝን ነን የሚሉ አድርባዮች ናቸው። ሃይሌ ግን ምን ቤት እንደሆነ ግልጽ አይደለም። በየትኛውስ እውቀቱ ነው ፍርድ ሊሰጥ የደፈረው? “አንድ ጋዜጣ የውሃ አምራች ድርጅትን እንዲዘጋ አድርጓል።” ሲል ሃይሌ በዚያ “ዘጋቢ ፊልም” ይወነጅላል። አንድ ጋዜጠኛ እውነትን ጽፎ የንግድ ድርጅትን ወይንም የመንግስት ተቋምን ማፍረስ ወይንም በተቋማቱ ላይ ጥርጣሬ መፍጠር ከቻለ እንዲያውም ጀግና ነው የሚባለው። ጋዜጠናው የሚጽፈው ውሸት ከሆነ ደግሞ ፍርዱን ለህዝቡ ለምን አይተውለትም?

አብራሃ ደስታ ሌላው በአሸባሪነት ሽፋን የተከሰሰ ጋዜጠኛ ነው። አብርሃ አሸባሪ መሆኑ የተረጋገጠው ፍርድ ቤት ሲገባ እና ሲወጣ ነው። ሲገባ በጭብጨባ ሲወጣ በጭብጨባ ተሸኝቷል። ህዝብ በነቂስ ወጥቶ ኣብርሃ ጀግና! የነፃነት ታጋይ! እንወዳሃለን፤እናከብርሃለን ሲለው እነ ሃይሌ ገ/ስላሴ የት ነበሩ?

ያልተገራ አንደበታቸውን በመገናኛ ብዙሃን ሲከፍቱ የነበሩት እነዚህ ተዋንያን የሚነግሩን እጅግ አሳፋሪ ነገር ነው። አጠቃላይ ይዘቱ በመንግስት ላይ ምንም አይነት ትችት መቅረብ የለበትም የሚል እንድምታ አለው። የህወሃትን አንባገነናዊነት መተቸት፣ የስርዓቱ ፖሊሲዎች መንካትና በባለስልጣናቱ ላይ ጥርጣሪ እንዲኖር ማድረግ… ስርዓቱን ያፈርሰዋል ነው እያሉን ያለው። ህግ አውጭው ከህግ አስፈጻሚውን፣ ህግ አስፈጻሚው ደግሞ ህግ ተርጓሚውን እርስ-በርስ የሚቆጣጠሩበት እና የሚያስተከክሉበት አካሄድ በሌለበት ሃገር ነጻው ፕሬስ ከዚህ ውጭ ምን ይስራ ነው የሚሉት? ፕሮፓጋንዳ?

ለፕሮፓጋንዳውማ በርካታ አማራጮሽ አሉ። አዲስ ዘመን ጋዜጣም አለልን። ለ90 ሚሊዮን ህዝብ የቀረው ጋዜጣ። አዲስ ዘመን በቁጥር ስንት ሺ እንደሚታተም ባናናውቅም በኪሎ እየተሸጠ የሸቀጥ እቃ መጠቅለያ ሆነ እንጂ። ‘የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ተመረቁ፣ ሃይለማርያም ደሳለኝ ወደ ሱዳን ሄዱ፣ ሃይለማርያም ደሳለኝ ከሱዳን ተመለሱ። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በ 11 እጅ እንደሚያድግ ሃይለማርያም ደሳለኝ ተናገሩ።’ …. የሚሉ ዘገባዎችን እየያዘ ከሸቀጥ እቃ መጠቅለያነት ውጭ ለሚመጻደቁለት እድገት ምንም እንዳልፈየደ እንኳ አያውቁትም።

የመገናኛ ብዙሃን አፈናው በነጻ ፕሬሱ ላይ ብቻ አልተገደበም። በኢትዮጵያ የመረጃ መረቦችም ታፍነዋል። ከሰብ ሰሃራ አፍሪካ በኢንተርኔት ይዞታ እና አገልግሎት የመጨረሻዋ ሃገር ናት። ኢንተርኔቱን የሚቆጣጠረው መንግስታዊው ቴሌኮም ስርዓቱን የሚተቹ ድረ-ገጾችን በቻይና ቴክኖሎጂ እንዲዘጉ አድርጓል። የዜጎችን ስልክ በህገወጥ ማንገድ መጥለፍ የተለመደ ተግባር ነው። እንዲሁም ስካይፕ እና ቫይበር ያሉ የቮይስ ኦቨር ስልኮች ደግሞ ፊን ፊሸር በተባለ የኮምፒዩተር ቫይረስ አማካኝነት ይጠለፋሉ። እንዲህ እያሉ በዜጎች የግል ህይወት ሳይቀር እየገቡ ቴሌን ሙሉ በሙሉ የስለላ ተቋም እንዳደረጉት የአሜሪካው ሂዩማን ራይትስ ዋች ይፋ አድርጓል።

ኢትዮጵያን ወደ ጨለማ ዘመን እየወሰዳት ያለው ይህ የህወሃት ስርዓት የኢንተርኔት ተጠቃሚው እንዲያሽቆለቁል እየጣረ እንደሆነ ነው መረጃዎች የሚጠቁሙት። በተለይ የፌስቡክ አብዮትን ለመግታት ስለሚሻ የኢንተርኔት አገልግሎትን ማዳከሙ ላይ ጥብቅ አቋም ይዟል። መንግስት አልባዋ ሶማልያ እንኳን፣ ስድስት የቴሌፎንና ስልክ አቅራቢ ኩባንያዎች አሏት። በዚህ ቀላል ቴክኖሎጂ እንኳን ከሶማልያ በታች ሆኖ ስለ እድገት መመጻደቃቸው ሊያፍሩበት ይገባል።

እጅግ የሚያሳዝነው ይህ ስርዓት ለፈጸመው ለዚህ ሁሉ በደል ለሽልማት መብቃቱ ነው። ልማታዊው አርቲስት ሰራዊት ፍቅሬ በአርቲስቶች ስም ለሟቹ ጠቅላይ ሚ/ር የወርቅ ብዕር ነበር ያበረከተላቸው። ብዕር ትልቅ ትርጉም አለው። ብእር የሚሸለም ሰው ለፕሬስ ክብር ያለው፤ ፕሬስን የሚያከብር ሰው ነው። ሰራዊት የወርቅ ብዕር እንዲሸልም አርቲስቶች አልወከሉትም ነበር። ይህንን ሲያደርግ የነጻው ፕሬስ ጋዜጠኞች እስር ቤት ውስጥ ይንገላቱ ነበር። ሰራዊት ይህንን ሲያደርግ የአለም አቀፍ ህብረተሰብ ጠ/ሚኒስትሩን የፕሬስ አፈና በእጅጉ ያወግዝ ነበር። እንደ ሰራዊት ያሉ ሃላፊነት የጎደላቸው ሰዎች ብዙ አይደሉም። ለህሊናቸው ሳይሆን ለሆዳቸው ሲሉ እንዲህ አይነት ስራ እየሰሩ በሰው በቁስል ላይ እንጨት ይሰድዳሉ። ታዲያ እንደነዚህ አይነቶቹ አድርባዮችም ለፕሬሱ መጥፋት ሚናቸው ቀላል አይደለም። የማያልፍ የለም። ሁሉም ያልፋል። መንግስትም እንደ አንሶላ ተጠቅልሎ ይሄዳል። ይህ ቀን አልፎም ለትዝብት ያበቃናል።

ማን ነበር “ፕሬስ የሌለው መንግስት ከሚኖረን መንግስት የሌለው ፕሬስ ቢኖረን እንመርጣለን።” ያለው? እርግጥ ነው። ያለ ፕሬስ የሚኖር ህዝብ በጨለማ ነው የሚጓዘው። ያለ ነጻ አስተሳሰብ እና ያለ ነጻ ፕሬስ፣ እድገት ይመጣል ማለት አይታሰብም። እንዲያው የህዝብን ንቃተ-ህሊና ዝቅ አድርጎ መመልከት ይሆናል እንጂ።

ማኅበረ ቅዱሳን ታገደ

HARA ETHIOPIA ሐራ ዘኢትዮጵያ

image

ማኅበረ ቅዱሳን ታገደ፣የማህበሩ አባላት የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች ዕጣ ይደርሰዋል ተብሎ ይጠበቃል
ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ ከ አዲስ አበባ ሀ/ስብከት የለቀቁት በ ወያኔ የደህንነት ኃይሎች በደረሰባቸው ማስፈራራት ነው ተባለ። ማተብ በጥሱም የሚል አዋጅም በ ወያኔ ታውጁዋል።
በወያኔው ፓትርያርክ አቶ ማትያስ ፊታውራሪነት ከተለያየ አድባራት እና ገዳማት የመጡት ጥቂት በጥቅም የተገዙ የደብር አለቆች፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት መምሪያ ሃላፊዎች፣የ አዲስ አበባ ሀገረስብከት ዋና ሥራ አስኪያጅ ተብሎ በወያኔ የተሾመው ኦህዴድን ወክሎ ወያኔ ፓርላማ ተመራጭ የሆነው አቶ በላይ መኮንን፣ንቡረ እድ ኤልያስ ኣብርሃ የሚመራውና አባ ሰረቀ ብርሃን ወልደ ሳሙኤል፣ መጋቤ ካህናት ኃይለ ሥላሴ ዘማርያም፣ መዝገበ ጥበብ ቀሲስ ዮሐንስ ኤልያስ፣ኤልያስ አብርሃ እንዲሁም ሊቀ ትጉሃን ዘካርያስ ሐዲስ ያሉበት ቡድን ከ ሚኒስትር ዶ/ር ሺፈራው ጋር በመሆን ባቀነባበሩት ክስ ማህበሩን ወደ ማገድ እና በ አሸባሪነት የማስወገዝ ደረጃ ተሸጋግረዋል ።

የጎዳና ላይ ነውጥ ለማነሣሣት ሁከትና ብጥብጥ የሚሰብኩና የሁከትና ብጥብጥ መንገድን የሚቀይሱ ግለሰቦችና ቡድኖች የተሰባሰቡበት ነው በሚል የሀሰት ክስ የመታገድ እርምጃ የተወሰደበት ማኅበረ ቅዱሳን እስካሁን ያወጣው ምንም አይነት መግለጫ የለም። የማህበሩ የጂማ ንዑስ ማዕከል እና የዋናው ማእከል አንዳንድ አመራሮች እና አባላት ባለፉት ሁለት ቀናት በወያኔ የ ፅጥታ ኃይሎች ማዋከብ እና ፍተሻ እየተካሂደባቸው ቢሆንም ምንም አይነት መረጃ ለሚድያ እንዳይሰጡ በማህበሩ ዋና ፀሐፊ አቶ ተስፋዬ ቢሆነኝ እንደተነገራቸው ለማወቅ ተችሉዋል ። ጉዳዩን በቅርበት የሚከታተሉ ታዛቢወች ማህበሩ ለ ቤተ-ክርስቲያኒቱ ትልቅ አስተዋፅኦ እያደረገ ቢሆነም የማህበሩ ጥቂት አመራሮች ግን ከወያኔ ጋር በመተባበር አሁን በ ወያኔ የተሾሙተን አቶ ማትያስ ከማስመረጥ ጀምሮ ከበስደት ሀገር ከሚገኘው በብፁዕ አቡነ መርቆርዮስ ከሚመራው ሕጋዊው ሲኖዶስ ጋር ይደረግ የነበረውን የአባቶችን የእርቅ ውይይት እስከ ማስተጉዋጎል ድረስ አፍራሽ ሚና ይጫወት እንደነበር አስታውሰዋል ። በአሁኑ ሰዓት ወያኔ በሀገራቺን ላይ እያደረሰ ያለው ግፍ ፅዋውን ሞልቶ እየፈሰስ ይገኛል ። በ ወንዶምቻችን የኢትዮጵያ ሙስሊሞች መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴዎች ላይ ያደረገውን የሐሰት ክስ አሁንም በማህበረ ቅዱሳን ላይ ሊደግመው ዝግጅቱን አጠናቆ ይገኛል ።

http://haraethiopiadotcom.wordpress.com/

ማዕተቤን አልበጥስም !!!

By Zemedkun Bekele

በአንድ ወቅት በጨካኝነቱ ተወዳዳሪ ያልነበረው የታላቋ ሩስያ መሪ የነበረው ስታሊን በአገዛዝ ዘመኑ የሩስያ ኦርቶዶቶዶክስን ለማጥፋት ያልወሰደው አረመኔአዊ ድርጊት አልነበረም ። ከእነዚህም አረመኔያዊ ድርጊቶች መካከል የቤተክርስቲያኒቱን አማኞች በጥይት መግደሉ ጥይት ማባከን ነው ብሎ በማሰቡ ከፓትርያርኩ ጀምሮ እስከ አራስ ህፃናት ድረስ ያሉትን ኦርቶዶክሳውያን በግዙፍ መርከቦች እየጫነ ውቅያኖስ ውስጥ በመጨመር ለአሳነባሪዎች ቀለብ እስከማድረግ መድረሱ ፣ ይህን የመሰለው ግፍ ግን ኦርቶዶክሳውያኑን ከማጥፋት ይልቅ ይበልጥ ሃይማኖታቸውን እንዲያጠብቁ አደረጋቸው ። እንዲያውም በሩሲያ ታሪክ እንደዚያን ዘመን የኦርቶዶክሳውያን አማኞች ቁጥር በዝቶ የታየበት ዘመን እንደሌለ የታሪክ ፀሐፊዎች ይናገራሉ ።

የሁኔታውን አደገኛነት የተገነዘበው ስታሊን ፓርላማውን ሰበሰበና እንዲህ አለ ።” ጓዶች ይሄ አካሄዳችን አላማረኝም ከሃይማኖቱ ሰባኪዎች ይልቅ የእኛ ግድያ የሩስያ ኦርቶዶክስን እያለመለመ እና እያጠነከረ ይገኛል። እናም ግድያው ይቁም ። ምክንያቱም ከዚህ አይነቱ አካሄዳችን የተማርኩት ነገር ቢኖር ክርስቲያን እና ምስማር በመቱት ቁጥር እየጠበቀ መሄዱን” ነው ብሎ ከቅዱሳን አበው አንዱ የተናገሩት እስኪመስል ድረስ የክርስቲያን እና የሚስማርን ጉዳይ አንስቶ ለእኛ ለክርስቲያኖች የሚገርም ጥቅስ ትቶልን ፣ የሩሲያን ኦርቶዶክስ ማጥፋትም ባለመቻሉም ድክም ብሎት አቆመ ይባላል ።

ትናንት ከግሸን እንደተመለስኩ ለ 10 ቀናት ያህል የተለየሁትን የማኅበራዊ ድረገፆችን ለማየት ብከፍተው አንድ ደስ የማይል ዜና ብዙዎች ሲቀባበሉት ተመለከትኩ ። ብዙዎች የሚያወሩት በስሜት እንዳይሆን ብዬ ወደ አንድ ወዳጄ ጋር ብደውል ወሬ አለመሆኑን አረጋገጠልኝ ። እኔም ምንም ከሌሎች የተለየ ነገር ማለት ባልችልም የአቅሜን ታህል ድምፄን ላሰማ አልኩና ይኸው ብቅ አልኩኝ።

ክቡር ሚንስትሩ በሲቪል ሰርቪስ ስልጠና ላይ ግልፅ በሆነ አማርኛ ” የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ይሄን የኦርቶዶክሳውያን ማዕተብ መበጠሳችን አይቀርም ” ብለው መናገራቸውን ሰማን ። አንድን ሰው ወንጀለኛ አድርጎ ከባድ ፍርድ እንዲፈረድበት የሚያደርገው ደግሞ ምቹ ጊዜ ሰዓትና በተገቢው ሁኔታ ቅድመ ዝግጅት አድርጎ ወንጀል መፈፀሙ ሲረጋገጥ መሆኑን የህግ ባለሙያዎች ይናገራሉ ። አንዳንድ ሰዎች የሰው ህይወት በእጃቸው ጠፍቶ 3 እና 4 ዓመት የሚፈረድባቸው እና ሌሎች ደግሞ በተመሳሳይ መንገድ የሰው ሕይወት አጥፍተው ከ ዕድሜ ልክ እስከ ሞት ፍርድ ድረስ የሚያደርስ ቅጣት የሚወሰንባቸው ከ3 እና የ4 ዓመት ፍርደኞቹ በተለየ መልኩ በስህተትና በአጋጣሚ ሳይሆን ሆን ብለው አቅደው ፣ቅድመ ዝግጅትም አድርገው ሆን ብለው የፈፀሙት ወንጀል በመሆኑ ነው ቅጣታቸውን ከባድ የሚያደርገው ።

እኝህ ክቡር ሚንስትር በዚህች ጥንታዊት ቤተክርስቲያን ላይ ደስ የማይሉ ንግግሮችን ቀን እየጠበቁ መናገራቸውን ከጀመሩ ቆየት ብለዋል ። እኝህ ሰው ዛሬም ሲናገሩ እግዚአብሔር በሰማያት ብዙዎቻችን በምድር እየሰማን ነው። ከሰመነው ሰዎች መካከልም፦

1. ቅዱስ ፓትርያርካችን ሰምተዋል ።
2. መላው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሰምተዋል።
3. ካህናት እና ዲያቆናቱም ሰምተዋል።
4. መነኮሳቱና ባህታውያኑም ሰምተዋል።
5. የሊቃውንት ጉባኤ አባላትም ሰምተዋል።
6. የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት በሙሉ ሰምተወል።
7. ዘማሪዎቻችንም ለዚህ የሚሆን ዜማ ባይደርሱም ሰምተዋል።
8. ፀሐፍያን ነን ብለው በየአጋጣሚው መከራ የሚያሳዪን ፀሐፍትም ሰምተዋል።
9. ከሁሉም በላይ ከየመንፈሳዊ ኮሌጆቻችን ተመርቀው የወጡና የአውደምህረት ላይ የስቱዲዮና የሲዲ ላይ አንበሶቻችንም በደንብ ሰምተዋል ። ግን ሁሉም ይስሙ እንጂ ምንም ሊሉን አልፈቀዱም።

ቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ ክቡራን ሊቃነ ጳጳሳቱ ከጥቂቶች በቀር ብዙሃኑ በእርግና ማእረግ ላይ የሚገኙ ያውም መቃብራቸው የተማሰ ልጣቸው የተራሰ ቢሆንም ዝም ብለዋል ። አረ ተዉ ውኃ ሽቅብ አይፈስም ነው እኮ የሚባለው። እናንተ ዝም ስላላችሁ እኮ ነው ፓስተር ዳዊት ነኝ የሚል ፍንዳታ ወጠጤ ተነስቶ እንደፈለገ ቅድስት ቤተክርስቲያንን የሚሰድባትን ሰው ነው እኮ እንዲያው ሰው የላትም ተብሎ ከሚቀር በማለት እነ መምህር ምህረተአብ የአቅማቸውን ያህል የሚፍጨረጨሩት ። ሌሎችም እንዲሁ በየአቅጣጫው እየተነሱ የፈሪ በትራቸውን ሲያወርዱባት ምነው ዝምታችሁ በዛ ።

ሰባኪዎቻችንም እንደሁ ከጥቂቶች በቀር ብዙሃኑ እኛን ኢትዮጵያን አትልቀቁ ዲቪም አትሙሉ እያሉን እነሱ ግን በቦሌም በባሌም ፣ በሚስትም በሲስተምም እልም እያሉ መኖርያቸውን ከኢትዮጵያ ውጪ ከማድረግ በቀር ፣ ንግድ ሚንስቴር በማያውቀው ነፃው አውደምህረት ላይ በየ ስቱድዮው በመቀረፅ ያልበላንን በማከክ ከሚያራግፉብን ሸቀጦች ሌላ እና ለእርድ እንደተዘጋጀ የሐረር ሰንጋ ራሳቸውን ከማደለብ በቀር ምንም ሲፈይዱ አይታዪም ።

እስቲ ጥሩልኝ ኢትዮጵያ ውስጥ የቀረ ኑሮውን በምእራብ ሀገራት ያላደረገ ሰባኪ ። ከ ምህረተአብ በቀር እንደው በቤተክርስቲያን ላይ የሚወረወሩ ቀስቶችን ለመመከት የሚፍጨረጨር ማን አለ ? ንገሩኛ እከሌ በሉኝ ። ወይኔ ዛሬ እንኳን ሰው ይጥፋ ? እነ አትናትዮስን እነ ቅዱስ ጊዮርጊስን የወለደችው ቅድስት ቤተክርስቲያን የወላድ መካን ሆና ትታይ።

እኔ የምለው ክቡር ሚንስትር ይሄ አሁን ግዜ እየጠብቅንለት ነው ብለው የነገሩን ማዕተብ ከኦርቶዶክሳውያን አንገት ላይ የመበጠሱ ነገር የምእራብ ኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ባለፈው ዓመት ከምእራብ የሀገራችን ክፍል መጥተው ለቅዱስ
ሲኖዶሱ እንደተናገሩት …… ” ፖሊሶች በአንዳንድ ትምህርት ቤቶች በራፍ ላይ በመቆም ከኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች አንገት ላይ እየበጠሱ ነው ያሉትን አቤቱታ መነሻ በማድረግ በዚያ የታየው ማዕተብ የማስበጠስ ስራ ተሞክሮው አበረታች ሆኖ በመገኘቱ ነው ለዚህ አዋጅ መሰል ዛቻ ያበቃዎት ?

ሲቀጥል ደግሞ እርስዎ የሚከተሉት ሃይማኖት ምን ይሆን ?

እኔ ግን እላለሁ

1. ባለፈው ጊዜ ማኅበረ ቅዱሳንን የመጎነታተል ነገር ቢሞከር ከታሰበው በላይ ከማኅበሩ በተለያዪ ምክንያቶች የራቁትን ጨምሮ ሌሎች አዳዲስ አባላትን ወደ ማኅበሩ በማምጣት ማኅበሩን በሰው ኃይል እንዲጠናከር አድርጎታል።

2. በሻሻ የሚባል ቦታ በሀገራችን መኖሩን የሚያውቅ ከአካባቢው ሰው በቀር ስለ በሻሻ የሚያውቅ ብዙ ሰው አልነበረም ። ነገር ግን ጥቂት ብዙኃኑን የእስልምና እምነት ተከታዮች የማይወክሉ አሸባሪዎች ማዕተባችንን አንበጥስም ባሉ የተዋህዶ ልጆች ላይ በፈፀሙት ግድያ ምክንያት በሻሻ በዓለም ላይ ታወቀች። ዛሬ በሻሻ ልክ እንደ አክሱም ፅዮን ፣ ግሸን ማርያም ፣ ቅዱስ ላሊበላ ፣ ቁልቢ ገብርኤል ከመላው ዓለም በሚመጡ ምእመናን ይጨናነቃል ። በአክራሪዎቹ የወደመችዋ ደሳሳዋ የበሻሻ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ቤተክርስትያንም ዛሬ በሚገርም ካቴድራል ተተክቷል ። ለዚህ እውቅና ደግሞ ሀገረ ስብከቱ ምንም ያደረገው አስተዋፅኦ የለም ። የሰማዕታቱ መሰየፍ እንጂ ።

ይገርምዎታል ክቡር ሚኒስትር የበሻሻ ጉዳይ መች በዚህ ብቻ ያበቃል መሰልዎ ። አሁን መላውን ዓለም እያስደመመ የሚገኘው የወጣቶች የጥምቀት በዓል አከባበርን የወለደው እኮ የበሻሻ ሰማእታት ደም ነው። በዚህ ጉዳይ የአንድም ሰባኪ እጅ የለበትም ። ከግሪሳዎቹ የተሃድሶ ርዝርራዦች መካከል አንዱ ግሪሳ ብቻ ነው የእኛ የአገልግሎት ነው ወጣቱን እንዲህ እንዲነሳሳ ያደረገው ሲል የተሰማው። ይህ ግን ሀሰት ነው ግሪሳዎቹ ኪሎና የባንክ አካውንታቸውን ከመጨመርና ከማብዛት በቀር አንድም ምእመን ወደ ቤተክርስቲያን ጉያ አልጨመሩም ።

አሁን ደግሞ ምን እየሆነ መሰልዎት እርስዎ የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ማዕተብ ማስበጠሳችን እንደሁ አይቀር አሉ ከተባለ ወዲህ ይገርምዎታል የኦርቶዶክሳውያኑን አንገት ቢመለከቱ ቀድሞ የሀብት መግለጫ የነበሩትን የወርቅና የብር ሐብሎች በሚያምሩና በወፋፍራም የማዕተብ ክሮች ተተክተው እየታዩ ነው ። የብዙኀኑ የፌስ ቡክ ፕሮፋይል ፒክቸሮችም በማዕተብ ክሮች እየተለወጡ ነው ። የማዕተብ ክር ነጋዴዎችም ገበያ ድርት ብሏል። ምነው ደግሞ ቅዳሴ ማስቀደስ ፣ ንስሀ መግባት ፣ ስጋወደሙ መቀበል ፣ ፆም መፆም የሚከለክል በመጣና ተአምር ባየን ። ከዘመኑ ሰባክያን ይልቅ ምእመናን ወደ ቅድስት ቤተክርስትያን ለመመለስ እግዚአብሔር ባወቀ በአንድም በሌላም መንገድ የአህዛብና የመናፍቃን መነሳሳት ሳይሻል አይቀርም ። እንደውም የዘመኑን ግሪሳ ሰባክያን እና ዘማርያን ልብ ብላችሁ አንገታቸውን ብታዩት ማዕተብ የለውም።

በመጨረሻም ክቡር ሚንስትር እኔ ማዕተቤን በአንገቴ የማስረው ለጌጥ ሳይሆን ጌታ በማቴዎስ ወንጌል ምእራፍ 10 ፣ 32 – 33 ላይ የተናገረውን አምላካዊ መመርያ መሰረት በማድረግ ነው። ” ስለዚህ በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ፤ በሰው ፊትም የሚክደኝን ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እክደዋለሁ ይላል። ይህ ማለት በአፌ ማንነቴን መግለፅ የማልችል ብሆንም እንኳን ማዕተቤን በአንገቴ ላይ ማሰሬ ብቻውን የክርስቶስ መሆኔን እርርሪሪ እያለ በመጮህ ይመሰክርልኛል ።

ግን ቆይ የማዕተብ ክር በአንገታቸው ላይ ያለውን እናቆይ እና ሌሎቹን በትግራይ ፣ በአማራ ፣ በኦሮምያ ፣ በደቡብና በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች ያሉትን በግንባራቸዉ ፣ በአንገታቸው ፣ በክንዳቸው ላይ የተነቀሱ ኦርቶዶክሳውያን ዕጣ ፈንታስ እንዴት ሊሆን ነው ? ለዛሬ አበቃሁ ።

ዘመድኩን በቀለ ነኝ
ከግሸን ደብረ ከርቤ መልስ
መስከረም 26/ 1 /2007 ዓም
አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ

የኢሕአዴግ ስልጠናዎችን የነፃነት ኃይሎች መተዋወቂያ፣ መደራጃ፣ መረጃ መለዋወጫ በማድረግ ስልጠናዎቹ የራሱን የኢሕአዴግ ጉድጓድ መማስ አለባቸው

በ ታደሰ ብሩ 

image

ከጥቂት ዓመታት በፊት ከዩኒቨርስቲ ሥራዬ በሚተርፉኝ ሰዓቶች እዚሁ ከተማ – ለንደን – ይገኝ በነበረ Boston College in London በሚባል አስገራሚ የመንደር ኮሌጅ ውስጥ ማስተማር ጀምሬ ነበር። ሙሉ በሙሉ ማለት በሚቻል ሁኔታ የኮሌጁ ተማሪዎች ከበርማ (የአሳን ሱቺ አገር) የመጡ ናቸው። አብዛኛዎቹ ተማሪዎች የምናገረውን አይሰሙም፤ እስኪደክመኝ አስረጅቼ ስጠይቃቸው ይደነጋገራሉ። ተማሪ ካልገባው “ስህተቱ የኔ ነው” ብዬ ስለማምን የተለያዩ ዘዴዎችን ፈጠርኩ። ለወትሮው የኔ ክፍሎች “ደባሪ” ከሚባሉት ወገን እንዳልሆኑ ተስፋ አደርጋለሁ። እዚህ ኮሌጅ ውስጥ የነበረኝን ክፍል ማራኪ ማድረግ ግን ተሳነኝ። ከተማሪዎቹ ጋር ጥሩ አግባብ አለኝ፤ ትምህርቱ ግን እየተካሄደ አልነበረም። 

ከጥቂት ሣምንታት በኋላ ምስጢሩን ደረስኩበት። አንደኛው ተማሪዬ ፀጉሩን እያሻሸ “ይህንን ኮርስ አውቀን ለመውደቅ እየተማርን ስለሆነ ብዙ አትልፋ” ሲል “መከረኝ” ። ውይይታችን የሚከተውን በሚመስል ሁኔታ ቀጠለ።

እኔ: ምን ማለት ነው ለመውደቅ አቅዶ መማር? 
እሱ: ይኸውልዎ፣ እኛ እዚህ አገር የመጣነው ለመማር ሳይሆን “ድህነትን ለማሸነፍ ነው”። የተማሪ ቪዛችን በሳምንት የተወሰኑ ሰዓታትን (ሁለት ቀናት ያለኝ ይመስለኛል) የመሥራት መብት ይሰጠናል። በእሱ የኮሌጁን ከፍለን ትንሽ አስተርፈን ራሳችንንም ቤተሰቦቻችንን መርዳት ነው ዓላማችን። 
እኔ: አዝናለሁ፤ ግን ይህ ለመውደቅ ከመማር ጋር ምን ያገኛኘዋል? እንዲያውም ደክማችሁ ያመጣችሁትን ገንዘብ የከፈላችሁበትን ትምህርት በትጋት እንድትከታተሉ ያደርጋችኋል። 
እሱ: በህግ በሚፈቀድልን ሰዓት የምንሠራውማ ከትምህርት ክፍያና ከቤት ኪራይ አያልፍም። አሁን ክፍል ውስጥ የምታየው ሰው ሁሉ ማታ ሲጠረግ፣ ሲያጥብ ያደረ ነው። 
እኔ: የምትነግረኝ ሁሉ ቢያሳዝንም “ለመውደቅ መማር” ያልከውን አይገልፀውም። 
እሱ: ይህንን ኮርስ ካለፍን እንመረቃለን። ከተመረቅን ቪዛችን ያልቃል። አሁን እኔ እያንዳንዱን ኮርስ እየደገምኩ የሁለት ዓመቱን ትምህርት 4 ዓመት አቆየሁት። አሁን ማለቁ። አንድ ሴሜስተር የመቆየት ተስፋ ያለኝ ይህንን ኮርስ ከወደቅሁ ነው። 

በሚቀጥለው ክፍለ ጊዜ ለተማሪዎቼ ግልጽ ድርድር አቀረብኩ። “የማርክ ጉዳይ ራሱን የቻለ ሌላ ርዕስ ነው። ከፈለጋችሁ ትምህርቱን አውቃችሁትም እያለ በታቀደ ሁኔታ ፈተና መውደቅ ትችላላችሁ፤ ማወቃችን ፈተና ያሳልፈናል ብላችሁ አትፍሩ። ሆኖም የከፈላችሁበት ነውና ትምህርቱን ብትማሩት ለሕይወታችሁ ይጠቅማችኋል። በዚህ መንፈስ ለመማር የምትፈልጉ እነማን ናችሁ?” ጥቂት እጆች ወጡ። መማር የሚፈልጉትን ወደ ፊት መስመር በማምጣት ትኩረቴን እነሱ ላይ አደረግሁ። ሌሎች እንዳይረብሹን፤ ሌላ የሚጠቅማቸውን ነገር እንዲሠሩ ተስማማን። ከዚህ ቢያንስ ሁለት ጥቅሞችን አግኝተናል ብዬ አስባለሁ፤ 1ኛ) መማር የሚፈልጉትን በተሻለ ትኩረት መርዳት ቻልኩ 2ኛ) ሌሎችም ሰዓቱን ይበልጥ ለሚጠቅማቸው ነገር ተጠቀሙበት – የተወሰኑ ቡድኖች ክፍለ ጊዜውን የሞባይል አፕሊኬሽኖች አጠቃቀምንና ሞባይል ራሱን መፍታት መግጠምን ተማማሩበት፤ ጥቂት የማይባሉትም “ሳያስጠጡ ተኙበት”። ይህ ከሆነ ከሁለት ዓመት በኋላ ኮሌጁ ራሱ የጥራት ደረጃ ባለሟሟላቱ ተዘግቷል።

ይህንን ማስታወሻ እንድጽፍ ያደረገኝ የሰሞኑ የኢሕአዴግ የግዴታ ስልጠና ነው። ለመማር ያልተዘጋጀን ሰው በግዴታ ማስተማር ማደንዘዝ ነው። ኢሕአዴግ የግዴታ ስልጠና እየሰፋ በሄደ መጠን ራሱን ይበልጥ እያስጠላ፤ ሰልጣኙን ደግሞ በተወሰነ መጠን እያደነዘዘ እንደሚሄድ ምንም ጥርጥር የለውም። ሰልጣኖች ብቻ ሳይሆኑ አሰልጣኖችም እያቅለሸለሻቸው እንደሚያሰለጥኑ እየሰማን ነው። ሕወሓት ኢሕአዴግን ደነዝ አደረገው። ኢሕአዴግ በተራው በግዴታ ስልጠና ሕዝብን ሊያደነዝዝ ተነስቷል። ይህንን የኢሕአዴግ ስልጠና ለሚረባ ነገር ማዋል ካልቻልን ጉዳቱ ከፍተኛ ነው። የኢሕአዴግ ስልጠናዎችን የነፃነት ኃይሎች መተዋወቂያ፣ መደራጃ፣ መረጃ መለዋወጫ ማድረግ ይገባል። የኢሕአዴግ ስልጠናዎች የራሱን የኢሕአዴግ ጉድጓድ መማስ አለባቸው። እንደ ኮሌጁ ሁሉ እነዚህ የግደታ ስልጠናዎች የኢሕአዴግን እድሜ ማሳጠር ይኖርባቸዋል።