በቋራ ያሉ የናይጄሪያ ዘላኖችና ‹ሸውሽዌ› ክፍል ፪

By Muluken Tesfaw

በቋራ ያሉ የናይጄሪያ ዘላኖችና ‹ሸውሽዌ›

ክፍል ፪

በዚህ በርሃና ጫካ ብዙ ገራሚ ነገሮች አሉ፡፡ መንደሮች በድንገት በሚነሳ ቋያ ሙሉ በሙሉ ይድማሉ፡፡ በርሜልን ጨምሮ ብዙዎቹ የሰፈራ መንደሮች በበርሃ ቋያ በየጊዜው እየወደሙ እንደገና ይሰራሉ፡፡ የበርሃ ሰው ተስፋ አይቆርጥም፤ ነገ በቋያ ቤቱ እንደሚወድምበት እያወቀ እንደገና ይገነባል፤ ይቃጠልበታል፤ ይሰራል…

በየመንገዱ ጅራታቸው የውሻ ያክል የረዘመ በጎች በብዛት አሉ፡፡ እነዚህ በጎች ‹ፈላታ› በመባል ይታወቃሉ፡፡ ፈላታዎች የናይጀሪያ ዘላኖች በጎች ናቸው፡፡ በጎቹ በዘላኖቹ ስም ፈላታ እየተባሉ ይጠራሉ፡፡ የናይጀሪያ ዘላኖች የሱዳንና የቻድን መሬት አልፈው ለምን ቋራ እንደከተሙ ለኔ ብዙ እንቆቅልሽ ነው፡፡ ነገር ግን ቋረኞች እንደሚሉት በቋራ ጫካዎች ውስጥ ፈላታዎች ከብቶቻቸውንና በጎቻቸውን ያረባሉ፡፡ እርግጥ ነው አካባቢው የግጦሽ ሳርና ውኃ ችግር ስለሌለበት ለከበት አርቢዎች ምቹ ቦታ ነው፡፡ የፈላታ ከብቶች አውሬዎች ናቸው፡፡ አበሻ ካዩ አባርረው ይዋጋሉ፡፡ ብዙ ግዜ አበሻዎች ከዛፍ ካልወጡ በስተቀር አያመልጧቸውም፡፡ ነገር ግን አበሾች የፈለታዎችን ከብቶች በጥይት በመምታት እንደሚወስዱባቸው ሰምቻለሁ፡፡ የፈላታ በጎች ተራብተው በድፍን ቋራና መተማ በብዛት አሉ፡፡ መልካቸው ነጫጭ ሲሆን ጸጉር የላቸውም፡፡ ጅራታቸው ረጅም ነው፡፡ ሥጋቸው ቆንጆ ነው ሲሉ ሰምቻለሁ፡፡ እርግጥ ነው የሔድኩበት ቀን አርብ በመሆኑ የበግ ሥጋ አልበላሁም፡፡

ወደ ጫካ አንድ ሰው ጂፒኤስ ሳይዝ ከሔደ የመጥፋት እድሉ ከፍተኛ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ አዲስ የመጣ የመንግሥት ተቀጣሪ ከሆነ መስክ ብቻውን መሔድ የለበትም ይላሉ፡፡ ወደ ጫካው ከሔደ በኋላ በርሃው ሕሊናውን ያነሆልለዋል፡፡ በበርሃ ሕሊናን የመሳት ሒደት ‹ሽውሽዌ› ይባላል፡፡ ሽውሽዌ የያዘው ሰው አቅሉን ስቶ ከመጓዝ ውጭ ወደየትና እንዴት እንደሚሔድ አያውቅም፡፡ በዚህ በርካታ ሰዎች ጠፍተው ቀርተዋል አሉ፡፡ ‹አሉ› የምለው ሰዎች በነገሩኝ መሠረት ስለምነግራችሁ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ይህች ሽሽዌ የምትባል ‹ነገር› አንዳች መለኮታዊ ነገር ይኑራት አይኑራት የሚታወቅ ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡ እርግጥ ብዙ ሰዎች እንደ ሰይጣናዊ ሥራ የሚቆጥሩት አሉ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ የአየር ንብረቱ ሞቃታማ መሆን የሰውነታችን ሥነ ሕይወታዊ (ፊዚዎሎጅካል) ሥራ ስለሚያወከው አእምሯችን በአግባቡ ሥራውን ማከናወን ያቅተዋል፡፡ በዚህም አቅጣጫ የመለየት ችግር ይገጥመናል የሚሉ አሉ፡፡ ነገር ግን የትኛው ትክክል እንደሆነ የተሰራ ጥናት አላየሁም፡፡ አቅጣጫ ሲጠፋ በአካባቢው የሚኖሩት ጉምዞች አቅጣጫን ለማወቅ የሚሆናቸው የለም፡፡ አንድ ጊዜ እንዲህ ሆነ አሉ፡፡ አንዲት ግብርና ተመድባ የመጣች ሴት ወደ ጫካው የገጠር አካባቢ ትሔዳለች፡፡ ብዙ እንደተጓዘችም ሽውሽዌ ትይዛታለች፡፡ ያኔ ወደየት እንደምትሔድ ሳታውቅ ብዙ ከገለጎ (የወረዳው ከተማ) ርቃ ሒዳለች፡፡ በዚህም ከፈላታዎች እጅ ትገባለች፡፡ እንደነገሩኝ ከሆነ ይህች ልጅ ፈላታዎችን አግብታ እርሷም ዘላን ሆና በመኖር ላይ ነች፡፡

ፈላታዎች ሴቶችን ጠልፈው ወይም ሽውሽዌ ከወሰደላቸው መቼም አይለቁም፡፡ በዚህ የተነሳ ይህች ሴት አንዳንዴ ለዘመዶቿ ደብዳቤ ከመጻፍ የዘለለ ከጫካ ውጭ ያለውን ዓለም በሽውሽዌ ከተጠለፈችበት ጊዜ ጀምሮ አይታው አታውቅም፡፡ ለማምለጥ ብትሞክር በፈላታዎች ጥቃት ስለሚደርስባት አስባም የምታውቅ አይመስልም፡፡ ፈላታዎች ብዙም ልብስ መልበስ የለመዱ አይደሉም፡፡ በሬዎቻቸውም ሆነ እነርሱ የማሽተት ኃይላቸው ከፍተኛ እንደሆነ ይነገራል፡፡ አደጋ ከመጣባቸው አሊያም አበሻ እየቀረባቸው መሆኑን ከብዙ ኪሎ ሜትሮች ርቀት አውቀው ይርቃሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች አእዋፍም የሚታዘዟቸው ይመስላል፡፡ ወደ እነርሱ እየቀረበ ያለው ሰው ይሁን ሌላ አንበሳ ሁሉንም አእዋፍ ሊነግሯቸው እንደሚችል የወሬ ምንጮቼ ያረጋግጣሉ፡፡

የአካባቢውን ማኅበረሰብ ወባ፣ እባብና ሽውሸዌ ያጠቁታል፡፡ መርዛማ የበርሃ እባብ አለ፡፡ በእጽ የሚከላከሉት ሰዎችም አሉ፡፡ እርግጥ እባብ የሚከላከሉበት እጽ ከሱዳን አስማተኞች የተገኘ ነው አሉ፡፡ አዲስ አበባ እባብ ስለሌለ ጥበቡን ማወቅ እንጅ እጹን አልፈለግኩትም፡፡ ስለዚህ ይዤ አልተመለስኩም፡፡ ጥበቡንም አልቀሰምኩም፡፡ ደሞስ መሥራት አለመሥራቱን ሳላረጋግጥ እንደኔ ዓይነት ቶማስ (ተጠራጣሪ) እንዴት ይዞ ይመጣል? ሽውሽዌ ብዙ ሰው ታጠቃለች፡፡ አንድ ጊዜም እንዲሁ ከቋራ ወረዳ ወደ ገጠር የተላኩ አምስት ያክል ባለሙያዎች በሽውሽዌ ይጠቃሉ፡፡ ሕሊናቸው ነሁልሎ የሚሔዱበትን አቅጣጫ ሳቱ፡፡ ሽውሽዌ የተጠቃ ሰው ያለ አቅጣጫው ኃይሉ እስከሚያልቅ ድረስ መጓዝ ነው፡፡ የእነዚህ ባለሙያዎች ኃይል አልቆ ኖሮ ወደቁ፡፡ ወዳጆቻቸው ለመፈለግ ሞከሩ፡፡ ሊገኙ አልቻሉም፡፡ ከረጅም ጊዜ በኋላ ለሌላ መስክ (ፊልድ) የተላኩ ሰዎች በርሃ ውስጥ ወዳድቀው በክረምት ዝናብ ሣር በቅሎባቸው ተገኘ አሉ፡፡ እንግዲህ ስለ ሸውሸዌና ፈላታ ናይጀሪያውያን ካላይ ያወጋሁት በሙሉ በቋረኞች በተነገረኝ መሠረት እንጅ ከፈለታ በግ ውጭ ያየሁት አንድም ነገር የለም፡፡ እርግጥ ነው ሁሉምን ለማየት አይቻለም፡፡ ደግሞም አደገኞች ናቸው፡፡ ሽውሽዌን ልይ ብል ተመልሦ ይህን ሪፖርት ማን ያስነብባችኋል? ዘላኖቹንም ማግኘት ሌላው ከባድ ነገር ነው፤ ደግሞም የሚመጡበት ወቅት አላቸው እንጅ ዓመቱን በሙሉ አይኖሩም፡፡ እባብ እንኳን በእውን በናሽናል ጂኦግራፊ ሳየውም ውቃቢየ አይወደው፡፡ በወባ ለመለከፍ አንድ ቀን ማደር ይጠበቅብኛል፡፡ ሁሉንም ግን አልሻም፡፡ የሔድኩባት ፒክ አፕ ወደ ሸኽዲ ትመለሳች፡፡

ጊዜ ቢኖረኝ ኖሮ ብዙ ነገር የሚታይ ነበር፡፡ ወደ ደጋማው የቋራ አካባቢ ቴዎድሮስ ከተማ የሚባል አለ፡፡ እዚያ የአጼ ቴዎድሮስ የልጅ ልጆችና ዘሮች እንዳሉ ሰምቻለሁ፡፡ እነርሱን የማግኘት እቅድ ነበረኝ፡፡ ጊዜም ገንዘብም ስለተመናመነ ብሎም ቀጣይ ጉዞ ስላለብኝ ያን በርሃ ትቼው መመለስ ግድ ይላል፡፡ ወጣሁም፡፡ ሸኽዲ ከተማ ባጃጅ ውስጥ ያነበብኩት ጥቅስ ለአካባቢ ምቹ (ኢንቫሮንመንት ፍሬንድሊ) ነው፡፡ እንደ አዲስ አበባ ‹የሰው ትርፍ የለውም› የሚል ጥቅስ እዚህ ቦታ አይታሰብም፡፡ ትርፍ አትጫን የሚል ሕግ የለምና፡፡ ባጃጅ ውስጥ ያለው ጥቅስ ‹ጊዜን አይቶ የማይከዳ ዕውነተኛ ጓደኛ የበርሃ ጥላ ነው› ይላል፡፡ ከዚህ የበለጠ ዕውነት በዚህ አካባቢ የለም፡፡ ቀን ላይ አይቸዋለሁና፡፡

አሁን እየመሸ ነው፡፡ ጀምበር መዘቅዘቅ ጀምራለች፡፡ ወደ ጎንደር የሚሔዱ መኪናዎችም ብዙ የሉም፡፡ ወደፊት 161 ኪሎ ሜትር መጓዝ ይጠበቅብኛል፡፡ ያገኘዋት ሚኒ ባስ በዚያ ሙቀት ሰው ጥቅጥቅ አድርጋ ሞላች፡፡ ጋቢና ነበርኩ፡፡ ጋቢና ሾፌሩን ሳይጨምር ሦስተኛ ሰው ታከለልን፡፡ አይሆንም ማለት አይቻልም፡፡ ዝም ብሎ መጓዝ ነው፡፡ ገንዳ ውኃን አለፈን፤ ደረቅ አባይ፤ ነጋዴ ባህር፤ አርሴማ፣ ሰራባ፣ ጭልጋ…. ጎንደር ምሽት ሦስት ሠዓት ሲሆን፡፡ ነገ ቀጣይ ጉዞ አለ፡፡ ወደ አርማጭሆ፡፡

በላንድ ማርክ ሆቴል የተደረገው የወልቃይት ጉዳይ ስብሰባ

የአርማጭሆን ጉዞ ከመጀመራችን በፊት ግን ትናንት በጎንደር ላንድ ማርክ ሆቴል ስለነበረው የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ብሔርተኝነት የማንነት ጥያቄ ስብሰባ የታዘብኩት ማስቀመጥ እሻለሁ፡፡ ሐሙስ እለት ላንድ ማርክ ሆቴል ስደርስ የእቴጌ ምንትዋብ የስብሰባ አዳራሽ ሞልቶ መፈናፈኛ አልነበረውም፡፡ ውስጥ ገብቼ አንዳንድ ነገሮችን ሪከርድ ለማድረግ ብሞክርም መሹለኪያ መንገድ ጠፋ፡፡ ስለዚህ የነበረኝ አማራጭ ውጭ ላይ ሆኖ በሞንታርቦው የሚነገረውን ማዳመጥ ነበር፡፡ ስብሰባውን የአዘጋጁት የጎንደርና የዳባት አገር ሽማግሌዎች ናቸው፡፡ ወልቃይት ቀድም ባሉት ጊዜያት የቆላ ወገራ አካል ሆኖ አውራጃው ዳባት ነበር፡፡ በዚህም ይመስላል የዳባት የአገር ሽማግሌዎች ከጎንደር ከተማ ጋር በመቀናጀት ስብሰባውን የአዘጋጁት፡፡ ኮሚቴዎቹ የደረሱበትና እየገጠማቸው ያለውን ነገር ሲያስረዱ ሕዝቡ ላይ የቁጭት፣ የንዴትና የተስፋ ስሜቶች ተደባልቀው ይነበቡ ነበር፡፡ በዚሁ ሰሞን በወልቃይት፣ በጠገዴና በኹመራ አካባቢዎች ለሠፈራ ከመጡት የትግራይ ተወላጆች በተጨማሪ በመኪና እየተጫኑ እየመጡ ‹‹ያልተመለሰ የማንነት ጥያቄ የለንም፤ ጸረ ሰላም ኃይሎችን አንታገስም…›› ወዘተ የሚሉ የማወናበጃና የማስፈራሪያ መፈክሮች በሰፊው የመንግሥት መገናኛ ብዙሃን ሽፋን ሰጥተዋቸው ሲስተናገዱ ሰንብተው ነበር፡፡ ነገር ግን የአማራ ተወላጆች ነን ላሉት እንኳንስ ሰላማዊ ሰልፍ ሊፈቀድ ቀርቶ የቤት ውስጥ ስብሰባም ተከልክለዋል፤ አማርኛ ሙዚቃ እንዳያደምጡ ተደርገዋል፡፡ አልፎም ወደ አገራቸው ለመሔድ ኬላዎችን ተሸለክልከው ነው፡፡

የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ከሆኑት መካከል ኮሎኔል ደመቀ የሚባሉት ይህን አስመልክተው ሲናገሩ ‹‹የእነርሱን ትግሬነት እኛ አልካድንም፤ እኛ የምንለው የእኛም አማራነት ይታወቅ ነው፡፡ አማራ የሆነ ሰው እንዴት በግዴታ ትግሬ ሊሆን ይችላል? በግዴታ እንዴት ማንነት ሊሰጠን ይችላል? እኛ እኮ በትግርኛ መርዶ ሰምተን በአማርኛ የምናለቅስ ነን፤ በትግርኛ የሰርግ ጥሪ ተላልፎልን በአማርኛ የምንዘፍን ሕዝብ ነን፡፡ ሕወሓት ጭቆና ወደ ጫካ አስወጣኝ ብሎ እኛ ላይ ያልፈጸመው በደል የለም፡፡ አማራ ነን ብሎ መናገር ምንድን ነው ጸረ ሰላም የሚያስብለው? ጠመንጃ መያዝ ለወልቃይት ሕዝብ ተራ በጣም ተራ ነገር ነው፡፡ ሆኖም ይህ የሚጠቅም ነገር ስላልሆነ በሕገ መንግሥቱና በሰላማዊ መንገድ ብቻ ጥያቄያችን እየቀርብን ነው፡፡ ይህ ጥያቄ የወልቃይት ብቻ ሳይሆን የመላው አማራ ነው፡፡ በእኛ ላይ የሚደርሰውን ግፍ ለማውገዝ የግድ አማራ መሆን አይጠበቅም፡፡ ትግሬዎች ራሳቸው ሕወሓትን በቃህ ሊሉት ይገባል›› በማለት በሰፊው አብራሩ፡፡ አቶ አታላይ ዛፌ የተባሉም በወልቃይት ሕዝብ በተለይ ደግሞ በሱዳን ወታደሮች እየተወሰዱ ስላለቁት የአማራ ወጣቶች፣ በሕወሓት ባለሥልጣናት ስለተደፈሩት ሴቶችና ተማሪዎች፣ ግሕንብ የምድር እስር ቤት ውስጥ ስላለቁት ወልቃይቴዎች በሰፊው ሲዘረዝሩ አንዳንዶች ያለቅሳሉ፤ ሌሎች ደግሞ ያጨበጭቡ ነበር፡፡ ፍጹም ድብልቅልቅ ያለ ስሜት፤ በቃ ደስታና ሀዘን፣ ተስፋና ተስፋ መቁረጥ፣ የዋህነትና በቀል፣ የአንድነትና የልዩነት…. ስሜቶች በአንድ ሰው ገላ ላይ ሳይታዩ አልቀረም፡፡

አንድ ስሙን ሳልሰመው ያለፈኝ የወልቃይት ተወላጅ ሁለቱን ወንድሞቹን የሕወሓት የጸጥታ ቡድኖች ወስደው እንዴት አሰቃይተው እንደገደሉበት ምስክርነቱን ሊሰጥ ማይክራፎኑን (የድምጽ ማጉያውን) ተቀበለ፡፡ ግን አልቻለም፡፡ ምንም እንኳ ግፉ የተፈጸመው ከዐሥር ዓመታት በፊት ቢሆንም አሁንም ድረስ በሐዘኑ ልቦናው እንደተሰበረ ነው፡፡ ሊናገር ሲል ትናገው መከፈት አልቻለም፡፡ በዐይኑ እንባ ፈሰሰ፡፡ ድምጹ ተቆራረጠ፡፡ ብዙ በጣም ብዙ በስብሰባው የነበሩ ሰዎች ዝም ብለው ማዳመጥ አልቻሉም፡፡ የሰዎች ኪስ ሲንኮሻኮሽ ይሰማል፡፡ ሶፍት ወይም ማኅረም ፍለጋ ነበር፡፡ የዛሬ ዐሥር ዓመት የተገደሉ ሰዎች ዛሬ መርዶአቸው የተረዳ መሠለኝ፡፡ ወንድ ልጅ ሲያለቅስ ማየት አልወድም፡፡ ቀረጻ ላይ ነበርኩ፡፡ እንባየ ተናነቀኝ፤ ታገልኩት፤ አልቻልኩም ፈሠሠ፡፡

ግለሰቡ ወንድሞቹን ከእናታቸው ነጥለው ወስደው አሰቃይተው ገድለውበታል፡፡ እርሱም አገር አለኝ ብሎ ተመልሶ አያውቅም፡፡ እንኳን ወልቃይት ሊሔድ ቀርቶ ጎንደር ኹመራ መውጫን ወለቃን አልፎ አያውቅም፡፡ በሐዘን የተሰበረ ልብ ይገርማል፡፡ በወልቃይት ሕዝብ ላይ ሕወሓት የፈጸመው ግፍ በቀላሉ ተነግሮ እንደማያልቅ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ ሰዎች ተገድለው በአዲ ረመጥ ከተማ በመኪና ላይ ተጭነው ለሕዝብ መቀጣጫ እንዲሆኑ እንደ ደርግ የቀይ ሽብር ሰለባዎች በዚህ ዘመን የተፈጸመው ከወልቃይት ሕዝብ ውጭ የትም አይኖርም፡፡ አማራ በግዴታ ወደ ትግሬነት የተቀየረው ከወልቃይት ሕዝብ ውጭ በአገራችንም በዓለማችንም አይኖርም፡፡ እውነታው ይሔ ነው፡፡ ከሌሎች የአማራ ክልል አካባቢዎች እኛም ጋ መጥታችሁ ጉዳዩን አስረዱን የሚሉ ጥያቄዎች ብዙ ነበሩ፡፡

ጎንደር ስሔድ ምሽት ላይ ብዙ ጊዜ ወደ አጼ በካፋ የባህል ምሽት ማዝገሜን አልተውም፡፡ ጥሎብኝ የዚህ የባህል ምሽት እወደዋለሁ፡፡ የዛሬው አካሔዴ ግን ለመዝናናት እንዳልሆነ ብናገር ተአማኒነት ስለማይኖረው ብዙም ምክንያት ማቅረብ አልሻም፡፡ ብዙ ዜጎቻችን በርሃብ ጠኔ የሚበሉትን አጥተው እየተቸገሩ እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ ይህንንም አይቻለሁ፡፡ በሰፊው ወደፊት ስለምሔድበት አሁን አልቀላቅልም፡፡ ቀን ላይ በወልቃይቶች ላይ የደረሰውን ስሰማ በእውነቱ እድሜ ልኬን በሐዘን የምኖርም መስሎኝ ነበር፡፡ ነገር ግን የሰው ልጅ ጠንካራ ፍጥረት ነውና የሐዘን ብዛት አጥንቱን አይሰብረውም፤ የመደሰቻ ሕዋሳቱን አያደነዝዝም እንጅ ትንሽ ብቻ በቂ ነበር፡፡ የሆነው ሆኖ አዝማሪ ምን አለ ለማለት ነበር የገባሁት፡፡

ተንኮለኛው ጋዜጠኛ ተስፋየ ገብረ አብ አንድ ጊዜ ጎንደር ሒጄ ሰማሁት ያላቸውን የአዝማሪ ግጥሞች አስታወስኩ፡፡

ጎንደር አገር ጠፍቶ ሲፈለግ ሌሊት

ቀን ታዲሱ ጋራ ሲሔድ አየሁት፤

በረከት አገሩ ስለናፈቀው

ዳሸን አናት ሆኖ አስመራን አየሁ፡፡

እነዚህን ግጥሞች ጎንደር በሔድኩ ቁጥር አዝማሪ ለአዝማሪ ቤት እየዞርኩ ልሰማቸው ፈልጌ አልተሳካልኝም፡፡ ግን የጎንደር አዝማሪ ከእነዚህ በላይ የግጥም ቅኔዎች ማሽሞንሞን ይችላል፡፡ ለምሳሌ ይህን ግጥም በሕሊናችሁ በማሲንቆ አጃቢነትና በመረዋ የቡርቧክስ አዝማሪ ድምጽ ስሙት (ቡርቧክስ ከጎንደር ከተማ 40 ኪሎ ሜትር ያክል የሚርቅ ማክሰኝት የምትሰኝ ከተማ ወደ በለሳ መውጫ በኩል ያለ የገጠር ቀበሌ ሲሆን የበርካታ አዝማሪዎች ቀዬ ነው)፡፡

ኧረ አገሬ ጎንደር ሸንበቆው ማማሩ፣

አገሬ ወስከንቢት ሸንበቆው ማማሩ፤

ኧረ አገሬ ቋራ፣ መተማ አርማጭሆ ሸንበቆው ማማሩ

አገሬ ወልቃይት፣ ቃፍታና ኹመራ ሸንበቆው ማማሩ፣

ቆርጠው ቆርጠው ጣሉት ለም-አገር እያሉ!

አዝማሪው አገሩን በሸንበቆ መስሎ ለም ለም የሆነው ሁሉ ተቆርጦ አንድም ለሱዳን አሊያም ለታላቋ የትግራይ ሪፐብሊክ ምስረታ መወሰዱን በቁጭት ነው በቅኔ የሚገልጸው፡፡ የሆነው ሆኖ በዚያ ቀን አብዛኛው በበካፋ የባህል ቤት ሲዘፈን ያመሸው ስለወልቃይት ነው፡፡ አንድ ራሰ በራ ድምጸ መረዋ አዝማሪ አለ፡፡ የድምጹ ነገር ወፍ ከሰማይ ያወርዳል፤ ወይንም በአገራችን አባባል ነብር ይጠራል፡፡ የፋሲል ደመወዝን ‹‹አረሱት መተማ፣ አረሱት ኹመራን የውም የእኛን እጣ፣ እነርሱ ምን ያርጉ ከእኛ ሰው ሲታጣ›› ያለ ጊዜ የምድር ቤት ውስጥ ያለው አዳራሽ በጩኸት ተናወጠ፡፡ መቼም በጩኸት ከኢያሪኮ ከተማ ውጭ የፈረሰ ግንብ አልሰማሁም እንጅ ያን እለት የነበረው ጩኸት ከዚህ ላይ ለመግለጽ ቃላት መፈለግ ግድ ይለኛል፡፡

አዝማሪው ያዘምራል፡፡ እንዲህ በማለት

ኧረ አገሬ ጎንደር ሰሜን ጃናሞራ ወልቃይት ጠገዴ፣

ለራበው እንጀራ ለጠገበው ጓንዴ!

ወደ መድረክ ሰው ሁሉ መቶ ብር መወርወር ጀመረ፡፡ በዚያ ምሽት ቤቱን አይቶ የማያውቅ እንግዳ ሰው ቢገባ የቤቱ ሕግ መስሎት መቶ ብር እንደሚወረውር በእርግጠኛነት መናገር እችላለሁ፡፡ መድረክ አካበቢ ወደ አዝማሪው ስመለከት ውር ውር የሚሉ አረንጓዴ ቢራቢሮዎች ባለማሲንቆውን ሸፍነውታል፡፡ አዎ ቢራቢሮዎች አይደሉም፤ የባለ መቶ ብር ኖቶች እንጅ፡፡ ከዚህ ቤት ውስጥ የታመቀ ብሶት ፈንድቷል፡፡ የተጠራቀመ ቁጭት ፈሷል፡፡ ወጣቱ ደሙ ፈልቷል፡፡ ባርነትን በቃህ የሚል ይመስላል፡፡ ማንም ይህን የተናገረ የለም፤ እኔ ግን እያንዳንዱ ሰው ፊት ላይ ያለውን ስሜት አንብቤዋለሁ፡፡ ሊመርጅ የገባው የደህነንቱም ሰው ስሜት ቢሆንም!!

እስኪ አንድ ሰው እስክስታ እየመታ ሲያነባ፣ ግማሽ ፊቱ የብርሃን ጸዳል ወርሶት ግማሹ ግን የዳመነ ሲሆን፣ ውስጡን በነገር ሞልቶ መተንፈስ አልችል ሲል፣ ሁለት ፍጹም ተቃራኒ ስሜቶች በአካላቱ ላይ ሲነበቡበት ያያችሁት ሰው አለ? ወይስ ይህ ስሜት ገጥሟችሁ ያውቃል? እኔ በዚያ ቤት ውስጥና በዚያ ሰዓት ያየሁት ግን ይህ ነው፡፡ ቤቱን ሁለት ፍጹም ተቃራኒ መናፍስት ወርሰውት አምሽተዋል፡፡

የሚቀጥል

የኢትዮ ሱዳን ድንበርን ለማጣራት ያደረግኩት ድካምና ውጤት

By Muluken Tesfaw

የኢትዮ ሱዳን ድንበርን ለማጣራት ያደረግኩት ድካምና ውጤት

ክፍል ፩

የካቲት 24 ቀን 2008 ዓ.ም. ጎንደር ከተማ አደርኩ፡፡ እራት ላይ ‹ትእቢት› የሚባል ምግብ በልቼ ተሰቃይቻለሁ፡፡ ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ ናይል ሆቴል ከአንድ የቀዬ ወዳጄ ጋር ሒደን ራት ስናዝዝ ‹የቤቱ ምርጥ ዛሬ ምንድን ነው?›› አልናት አስተናጋጇን፡፡ ‹‹ትእቢት ይምጣላችሁ›› አለችን፡፡ በስሙ እየተገረምን ምግቡ ምን ዓይነት ይሆን ይሆን? እያለን የሚጠጣ አዘዝን፡፡ ‹ምኒልክ› በጎንደር የድራፍት መጠጫ ሆኖ አገኘሁት፡፡ የምኒልክ ብርጭቆ ስለተመቸን ነው መሠል ደጋግመን ተጎነጨን፡፡ የምር በምኒልክ ጃምቦ መጠጣት ደስ ይላል፡፡ ምግቡ መጣ፡፡ መመገብ ጀመርን፡፡ በአጭሩ ምግቡ የሚጣፍጥ ነገር ግን የሚያሰቃይ ነው፡፡ የተፈጨው ሥጋ በበርበሬ ተለውሶ ከዚያ ላይ ቃሪያ (ቄጦ) ታክሎበት የሚጣፍጥ ሆኖ ነው የቀረበ፡፡ እንዳንበላ ያቃጥላል፤ እንዳንተወው ይጣፍጣል፡፡ ደጋግሜ በጎርስኩ ቁጥር በፊቴ ላይ ላቨት መንቆርቆር ጀመረ፡፡ ምግቡ እልክ ያስይዛል፡፡ በላይ በላዩ በምሊክ ድራፍቱን ባንቆረቁርበትም ሊበርድ የሚችል አልሆነም፡፡ እንዳሉትም ትእቢት ያራግፋል፡፡ የሆነው ሆኖ እንዲህ ያለውን ምግብ የጤና ጥበቃ ቢከለክለው የሚል ሐሳብ አለኝ፡፡ የሆቴሉ ባለንብረቶች አንድ ቀን አንድ አቅመ ደካማ ሰው እንዳያሸልብባቸው እሰጋለሁ፡፡

የካቲት 25 ቀን 2008 ዓ.ም. ወደ መተማ ማልጄ ወጣሁ፡፡ እግረ መንገዴን ባለፉት ወራት ከቅማንት የማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ የደረሰውን ጉዳት ለማጣራት አሰብኩና እያቆራረጥኩ መጓዝን መረጥኩ፡፡ ከጎንደር ጭልጋ፣ ሰራባ፣ ነጋዴ ባህር፣ ገንዳ ውኃና መተማ በየተራ እያረፍኩ ጉዞ ጀመርኩ፡፡ በየቦታው የተወሰኑ ሰዎችን ለማነጋገር ሞክሬያለሁ፡፡ ሁሉም ግን የሚሰጡኝ መረጃ የተቀራረበ ነው፡፡ ከቅማንት የማንነት ደጋፊዎች ጋር ባደረግኩት ሁሉ አብዛኛዎቹ ብአዴን ሆን ብሎ ቅማንቶችን በወታደር አስጨፍጭፏል የሚል ቅሬታ ይቀርባል፡፡ የሚነግሩኝን ከመስማት ውጭ ምን ያክል እውነት እንደሆነ ማረጋገጥ አልቻልኩም፡፡

ከመተማና ጭልጋ ወረዳዎች ያሉ አንዳንድ ሲቪል ሠራተኞች የነገሩኝ በጣም አስደንቆኛል፡፡ ከባድ ሆኖ ያገኘሁት ነገር ቢኖር ከሰው ጋር በቀላሉ ግንኙነት መመስረት ነው፡፡ ማንም ሰው ማንንም አያምንም፡፡ መንግሥትን ብታማም ብታሞግስም የወያኔ ሰላይ ነው ተብሎ ይታሰባል፡፡ እንዲሁ ማኅበራዊ ነገሮችን ለማውራት ደግሞ ቶሎ ወደ ወቅታዊ ጉዳዮች ሊገባ የሚችል ሰው የለም፡፡ በዚህ ምክንያት ጥናቴን አስቸጋሪ አድርጎብኝ ነበር፡፡ ከተጓዦች አሊያም ምግብና ካፌ ላይ ከሚጠቀሙ ሰዎች ጋር ግንኙነት ለመመስረት አስቸጋሪ መሆኑን መግለጽ በቂ ነው፡፡

ባለፈው የቅማንት የማንነት ጥያቄን ምክንያት በማድረግ የብዙ ሰዎች ሕይወት አልፏል፡፡ የሚያሳዝነው ጎረቤት ከጎረቤት ተገዳድለዋል፡፡ ባልና ሚስት በተኙበት በጩቤ ተወጋግተዋል፡፡ እያንዳንዱ የሆነው ነገር ሁሉ እጅግ የሚያሳዝንም የሚያስተክዝም ነገር ነው፡፡ አንድ ቋንቋ እያወሩ፣ አንድ እምነት እየተከተሉ አብረው አድገው፣ ተዋልደውና ከብደው እርስ በእርስ ለመተራረድ ከመፈላለግ በላይ አሳዛኝ ነገር የለም፡፡ ብዙ ቤቶችና በአውድማ ላይ ያለ ምርት በቃጠሎ ወድሟል፡፡ ለሺህ ዓመታት አብሮ የኖረ ሕዝብ እንዴት እንዲህ ሊሆን እንደቻለ እንቆቅልሽ ነው፡፡ ማንም እንግዳ ሰው ከዚያ አካባቢ ቢሔድ ያለውን ልዩነት ማሳዬት እንደማይችል በእርግጠኛነት መናገር ይቻላል፡፡ ታዲያ ለምን ይህ ሆነ? ብለን ስንጠይቅ ነዋሪውም ሆነ አመራሩ ተጠያቂ የሚያደርገው ሕወሓትን ነው፡፡ ሕወሓት በወልቃይትና ጠገዴ የተነሳውን ተቃውሞ ለማፈን የፈጠረው ብሎም የቅማንት ሕዝብ የአርማጭሆን፣ የቋራን፣ የደንቢያንና የወገራን በከፊልና ሙሉ አካባቢዎችን በመያዝ አዲስ ማንነት ከፈጠረ በወልቃይት የተጀመረው የመስፋት (ታላቅ የመሆን) ምኞት ለማስፈጸም እንደሆነ ሁሉም ሰው ይናገራል፡፡ ባለፉት ዓመታት የታችና ምዕራብ አርማጭሆን አካባቢዎች ወደ ትግራይ ለመጠቅለል ሰሊጥ ለማምረት የመጡት የሕወሓት ሰዎች የፊርማ ማሰባሰብ ሥራ ጀምረው እንደነበር ያስታውሳሉ፡፡ ጎንደር ላይ ትምህርት በትግርኛ እንዲሰጥ ጥያቄ ቀርቦ እንደነበር ሁሉ ከሕጻን እስከ አዋቂ የሚያውቀው ነው፡፡

ባለፉት ወራት በነበረው የእርስ በእርስ ግጭት የተፈጠረው እጅግ የሚያሳዝን ነው፡፡ ከላይ የገለጽኩት አዲስ ያልኩት መረጃ የሚከተለው ነው፡፡ ከብዙ የማኅበረሰቡ ክፍሎች ብሎም ከአመራሮች ለማረጋገጥ ሞክሬያለሁ፡፡ የተባለውን እውነት ነው ለማለት ግን እኔ አላየሁትም፤ የተነገረኝ ግን ይህ ነው፡፡ ግጭቱ ሊፈጠር ጥቂት ቀናት ሲቀሩት ከትግራይ ክልል በሽተኛን በሚያመላልስ አምቡላንስ መትረጊስ ተጭኖ ወደ ጭልጋ ገባ፡፡ መትረጊሱ በአምቡላንስ የመጣበት ምክንያትም አምቡላንስ ስለማይፈተሸ ነው፡፡ አንዲት የጀበና ቡና በማፍላት የምትተዳደር ሴት እጅግ በርካታ መጠን ያለው ገንዘብ በጉንፏ (በልብሷ ደብቃ) ይዛ መግባቷን ሁሉ በድፍን ጎንደር ይወራል፡፡ የመጣው መትረጊስ በርካታ ዜጎችን መቅጠፉ ያሳዝናል፡፡ በተለይ ደግሞ የተጨራረሰው በአንድ ሕዝብ መካከል ልዩነት ለመፍጠር መሆኑን ማወቅ ለአእምሮ ሰላም አይሰጥም፡፡ ይህ ሁሉ እንግዲህ የተደረገው ጎንደሬን እርስ በእርሱ ለማጫረስ በሕወሓት የተሸረበ ሴራ መሆኑ ነው፡፡ ይህን መረጃ አንድ ሕጻን ልጅም፣ አዛውንትም፣ ተራ ተቀጣሪ ሠራተኛም፣ ካቢነውም የሚያወሩት ነው፡፡ አሁን ላይ ሕዝቡ ወደ ቀደመው አንድነቱ የተመለሰ ይመስላል፡፡ በሁለቱም ወገን ማን እያፋጃቸው እንደሆነ ግንዛቤ እንደወሰዱ ያወራሉ፡፡ ብስለት የሚመጣው ዘግይቶ ሆነና የሞቱት ሰዎችን ሕይወትና የጠፋውን ንብረት ማስመለስ አልተቻለም፡፡ ለወደፊትም ይህ እንዳይደገም ስምምነት መኖሩ የሚያስደስት ነው፡፡

ከጎንደር እስከ መተማ ድረስ በየቦታው የወዳደቁ መኪናዎች ይበዛሉ፡፡ ይደንቃል፤ በመኪና አደጋ የሚረግፈውን የአገሬ ዜጋ ሳስብ አዘንኩ፡፡ በአማካይ በየዐሥር ኪሎ ሜትር የተጋጩ መኪናዎችን ወይም መስመር ወጥቶ የተከሰከሰ ተሸከርካሪን ማዬት ይገርማል፡፡ ከጎን የተቀመጡትን ስጠይቅ ‹ይህ ትናንት ነው፤ ዐሥራ አምስት ወታደሮችን የጫነች ኦራል መኪና ከሚኒ ባስ ጋር ተጋጭታ ስትገለበጥ ሁሉም ወታደሮች አመድ ሆኑ፤ የሚኒባሱ ጋቢና ያሉት አልተረፉም፡፡ ይህ ደግሞ ከሱዳን መኪና ጋር ተላትሞ ነው፡፡ ሲኖማ ሲሔድ ጭኖ ሲመለስ ተጭኖ› የሚሉ ነገሮችን ትሰማላችሁ፡፡ ብዙ አደጋ የደረሰባቸውን ተሸከርካሪዎች ባየው ቁጥር ከጎኔ ያሉ ሰዎችን መጠየቅ ሰው ያሰለቻል ብየ ስለማስብ አንዳንዴ እኔም እየሰለቸኝ ዝም ብዬ እጓዛለሁ፡፡ የእኛ ሕይወትም ከእነዚህ እንደ አንዱ እንዳይሆን አሰጋለሁ፡፡

አካባቢው ሙቀቱ ከፍተኛ ነው፡፡ መንገዱ ዳርና ዳር በበርሃ ግራሮች የተሸፈነ ነው፡፡ በርቀት ግራሮቹን ሲያዩያቸው ነጫጭ ወፎች ያረፉባቸው ነው የሚመስሉት፡፡ ምንድን ነው? ብዬ ስጠይቅ ጥጥ የጫኑ መኪናዎች ሲመጡ ጥጡን ዛፎቹ ስለሚያስቀሩት ግራሮቹ በሙሉ ጥጥ አባዛች (ደዋሪ) ሆነዋል፡፡ መተማ ከተማ ወረድኩና ምሳ በላሁ፡፡ ወደ ጋላቫት እስከ ዐሥራ አንድ ሠዓት ድረስ መግባት ይቻላል፡፡ ጋላቫት ማለት ብዙ ኢትዮጵያውያን የሚነግዱባት የሱዳን ከተማ ነች፡፡ መተማ ማለት ደግሞ ብዙ ሱዳናዉያን የሚሰክሩባት የኢትዮጵያ ከተማ ነች፡፡ ጋላቫት ብዙ የአገራችን ሴቶች በረንዳ ላይ ቡና እያፈሉ ገላቸውንም ጭምር የሚሸጡ አሉ፡፡ ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር በአካባቢው የበዛ በመሆኑ ብዙ ዓይነት ቋንቋ ተናጋሪ ሴተኛ አዳሪዎች አሉ፡፡ አዘዋዋሪ ደላላዎቹ ካርቱም አሊያም ሊቪያ እናደርሳችኋለን ወደ ኢጣሊያም በቀላሉ ትገባላችሁ እያሉ ገንዘባቸውን ከወሰዱባቸው በኋላ እንጣጥ ፍርጥ እያሉ ከአንዱም ሳይሆኑ ሴተኛ አዳሪ ብቻ ሆነው ይቀራሉ፡፡ የሱዳን ሲም ካርድ ይገዙና ቤተሰቦቻቸውን በሱዳን ሞቫይል በመደወል መተማ ተቀምጠው ካርቱም ነው ያለሁት እያሉ የሚደልሉ ሞኞችም ሞልተዋል፡፡
እንደሰማሁት ከሆነ በሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውሩ አንዳንድ ቱባ የመንግስት ባለሥልናትና የፌደራል ፓሊስ አባላት አሉበት፡፡ ደላላዎቹ ወደ ሱዳን ለመሻገር የመጣን ሰው በቀላሉ የሚለዩበት ክሕሎት የሚገርም ነው፡፡ የድንበር ከተማ ከመሆኑ አንጻር ብዙ አዳዲስ ሰዎች ማየት የሚደንቅ አይደለም፡፡ ነገር ግን አዲስ መተማ ከሚደርሱ ሰዎች መካከል የትኛው ወደ ሱዳን እንደሚሰደድ አሊያም ለኮንትሮቫንድ ንግድ እንደመጣ ማወቅ ለደላላዎቹ ምንም ያክል አይከብድም፡፡ በደላላ እጅ የገባች ተሰዳጅ ደላላው በፈለገው ነገር ያሳምናታል፡፡ ለደላላዎች የእራሳቸውን ሽያጭ ዋጋ ከከፈሉ በኋላ ያሰቡበት ቦታ ሳይደርሱ ከኮሚሽን ተካፋይ ባልሆነ ወይም ቅሬታ በገባው የጸጥታ አካል ተይዘው መተማ ፖሊስ ጣቢያ ይታሰራሉ፡፡ እነዚህ እህቶች አንዳችም ነገር ሳያስቀሩ ለደላላው ሰጥተዋል፡፡ ደላላው ደግሞ ከዚህ በኋላ አይገኝም፡፡ ያላቸው ብቸኛው ተስፋ ራሳቸውን መሸጥ ብቻ ይሆናል ማለት ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ሴተኛ አዳሪ ሆነው የቀሩ እህቶች ቁጥር የትየለሌ ነው፡፡ የበርሃ ሰው የመጠጥና የሴት ነገር አይሆንለትም፡፡ የፍየል ግንባር በምታክል ከተማ ያን ያክል ሰው በዚህ መተዳደሩ ለዚህ ነው፡፡ በአናቱም ሱዳናዉያን ወደ መተማ የሚሻገሩት አንድም ቢራችንን አሊያም እህቶቻችንን ለመሸመት ነው፡፡ መጀመሪያ በገንዛ ብራቸው (ገንዘባቸው) ራሳቸውን ለደላላ የሸጡ ሴቶች ገላቸውን ቸርችረው አጠራቅመው ነገም ካርቱም አሊያም ጣሊያን ለመድረስ ተስፋን ይሰንቃሉ፡፡ የሰው ልጅ ምን ያክል ተስፈኛ መሆኑን ተገንዝቤያለሁ፡፡ ወላጆቻቸውን በውሸት ካርቱም ተቀጥሬ እየሰራሁ ነው ያለች አንዲት የጂማ ልጅ መተማ መቀመጧን ማንም እንደማያየት እርግጠኛ ስለሆነች ነው፡፡ በዚያ ላይ የሱዳን ሲም ከኢትዮ ቴሌኮም በተሻለ ኔትወርክ መሥራቱ ላይክስ አይበድል ነው፡፡ ገላቸውን ቸርችረው ትንሽ ገንዘብ ማጠራቀም የቻሉ ሴቶችም ወደ ኢትዮጵያ የሚመጣ ሰው አግኝቻለሁና ከጎንደር በባንክ ይልክላችኋል ብለው ለቤተሰቦቻቸው በመንገር በሌላ ሰው ስም መተማ ባሉ ባንኮች የሚልኩ አሉ፡፡

ሳስበው አገራችንን ጥለን ለመሔድ ራሳችንን ክደን ክብራችንን አውልቀን የጣልንበት ጉድጓድ ጥልቀት ይገርመኛል፡፡ በአገራችን ሰርተን መለወጥ እንዳንችል ያደረገን ነገር ምንድን ነው? ኢትዮጵያዊነታችን አውልቀን ለመጣል ያስገደደን ምክንያቱ ከቶ ምን ይሆን? እነዚህ ጥያቄዎች ሁልጊዜም አብረውኝ የሚጓዙ ናቸው፡፡ ገንዘብ እንዳንል አንዲት እህት ከተወለደችበት ተነስታ ጣሊያን ወይም የመን ለመድረስ በአማካይ ከ20 እስከ 30 ሺህ ብር ያስፈልጋታል፡፡ ይህንን ብርም ወላጅና አሳዳጊ ከየትም ከየትም ሰብስቦ ተሰድዳ ነገ ለምታሳልፍለት ልጁ ይሰጣል፡፡ ሴትነት በራሱ ፈተና ነው፡፡ በየመንገዱ እየተደፈሩ ከጋላቫት ገዳሪፍ ካርቱም ለመግባት ብቻ ቀናትን በበርሃ መጓዝ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ከዚያ በኋላ እንደገና የሱዳን ደላሎች የመንግሥት ጥበቃ ልል በሆነባቸው የግብጽና የቻድ በርሃዎችን አቆራርጠው ወደ ሊቪያ ይገባሉ፡፡ በበርሃ አካላቶቻቸው እየተበለቱም የሚሸጡባቸው ሰዎች አሉ፡፡ ኩላሊትን የመሠለ አካል አንደኛው መገኛ ቦታው የግብጽ፣ የቻድና የሊቪያ በርሃ ነው፡፡ ከሊቪያ እንደገና ወደ ደቡባዊ ጣሊያን ለመሻገር የሜዲትራኒያን ባህርን ከሻርክ ጋር ታግለው ማለፍ ይጠበቅባቸዋል፤ ሌላም ሌላም፡፡

ታዲያ የአገሬ ዜጎች በዚህ መልኩ ከሞት ጋር ግብግብ እየገጠሙ ስለምን ይሰደዳሉ? ያልን እንደሆነ መልሱ ነጻነትን ፍለጋ ነው፡፡ ነጻነትን ያጣው ፖለቲከኛ አሊያም ጋዜጠኛ ብቻ አይመስለኝም፡፡ ይህ ቢሆንማ ኖሮ ሁላችንም ጋዜጠኛነቱን አሊያም ፖለቲከኛነቱን ትተን ነጻነታችን ባወጀን ነበር፡፡ በእኛ ምድር ሰው በነጻነት መኖር፣ መስራት አይችልም፡፡ ይህም ብዙዎቻችንን ከሞት ጋር እንድንጋፈጥ አድርጎናል፡፡ መልኣከ ሞት ፊታችን ቆሞ እያየን ኢትዮጵያ ያለው ጭቆናና ባርነት ከፊታችን ከቆመው መልኣከ ሞት የበለጠ ስለሚሆንብን አገራችን ትተን እንሰደዳለን፡፡ ከንአንን የመሰለች አገር እያለችን በባዕዳን መሸጥን መምረጥ በእውነት መረገም ነው፡፡ እርገመቱስ መቼ ይሆን የሚለቀን?

ጋላቫት ከአበሻ ሴቶች ጋር ቡና በዐሥር ብር ገዛሁ፡፡ ከላይ የገለጥኩትን የስደተኞች ጉዳይ በዝርዝር ያጫወቱኝ እነዚሁ አንስቶች ናቸው፡፡ ቡና ለመጠጣት ቁጭ ባልኩበት ሰዓት እንኳ ከዳሚዋን ልጅ ስንት ሱዳን መጥቶ እንደወደቀባት ያየሁት ምስክር ነኝ፡፡ አንደኛው ሲያልፍ ይቆነጥጣታል፤ ሌላኛው ሲመጣ ጡቷ አካባቢ ሆን ብሎ ይነካታል፤ ሌላኛው መቀመጫዋ ላይ፡፡ እርሷ ለሁሉም ትስቃለች፡፡ ለሁሉም የፈላጊነት ስሜት ታሳያለች፡፡ የእኛ እህቶች ኑሮ ይህ ነው በመተማና በጋላቫት፡፡ ወደ ቋራ መሔድ ስለነበረብኝ ሒሳብ ከፍየ ተነሳሁ፡፡ ደረቴ ላይ በጣም የሚያቃጥል ስሜት ተሰማኝ፡፡ ለካስ አንገቴ ላይ ያለው ሐብል ግሎ በእሳት የተጠበሰ ብረት ሆኗል፡፡ በእጄ አነሳሁት አቃጠለኝ፡፡ የሚገርም ነው፡፡ በአካባቢው ጸሀይ ከአናት አንድ ሜትር ከፍታ ያላት ነው የሚመስለው፡፡ ብዙ ሰዎች ራቁታቸውን መሆን ይወዳሉ፡፡ ሽፍን ጫማና ጥቁር ቲሸርት በመልበሴ እንግዳ እንደሆንኩ በቀላሉ እለያለሁ፡፡ ፀሀይ ገና በማለዳ ይህን ያክል ኃይል ካለት ከተሲያት ምን እንደምትሆን ማሰብ ይቻላል፡፡

መተማ ዮሐንስ ገባሁ፡፡ ይህ ቦታ አጼ ዮሐንስ ከድርቡሾች ጋር ሲዋጉ ሕይወታቸው ያለፈበት ነው፡፡ በኒም (በብዛት ያለ ዛፍ) ዛፎች የተሸፈነውን የመተማ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ተሳልሜ ከዛፎቹ ሥር ትንሽ ተቀመጥኩ፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት ፕሮፌሰር መስፍንን በድንበር ጉዳይ ስጠይቃቸው ‹ስለምን አንድ ቁርጠኛ ሰው ጂፒኤስ ይዞ በመሔድ ትክክለኛ ካርታው የት ላይ እንደሚያርፍ አያረጋግጠም?› የሚል መልስ ሰጥተውኝ ነበር፡፡ የእሳቸው መልስ ይህን እንድወስን ሳያደርገኝ አልቀረም፡፡ ጎግል ማፔን ከፍቼ የት ላይ እንዳለሁ ለማረጋገጥ ሙከራ አደረግኩ፡፡ ምንም እንኳ ያለኝ የካርታ እውቀት ውስን ቢሆንም ጎግል ያለሁበት ቦታ (ከረንት ሎኬሽን) ከሱዳን ድንበር ትንሽ ሜትሮችን ራቅ ብዬ እንደሆነ ነገረኝ፡፡ እርግጥ ነው ይህ ቦታ አሁንም ድሮም የአገራችን ነው፡፡ ይህ ትክክል ከሆነ የት ቦታ ላይ ሊሆን ይችላል ወደ ሱዳን የተካለለ? የሚለውን ጥያቄ መመለስ ግድ ይለኝ ነበር፡፡ የጀበና ቡና እና ጫት ደባልቀው ወደሚጠቀሙ ወጣቶች ተደባልቄ ወሬ ጀመርኩ፡፡ ጥርጣሬ በማይፈጥር መልኩ የድንበርን ጉዳይ ለማንሳት ሞከርኩ፡፡ በአጭሩ በዚያ ማኅበር የተነሳው ሐሳብ የሚያስረዳው እንደመተማ ያሉ ታዋቂ ከተሞች ወደፊትም እንደማይነኩ ነገር ግን ሰው ያልሰፈረባቸው ጥቅጥ ጫካዎች በተለያየ ጊዜ ወደ ሱዳን እየተካለሉ እንደሆነ ፍንጭ ሰጡኝ፡፡ ስለዚህ ተወደድም ተጠላም ከመተማ ወደ ሰሜንና ደቡብ የቋራና የአርማጭሆ ጫካዎች መፈተሸ ይኖርባቸዋል ማለት ነው፡፡

ቋራ ለመሔድ ወደ ሸኽዲ ከተማ ተመለስኩ፡፡ ሸኽዲ ከተማ ከመተማ 30 ኪሎ ሜትሮችን ያክል ወደ ጎንደር መስመር ትገባለች፡፡ ከተማዋ መሐል አስፓልት ላይ ቆመው የሚያድሩ ወይም የሚውሉ መኪናዎች ብዙዎቹ ነዳጅ ጫኝ ናቸው፡፡ አንድ መኪና ላይ የእሳት አደጋ ቢከሰት ያ ሁሉ ነዳጅ የተሸከመ መኪና ብቻ ሳይሆን ከተማዋም እንዳለ ልትጠፋ ትችላለች፡፡ በነገራችን ላይ ይህ የእኔ ብቻ ሳይሆን የከተማዋ ነዋሪም ስጋት እንደሆነ ለማረጋገጥ ሞክሬያለሁ፡፡ የገንዳ ውሃን እንደተሻገርን አንድ ቦቲ ተቃጥሎ የመንደሯን አብዛኛዎቹን ቤቶች እሳቱ ላፍ አድርጓቸዋል፡፡ መኪና መንገዱም በመዘጋቱ በቅያሬ ነው የሔድነው፡፡ እዚህ ላይ ሌላ የገረመኝ ነገር የኮንትሮ ባንድ ነጋዴዎች ጉዳይ ነው፡፡ ከጋላቫት በርካታ ነገሮች በእርካሽ ዋጋ ይገዛሉ፡፡ የልብስ ማጠቢያ ሳሙና (ኦሞ) በኪሎ ግራም፣ ጫማ፣ የመኝታ ልብሶች፣ ጥይትና ሌሎችም የደራ ገበያ አላቸው፡፡ መተማ ጉምሩክ ዘመድ ያላቸው ሰዎች በቀላሉ ያልፋሉ፡፡ ዘመድ የሌላቸው ደግሞ አንድም የመተማ ጉምሩክ ኬላን አሊያም የመተማ በርሃን አታለው ማለፍ ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሁለቱም ቀላል አይደሉምና ዋጋ ያስከፍላሉ፡፡ አስቀድመው በስልክ የሚሰጡትን ኮሚሽን (?) ተደራድረው ያለምንም ፍተሻ የሚያልፉት ብዙ ናቸው፡፡ ያም ሆኖ ግን ሸኽዲ ከሚገኘው የመተማ ጉምሩክ ኬላ ላይ ንብረታቸውን ተቀምተው የሚያለቅሱ ሰዎች አይታጡም፡፡ ጉምሩክ ሠራተኞቹ አንዳንድ ጊዜ ከኮንትሮ ባንድ ነጋዴዎች ላይ ግማሹን ወስደው መካዝን ሳያስገቡ ያስቀምጡታል፡፡ ያ የግላቸው መሆኑ ነው፡፡ ወደ መካዘን ለምን አይገባምና ደረሰኝ አልትሰጠኝም ብሎ የሚከራከር ንብረቱ የተወሰደበት ግለሰብ ሙሉን ሊቀማ ይችላል፡፡ የሚፈትሸው ሰው እንደሚወስደው እያወቁ ሁሉንም ከማስዘረፍ ብለው ብዙዎች ይተዋሉ፡፡ አንዳንዶች ብልጥ ነጋዴዎች ደግሞ መኪና ውስጥ ላለው ሰው ያከፋፍሉና የእኔ ነው በሉ ይላሉ፡፡ ይህም አንድ ሰው አንድ ዓይነት እቃ በቁጥር ይዞ መንቀሳቀስ ስለሚችል ከመዘረፍ ይድናሉ፡፡

ጥይት ወደ ጎንደር የሚገባበት መንገድ አስገርሞኛል፡፡ የጠርሙሱ ስፕራይት ለስላሳ (ሱዳኖች እስቲም ይሉታል) ቀለሙ አረንጓዴ ነው፡፡ ስቲሙን የተወሰነ በመጠጣት አሊያም በመድፋት ካጎደሉት በኋላ ብዙ ጥይት ወደ ላስቲኩ ይጨመራል፡፡ ከዚያም ጥይት የሚነግደው ግለሰብ እስቲሙን የሚጠጣ በመምሰል ወደ አፉ እያስጠጋ ጥይቶቹን ከጉምሩክ በቀላሉ ያሳልፋል፡፡ እርግጥ ይህ ዘዴ አሁን ተነቅቶበታል፡፡ በዚህ ሁሉ ዘዴ ማሳለፍ የማይችል ከሆነ ግን ከ30 ኪሎ ሜትር በላይ በጫካ ከበርሃና ከአራዊት ጋር ታግሎ ሸኸዲን ማለፍ ይጠበቅበታል፡፡ ሌላም አማራጭ አለ፡፡ ከሸኽዲ መሀል ከተማ ላይ ወደ ቋራ በመታጠፍ ቢሻው በቆላ ድባ አሊያም በአቸፈር አድርጎ ማምለጥ ይችላል፡፡ በቋራ በኩል ፍተሻው ጥብቅ አይደለም፡፡ ሸኽዲ ከተማ መካከል ላይ መውረድ ቢኖርብኝም ረስቼ የጉምሩክ ኬላ ላይ ስደርስ ከተማውን ማለፌን አረጋገጥኩ፡፡ በዚህ ከመጠን በላይ በሚሞቅ ጸሀይ እንደገና እየተቃጠልኩ ወደ ኋላ ተመለስኩ፡፡ የሚገርመው ከፍተኛ ንፋስ አለ፤ ነገር ግን ንፋሱ በራሱ ፊት ይጠብሳል፡፡ ንፋስ ብርድ ሲሆን እንጅ ሲያቃጥል ያየሁት መተማ ነው፡፡ ሙቀቱ ገና በረፋድ እንዲህ ከሆነ እኩለ ቀን ላይ ምን እንደሚሆን መገመት ይቻላል፡፡

ከሸኽዲ ወደ ገለጎ ቋራ ለመሔድ መኪና ማፈላለግ ያዝኩ፡፡ የቋራና የሽንፋ ሰው በጭነት አይሱዚ እላይ ተጭኖ መሔድን ይመርጣል፡፡ ለምን እንደሆነ ስጠይቅ የመኪናው ውስጥ ሙቀት ከመጠን ያለፈ ስለሆነ ከጭነቱ እላይ መሆን የተሻለ እንደሆነ ለእኔ ለእንግዳው ነገሩኝ፡፡ እድለኛ ነኝ መሰል ወደ ቋራ ሒዳ እንደገና የምትመለስ ፒካ አገኘሁና በእርሷ ወደ ቋራ መንገድ ጀመርኩ፡፡ ሽንፋ ደርስን፡፡ ሽንፋ ከአንድ ወር በፊት ወደ አምስት ሺህ የሚጠጉ በእርስ በእርስ ግጭት የተጎዱ ተፈናቃዮች ሰፍረውበት ነበር፡፡ እዚህ አካባቢ ያለው ሙቀት መተማ ካለውም ያይላል፡፡ ንፋሱም አይንቀሳቀስም፡፡ በነገራችን ላይ መተማና ሽንፋ አካባቢ አንዳንድ ጊዜ ሰዎች በተኙበት ሊያሸልቡ ስለሚችሉ ሌሊት ላይ የአየር ሁኔታውን አይተው የፖሊስ አምቡላንስ መኪና ከእንቅልፍ ይቀሰቅሳሉ ብለውኛል፡፡ አሁን የምሔድበት አካባቢ ጫካ ብቻ ነው፡፡ የቋራ ወረዳ ኹለት ሦስተኛው የአልጣሽ ብሔራዊ ፓርክ ሲሆን ጥቅጥቅ ጫካ ብቻ ነው፡፡ ፓርኩ እኛ ከምንሔድበት መንገድ ወደ ቀኝ ገባ ብሎ ነው፡፡ ከሰሞኑ የዓለማችን ሳይንቲስቶች ከኹለት መቶ በላይ አናብስቶችን በሳትላይት አይተናል ያሉት ከዚህ ነው፡፡ ፓርኩ በሱዳን ድንበር የተዋሰነ ነው፡፡

ገለጎ (ቋራ) ስንደርስ ዘጠኝ ሰዓት አልፎ ነበር፡፡ እንደማንኛውም የሙቀት አካባቢ ከተሞች ሰዎች ሁሉ በረንዳ ላይ ከገመድ በተሰራ ወንበር ወይም አልጋ ላይ ተቀምጠው ይመገባሉ፤ ይጠጣሉ፡፡ ምንም እንኳ የወረዳው ከተማ ብገኝም የሱዳን ድንበር ካለሁበት በጣም የሚርቅ ብቻም ሳይሆን መንገዱ የራሱን መኪና ላልያዘ ሰው የሚመች አይደለም፡፡ ስለሆነም ድንበሩን በተመከተ የማቀርበው ያየሁትን ሳይሆን በቅርብ የሰማሁትን ብሎም የተቻለኝን ያክል ለማረጋገጥ የሞከርኩትን ያክል እንደሆነ አንባቢ እንዲረዳ እሻለሁ፡፡ ቋራ ላይ የሰማሁት በኋላም ሸኽዲ ያሉ የመንግሥት ሠራተኞች ያረጋገጡልኝ ነገር ቢኖር የሱዳን ወታደር ሽንፋ ወንዝ ተሻግሮ የኢትዮጵያ ድንበር ውስጥ መስፈሩን ነው (ሽንፋ ወንዝ የመተማና የቋራ ወረዳዎችን እያካለለ ከሔደ በኋላ እንደገና ለሱዳንና ለኢትዮጵያ ድንበር ይሆናል፡፡ የኢትዮጵያ ድንበር ሆኖ የአላጣሽ ፓርክን እየከለለ በመጨረሻም በበርሃ ሰርጎ ይቀራል እንጅ ከአባይ አይጨመርም አሊያም ሌላ ገባር የለውም፡፡ መተማና ቋራ ድንበር ያለችው ከተማ በወንዙ ስም ሽንፋ ትባላለች)፡፡ የሰፈሩበት አካባቢ ‹ሰልፈረዲ› ቀበሌ ቁጥር 3 በተባለ በርሃ ቦታ ነው፡፡ ቀድም ባሉት ጊዜያት የሱዳን ወታደሮች ቁጥር አምስት በተባለው ‹አንቶቭ ኮረብታ› ካምፕ ነበራቸው፡፡ ይህ ቦታ በአማርኛ ቁጥር 5 ተብሎ እየተጠራ የሱዳን ግዛት እንደሆነ ብዙም ግልጽ አይደለም፡፡ በዚህ አካባቢ ያሉ የሠፈራ ጣቢያዎች በቁጥር ይጠራሉ፡፡ አስቀድሞም የሱዳን ግዛት ከሆነ ቁጥር 5 ተብሎ መጠራት ላያስፈልገው ይችል ነበር፡፡ ከባዱ ነገር ከዚህ አካባቢ ሁሉም በኃይል እንጅ በሕግ የሚተዳደር ስለሌለ ቁጥር 5 ብቻም ሳይሆን የኢትዮጵያ እንደሆነች የምትታወቀው ቁጥር 3 በበርካታ ግጭቶችና የቋያ ቃጠሎ ምክንያት ሰው አልባ ናት፡፡ በዚህ ከብት የሚያረቡ ዘላኖች ብቻ ይኖራሉ፡፡ ሆኖም ግን በቅርብ ጊዜ ወዲህ ነው የሱዳን ወታደር ወደዚህች ቀበሌ የመጣው፡፡ በነገራችን ላይ የሰልፈረዲ ቀበሌ ስፋቱ ራሱን የቻለ አንድ ወረዳ ቢያንስ እንኳ ንዑስ ወረዳ ይሆናል፡፡ መተማ ወረዳን የተወካዮች ምክር ቤት ቋሚ ኮሚቴ ለጉብኝት በሔደ ጊዜ የመተማና የቋራ ሕዝብ ተወካዮች ‹‹እነዚህ የሱዳን ወታደሮች ስለምን እኛ ድንበር ውስጥ ካምፕ ሠርተው መኖር ተፈቀደላቸው?›› የሚል ጥያቄ አንስተው ነበር፡፡ የተወካዮች ምክር ቤት የመጡት ኮሚቴዎች በትክክል መልስ አልሰጡም፡፡ በገደምዳሜ ‹‹በአካባቢው ያሉ ጸረ ሰላም ኃይሎችን በጋራ ለመከላከል በእኛ ጥሪ ነው የመጡት ሆኖም የክልሉ መንግሥት እንዲወጡ እየተነጋገረ ነው›› በማለት መልሰዋል፡፡ በአካባቢው ያለን ጸረ ሰላም ኃይል ለመከላከል በሚል እኛ ድንበር ላይ የሱዳን ወታደሮች በቋራ መስፈራቸው የአካባቢው ማኅበረሰብ ላይ ቅሬታ ፈጥሯል፡፡ የሚገርመው ነገር አንድ መንግሥት ስለ አገሩ ዳር ድንበር ዴንታ በሌለበት በዚህ ጊዜ እነዚህ ነዋሪዎች ግን የሱዳን ወታደር ተሻግሮ መጥቶ ቢራ ጠጥቶ ከመሔድ በዘለለ ካምፕ መሥራታቸው የእግር እሳት ሆኖባቸዋል፡፡ ማኅበረሰቡ የሽንፋ ወንዝ እስኪሞላ ድረስ በተጠንቀቅ እየጠበቁ ነው፡፡ እንደሰማሁት ከሆነ የሱዳን ወታደር የእኛ አገር ገበሬዎች በተኩስ ከገጠሙት እየዘለለ ወደ ውኃ በመግባት በወንዝ የመወሰድ እድል ብቻ ይኖረዋል፡፡ ቆሞ እንኳ ገበሬዎችን ለመከላከል አቅም እንደሌለው ነው ያወሩኝ፡፡ ነገሩን ጠቅለል ስናደርገው በዚህ አካባቢ የሱዳን ወታደሮች እኛ ክልል ውስጥ ሰፍረዋል፡፡ የሰፈሩበት ቦታ የተሰጣቸው ይሁን አሊያም እንደተባለው ለጊዜያዊነት ብቻ ማንም አያውቅም፡፡ ነገር ግን ቁጥር 5 የተባለው አካባቢ በትክክል በሱዳን የሚተዳደር ቦታ ነው፡፡ ቀድሞ የማን ቦታ ነበር ለሚለው ጥያቄ እኔ መልስ መስጠት አልችልም፡፡

የሚቀጥል…

ለሱዳን ሊሰጥ ነው ስለተባለው መሬት : ጆሮ ያለው ይስማ ልብ የአለው ልብ ይበል!

By historian   Fikre Tolossa

ለሱዳን ሊሰጥ ነው ስለተባለው መሬት
—————————————————-

eprdf berber

አሁን በጎንደር አና በቤንሻንጉል አካባቢ የሜገኙት የእነ ኦሜድላና ጋምቤላ መሬቶች በአውነት የማን ናቸው? ያለጥርጥር የኢትዮጵያ ናቸው። ለምን እንደዚህ እንዳልኩ ዝቅ ብዬ አስረዳለሁ። መሬቶቹ በታሪክ የሱዳን ነበሩና ለሱዳን ይሰጡ የሚሉት የኢትዮጵያ ባለስልጣናት መሬቶቹን ለሱዳን ለመስጠት የሚያቀርቡት ምክንያት “በ በሱዳን የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ጊዜ የእንግሊዝ መንግሥት ተወካይ የሆነ አንድ ሻለቃ የወሰን ምልክቱን የተከለው እዛ አካባቢ ነው፤ቀድሞ አፄ ምንይልክ በዚህ ተስማምተው፥ በሁዋላ ደግሞ አፄ ኅይለሥላሴ እና ደርግም ይህን አፅድቀውታል፤” የሚል ነው። በሌላ አነጋገር፥ በታሪካዊ ምክንያት ነው። እዚህ ላይ አንድ አስቂኝ ታሪክ ታወሰኝ። አንድ እንግሊዛዊ ከሱዳን የኢትዮጵያን ድንበር ተሻግሮ የዱር እንስሳና አውሬ ለማደን በሚል ፈሊጥ ሲዘዋወር ለስለላ ነው ብለው በጠረጠሩት የሃገሬው ተወላጆች ተገሎ እዛው ተቀበረ። ታዲያ ይህን ሰበብ አድርጎ አንድ እንግሊዛዊ መኮንን (ምናልባትም እላይ የተጠቀስው እብድ ሻለቃ) ያ አካባቢ በሞላ ለእንግሊዝ መንግሥት ሊሰጥ ይገባል፤አለ። በምን ሂሳብ ተብሎ በአባ መላ (ፊታውራሪሃብተጊዮርጊስ ዲነግዴ) ተጠየቀ። አንድ የእንግሊዝ ዜጋ ሞቶ እዚህ ስለተቀበረ፤ሲል መለሰ። አባ መላም ከትከት ብለው ስቀው፥እሺ ደግ ነው፤አንድ የእንግሊዝ ዜጋ ሞቶ እዚህ ስለተቀበረ ይሄን ሁሉ መሬት ለናንተ እንሰጣችሁአለን። የአፄ ቴዎድሮስ ልጅ ልዑል ዓለማየሁ ለንደን ውስጥ ሞቶ እዛው ለንደን (ዌስትሚኒስትር አቢ) ስለተቀበረ እኛ ደግሞ ለንደንን እንረከባችሁአለን። በዚህ ከተስማማህ ውል መፈራረም እንችላለን፤ብለው አሾፉበት። ከዛ ቦታ በቅፅበት ዳብዛው ጠፋ። ስለታሪክ ካወሳን ዘንድ፥ ይሄ ዛሬ ሱዳን የተባለው ምድር ሁሉ ቢያንስ ለ 4000 ዓመታት ያህል የኢትዮጵያ ግዛት ነበር።ጥንት የሚታወቀው ኑብያ ተብሎ ነበር። ኖባ በተሰኘው የኩሽ ዘር ስም።መናገሻውም መርዌ ነበር። የዛሬ 2900 ዓመት ግን ሱዳን ይባል ጀመር። ይህ ስም የወረደው ከአፄ አክሱማይት እናት ከንግሥት ሳዶንያ ነው። እሱ በህፃንነቱ የግብፅ ፈርኦን ሆኖ እስከሚያድግ ድረስ እስዋ በ 350,000 የአማራ ሰራዊት ታጅባ ዙፋኑን እየጠበቀች በሱ ስም ግብፅን፥ ሊብያን እና የዛሬውን ሱዳን ታስተዳድር ነበር። በዚህ ምክንያት፥ ከሳሃራ በርሃ በታች የአለው ምድር በሞላ ሳዶንያ ተባለ። ቀስ በቀስ ደግሞ ሱዳን። እንዳውም ኑብያ ውስጥ የነበረው መርዌ ለዛ አካባቢ እንደ ዋና ከተማ ሆኖ ያገለግል ነበር። ቢያንስ 14 የኢትዮጵያ ሴቶች ህንደኬ በሚል ማእረግ በንግሥትነት በተከታታይ ዛሬ ሱዳን፤ ግብፅና ሊብያ የሚባሉትን ሃገሮች ለ 1000 ዐመት ያህል ገዝተዋል። ለመጨረሻ ጊዜ የኑብያ ንጉሥ የነበሩት በ 16ኛው ክፍለ ዘመን የኖሩት አፄ ፋሲል ነበሩ። ከኑብያ ብቻ ሳይሆን ከስናር (ከካርቱምብዙያልራቀ ስፍራ) ድረስ የወርቅ ግብር ይመጣላቸው ስለነበር አዝማሪ አንዲህ ሲል የሱዳን ገዥነታቸውን አረጋግጦላቸው ነበር፤-

ጎንደር ቢያጉረመርም ፋሲል ፈረስህ ኑብያና ስናር ወርቁን ጫኑልህ፥ሳሩን ተጠየፈ የፋሲል ፈረሱ፥ ክምር የሱዳን ወርቅ ገፈራው ነው ለሱ።

“ገፈራ” ማለት የፈረስ ምግብ ነው። ዛሬ ፉርሽካ የምንለው ዐይነት። እንግዲህ ይህ ግጥም፥ ሱዳን አስከ የዛሬ 500 ዐመት የኢትዮጵያ ግዛት አንደነበረች ይመሰክራል። በሁዋላ በዘመነ መሳፍንት አና ከዛ ትንሽ ቀደም ብሎ ኢትዮጵያ አየተዳከመች ስትሄድ ቱርኮች ያዝዋት። ቱርኮች ተዳክመው ለእንግሊዝ ለቀቁላት። እንግዲህ ከእጅ የወጣ ሃገር በታሪክ ሰነድ ወይም ማረጋገጫ የሚመለስ ቢሆን ኖሮ፥ መላው ሱዳን ለኢትዮጵያ በተመለሰ ነበረ። ከላይ አንደ ተረዳነው ሱዳን የኢትዮጵያ እንጂ ኢትዮጵያ የሱዳን ሆና አታውቅም። ታዲያ በምን ምክንያት ነው አሁን የኢትዮጵያን መሬት የጠየቀችው? እስዋ አፍዋን ምን ቁርጥ አርጉዋት ጠየቀችና? እስዋ በራስዋ ተነሳስታ ደፍራ መሬት አለኝ አላለችም።

አሁን በአመራር ላይ የአሉት የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ደርግን በሚዋጉበት ሰዐት ሱዳን ለዋለችላቸው ውለታ ወሮታውን ሊመልሱላትና አሁንም ተቀዋሚዎቻቸውን እንዳታስተናግድ የሚከፍሉዋት ዋጋ መሆኑ ነው። ወዲህም መሬቱ ያለው በአማራ፥በቤንሻንጉል፥ በጋምቤላና በአሮሞ ክልሎች ስለሆነ የእኛን ምድር ስለማይመለከት ችግር የለውም ዐይነት ነው። ብሄራዊ ስሜት የሚባል ነገር ስለሌለ። መሬት በነፃ እንካ ከተባለ ማን ይጠላል? ስለዚህ ሱዳኖቹ እየፈነጠዙ ሊወስዱ አኮብኩበዋል።አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው መንግሥት 1600 ኪሎሜትር ለም መሬት ለሱዳን ይገባታል ብሎ ጠበቃ የቆመላት እላይ የተጠቀሰው ቅኝ-ገዢ መኮንን በቸከለው ድንበራዊ ችካል ክሆነና በእንግሊዝ ቅኝ ገዥነት አገር ቅርጫ አንዲሆን ከተፈቀደ፥ እንዲሁም እንግሊዝ ያቀናው መሬት ሁሉ ለሱዳን ይቸር ዘንድ ከተፈረደ፥ የቀድሞው የአንግሊዝ ቅኝ ግዛቶች የነበሩት እነ ዩጋንዳና ሱዳን፥ ካስፈለገም እነ ናይጀሪያ ሁሉ ለሱዳን መሰጠት ይገባቸዋል ማለት ነዋ!!! የሆነ ሆኖ፥ ያ ሆፈፌ ቅዥተኛ እንግሊዝ ምኞታዊ ህልም አልሞ የፈለገውን ያህል የወሰን ድንጋይ ቢተክልና አፄ ምኒልክም አልተስማሙም እንጂ ቢስማሙለትና መሬት ቆርሰው ቢሸልሙትም አንኩዋን ያ ውል የሞተ ነው። ለምን ቢባል፥ ሱዳንን ዐለምና የተባበሩት መንግሥታትም ያወቃትና በታሪኩዋ ለመጀመሪያ ጊዜ ራስዋን ችላ የራስዋን ባንዲራ ያውለበለብችበት ዳር ድንበር አሁን የአለው ነውና። እኤአ በ 1953 ዐመተ ምህረት እንግሊዝ ግዛቴ ይሄ ብቻ ነውና ያንቺም ግዛትሽ ይሄው ነው ብሎ በዐስር ጣቱ ፈርሞ የተወላት መሬት ነው። እሱውም ከመከፈልዋ በፊት የነበረው የቆዳ ስፋቱ 2,505,813 ስኩዌር ኪሎሜትር የሆነው ነው። ከመከፈልዋ በፊት ሱዳን በቆዳ ስፋት ከአፍሪካ አንደኛ ነበረች። አሁን ሶስተኛ ነች። አሁንም ከኢትዮጵያ ትልቃለች ማለት ነው። የያዘችው ይበቃት ነበር። የኢትዮጵያን መሬት ለግሰናት በደቡብ ሱዳን የተወሰደባትን መሬት እንተካላት ካልተባለ በቀር። ሰጭና ነሽው አንግሊዝ ከተደረገና የእንግሊዝ መንግሥት ለክቶ፥ “አበጥሮ”፤ “አንጥሮ” ሁሉን አጣርቶ ራሱ በመጨረሻ ያረጋገጠው የሱዳን ምድር እላይ የተጠቀሰው ስፋት ከሆነ በምን ሂሳብ ነው አንግሊዝም ሆነ የተባበሩት መንግሥታት የማያውቁትን የኢትዮጵያን መሬት በ ህቡዕ ለሱዳን የሚለገሳት? አይገባትም አንጂ በእርግጥ ሱዳን ይገባኛል የምትለው መሬት ከአላት ወደ ተባበሩት መንግሥታት ሄዳ ነው አንጂ አቤቱታዋን የምታቀርበው በስርቆሽ በር ነው እንዴ መሬት ቆርሳ የምትሮጠው? ወይንስ መሬቱን ከቦጨቀች በሁዋላ ወደ ተባበሩት መንግሥታት ቀርባ መርቁልኝ ልትል ይሆን? እስዋ ግን ወደ እዛ እስካሁን ያልሄደችው እኤአ በ 1953 እንግሊዝ ካስረከባት በቀር ሌላ መሬት ስለማይገባት “ወይጅ ወዲያ አትቀልጅ!” ይሉኛል፤ ብላ ፈርታ ነው። አለዛ ሱዳን ነፃ ከወጣች ጀምሮ መሪዎችዋ ከ ኢብራሂም አቡድ ጀምሮ እስከነ ኑሜሪ አና አሁን ያለውም አል በሺር የይገባኛሉን ጥያቄ ገና ድሮ ባቀረቡ ነበር። ሰብብ ፈጥረን ስለቀድሞ ውለታዋ እና ተቀዋሚዎቻችንን ስለምትገታልን እንዲሁ በነፃ እንቸራት ካልተባለ በቀር እንደ እውነቱ ከሆነስ ሱዳን፥ “ኢትዮጵያ ያዘችብኝ፥ ይገባኛል፤” የምትለው አንዲት ስንዝር መሬት የላትም። ከቅኝ ግዛት ነፃ ከወጡ በሁዋላ የአፍሪካ ሀገራት በሞላ የያዙት ድንበርና ወሰን የቅኝ ገዥዎችቸው አነዚህ ናቸው፤ ብለው ያረጋገጡላቸውን ብቻ ናቸው። ስለዚህ ሱዳን ከሌሎቹ የአፍሪካ ሃገራት በምንም አትለይም። በመሆኑም ከኢትዮጵያ ልቀበል ይገባኛል ልትል የሚያስችላት ኢትዮጵያ ውስጥ አንድ ጥሪኝ አፈር የላትም። ስለ ኦሜድላ ብቻ እንኩዋን ብንዘክር፥ አፄ ኅይለሥላሴ በሱዳን በኩል ከስደታቸው ሲመለሱ ከ 5 ዐመታት በሁዋላ ለመጀመሪይ ጊዜ የኢትዮጵያን ሰንደቅአላማ ሰቅለው የአውለበለቡት ኦሜድላ ላይ ነበር። ይህን በሚያደርጉበት ጊዜም የ እንግሊዝ የቅኝ ገዢ ትልቅ ባለስልጣናት ለ ሰንደቅአላማዋ አክብሮት በተጠንቀቅ ቆመው መሬቱ የኢትዮጵያ መሆኑን ተቀብለው ይመለከት ነበር እንጂ “የሱዳን መሬት ላይ እንዴት ባንዲራ ያውለበልባሉ!” ሲል በንጉሱ ላይ ቅዋሜ አላሰሙም።

ኦሜድላ የኢትዮጵያ ለመሆንዋ ከዚህ በላይ ምን ማረጋገጫ አለ? ታዲያ በምን ምክንያት ነው አሁን ይቺ ታሪካዊ ስፍራ ለሱዳን የምትሸለመው? ቀዳማዊ ኅይለሥላሤ ኦሜድላ ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅአላማ ሲያውለበልቡ ጦሩን እንዲያቀነባብር በእንግሊዝ መንግሥት ተሹሞ አብሮአቸው በሱዳን በኩል የገባው ሜጄር ዊንጌትም ታዛቢ ሆኖ እጎናቸው ነበረ። ንጉሡን ተሽቀዳድሞ አዲስ አበባ የገባው ሎርድ ካኒንግሃምም እሳቸው ኦሜድላ ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅአላማ እንዳውለበልቡ አሳምሮ ያውቅ ነበር። እነዚህም ሁለት ታላላቅ የእንግሊዝ መንግሥት ተወካዮች ኦሜድላ የኛ ናት አላሉም። የሆነ ሆኖ እውነት እንግሊዝ ከ አፄ ምንይልክ ጋር ተዋውሎ ከነበር እሱው እንግሊዝ የመሬት ይገባኛል ጥያቄውን ያቅርብልን እንጂ ያልተዋዋልናት ሱዳን ምን አገባት? ከሱዳን ሳንዋዋል እንዴት ሱዳን የተዋዋልነው ይከበርልኝ፥ ልትል ትደፍራለች? ይህን ጥያቄ ሊያነሳ የሚችል አንግሊዝ ብቻ ነው። ነበርም። ግን እንግሊዞች አላነሱም። ምክንያቱም ቀላል ነው። የዚህ ዐይነት ውል ከአፄ ምንይልክ ጋር ስላተፈራረሙ። ተፈራርመው ቢሆን ኖሮ መጠየቅ ብቻ አይደለም፥የተፈራረሙበት ቀለም ሳይደርቅ መሬቱን እጃቸው ያስገቡ ነበር። ስላልተፈራረሙ ይህን አላደረጉም። የሱዳንን ነፃነት እንግሊዞች ሲፈቅዱም የተባለውን መሬት የኔ ነበር ብለው ወደ ሱዳን አላዘዋወሩም። አሁን ያለውን መሬት ብቻ ነው ትተውላቸው የሄዱት።አሱም ለሁለት ተከፍሎባቸዋል። ከአንግሊዝ የተረከቡትን መሬት እንኩውዋን በቅጡ መያዝ አቅቶአቸው “የቆጡን አወርድ ብላ የብብትዋን ጣለች፤” የተባለው ተረት በነሱ ላይ ተፈፅሞባቸዋል። የራሳችውን አጥብቀው መያዝ ሳይችሉ የኛን መሬት መከጀላቸው ማስቆጣት ብቻ ሳይሆን ያስደንቃል። እንግዲህ እንግሊዝ ከአፄ ምንይልክ ጋራ መሬትን አስመልክቶ ላለመዋዋሉ ሶስት ማስረጃዎች አሉ ማለት ነው። አንደኛ፥ የተባሉትን መሬቶች ቀደም ሲል እጁ ባለመክተቱ፤ ሁለተኛ፥ ንጎሱ ኦሜድላ ላይ ሰንደቅአላማችንን ሲሰቅሉ አለመቃወሙ፥ ሶስተኛ፥ ሱዳንን ለቆ ሲሄድ ለሱዳን ከተወላት የተባበሩት መንግሥታይ ባፀደቀላት ዳር ድንበር ውስጥ እነዚህን ሁሉ የኢትዮጵያ መሬቶች በካርታም ሆነ በፅሁፍ ባለማካተቱ። በነዚህ ሶስት ማስረጃውች ምክንያት እሩቅ ሳንሄድ፥ ሰነድ ለማግኘት አፈር ሳንቆፍር እና ድንጋይ ሳንፈነቅል ምንይልክ እና እንግሊዝ አንዳችም የመሬት ውል እንዳልተፈራረሙ እናረጋግጣለን። ተፈራርመዋል የሚል እስቲ ሰነዱን ያቅርብልን!!! ደግሞም ቢፈራረሙም እንኩዋን ውሉ የቅኝ ገዥዎች ሰለሆነና ምንይልክም ሆነ ማንኛውም መሪ የአትዮጵያ መሬት የግል ንበረቱ ስላልሆነ መሬት ለባእዳን ሰጥቻለሁ ቢል አይፀናም።አፄ ምንይልክ ተስማምተውበት፥ አፄ ኅይለሥላሴ እና ደርግ ያፀደቀውን ነው እኛ በ ተግባር የምናውለው፤ ሲል ኢህአዲግ ደጋግሞ ተናግሮአል።

ይህን መሰረት በማድረግ እኔ ብዙ ምርምር አካሂጄ ሁለቱ አፄዎችና የደርግ ሊቀመንበር የነበሩት ኮረኔል መንግሥቱ ኅይለማርያም ለሱዳን መሬት ለመስጠት የተዋዋሉበት አንድም ሰነድ አላገኘሁም።ምክንያቱም ስላልነበረ። ስለ ሌለም። አሁን በህይወት የአሉት ኮሎኔል መንግሥቱም አንድም የዚህ ዐይነት ውል ከሱዳን ጋር እንዳልተፈራረሙ አበከረው መስክረዋል። ይልቁንም አኔ ያገኘሁት መረጃ፥ አውሮፓውያን መንግሥታት ለብቻቸው ተሰብስበው አፍሪካን ለመቀራመት ያደረጉትን ውል ለአፄ ምንይልክ ነግረው የኢትዮጵያን ነፃነት ግን አንደሚያስጠብቁ ቢገልፁላቸው፥ “እኔ በሌለሁበት እናንተ ተሰብስባችሁ ያደረጋችሁትን ውል በፍፁም አልቀበልም፤ የኢትዮጵያን ነፃነት አናስጠብቃለን ሰለአላችሁት ግን አመሰግናለሁ፤” በማለት ተንኮላቸውን ውድቅ ማድረጋቸውን የሚያሳይ ነው። በነገራችን ላይ፤ አፄ ምንይልክ እንኩዋን ለሱዳን መሬት ሊሰጡና በሰላም ኢትዮጵያ ውስጥ ይኖሩ የነበሩት የውጭ ሀገር ሰዎች መሬት አንዲገዙ አይፈቅዱላቸውም ነበር። አላደረጉትም እንጂ ሶስቱም መሪዎች አድርገውትም እንኩዋን ቢሆን፤የኢትዮጵያን ህዝብ መሬት አንስተው ለባእዳን ለመቸር ምንም መብት አልነበራቸው። ኢትዮጵያ፥ እንዲያስተዳድሩዋት አደራ የተሰጠቻቸው ምድር እንጂ እንዳሻቸው ለፈለጋቸው አገር ገፅበረከት አድርገው የሚለግስዋት የግል ንብረታችው አልነበረችምና። አሁን ያለውም መንግሥት አንዲሁ የኢትዮጵያን መሬት ገምሶ ለባእዳን ለመቸር ከቶም አንድም ህገመንግሥስታዊ ነፃነት ወይም ስልጣን የለውም። በጉልበቱ ካልሆነ በቀር። ረጅሙን ታሪካችንን ወደ ሁዋላ መለስ ብለን ብናስተውል፥ ባለፉት 5300 ዐመታት ኢትዮጵያን የመሩት መንግሥታት ድንበር ከማስፋት በቀር መሬታቸውን እንደ አንጀራ ቆርሰው ለባእዳን ሲቸሩ በፍፁም ተስተውሎ አያውቅም። አሁን ከአለው መንግሥት በስተቀር።እዚህ ላይ ባድመ ይታወሰናል። ባድመ ባድማው ደረቁ መሬት ከአትዮጵያና ኤርትራ በኩል ወደ 150000 ገደማ ወይም ከዛ በላይ ምስኪን ሰዎች በከንቱ አስጨረሰ። ከዚያ አልጀርስ ላይ ለኤርትራ ይገባታል ይሰጣት፤ ተብሎ ተፈረደላት።ባድመ እስካሁን በ ኤርትራ እጅ ውስጥ አልገባችም። ለምን? የትግራይ መሬት ውስጥ ስለሆነች የማትነካ፥ የማትገሰስና የተቀደስች ሆና ወይስ በሌላ ምክንያት? ሰፊ መሬት አለኝ ብሎ ከማውራት በቀር ለማንም የማይጠቅመውን ጠፍ መሬት አንሰጥም ብሎ ይዞ፥ ለመሬት ብላ ከኛ ላልተዋጋችው ሱዳን ለምለም ምድር ገምጦ ለመቸር መቸኮል ምን ይባላል? ይህ ለሰሚው ግራ ነው። ባድመም በኤርትራ ላትወስድ የቻለችው፥ “ትግራይ ሀገርህ ተወራለችና የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ! ተነሳ!” ተብሎ በተጠራው የሀገር ማዳን ጥሪ መሰረት፥ “ጉዳዩ እኔን አይመለከተኝም ይህ የትገራይ መሬት ነው፤” ሳይል በብሄራዊ ስሜት የነደደው ቆራጡ የኢትዮጵያ ህዝብ አጥንቱን ከስከሶ፤ ደሙን አፍሶ፤ንብረቱን አጉድሎ ባደረገው ተጋድሎ ነው። ትግራይ ስትወረር የኢትዮጵያ ህዝብ ፥ “ወይኔ ሃገሬ!” ብሎ ደሙን ሲያፈስ ባድመ የመጨረሻው እንጂ የመጀመሪያው አይደለም። ከዛ በፊት ጣልያን ከማንም አስቀድሞ ትግራይን በወረራት ጊዜ በመቀሌ፥ በአምባላጌ፥በአድዋ እና በማይጨው በ 40 ዐመታት ልዩነት ውስጥ ሁለቴ ከፍተኛ መስዋእትነት ከፍሎአል። ለዚህ ሁሉ ውለታው አፃፋው ይሄ ነውን? እባካችሁ ሰከን ብላችሁ ነገሩን አስቡበት። ይህ ድርጊት በትውልድ ያስወቅሳችሁአል። ጠንቁ ለልጆቻችሁና ለልጅ ልጆቻችሁ፤ እንዲሁም ለዘራችሁ ይተርፋል። ለስልጣን ያበቃችሁ የትግራይ ህዝብ ሳያቀር በአደራጎታችሁ ያፍርባችሁአል። የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬ አቅም ባይኖረው ነገ ሊጠነክር ይችላል። ሳይወድና ሳይፈቅድ መሬቱን ሱዳን አሁን ብትወስድበት እንኩዋን ነገ ሲጠነክር ተዋግቶ ያስመልሰዋል። በዚህ ሳቢያ አሁን ልትጠቅምዋት ያሰባችሁአት ሱዳንም ሰላም አታገኝም። የ እናንተም ስም በክፉ ተነስቶ አፅማችሁም ሲወቀስ ይኖራል። ስለዚህ ሱዳንን በሌላ በሌላ ነገር ካስዋት እንጂ የስንት ሰማአታት ወገኖቻችን ደም እና ላብ የአለማውን መሬታችንን አሳልፋችሁ በብላሽ አትስጡ። ለሱዳን ካሳ፥ አፍንጫዋ ስር የተገነባላት የአባይ ግድብ መች አነሳት? በዚህ የኢትዮጵያ ህዝብ ገንዘቡን በከሰከሰበት ግድብ ከማንም በላይ ተጠቃሚዋ ሱዳን አይደለችንምን? ግድቡ ይበቃታል፤ መሬቱ ይቅርባት። ብቻችሁን ይህን መወሰን ካስቸገራችሁ ደግሞ ፓርላማችሁና የኢትዮጵያ ህዝብ ይምከርበት። ለይስሙላስ ቢሆን ፓርላማ አለ አይደል? እንዲህ ዐይነቱ ትልቅ የሀገር ሉአላዊነት ጉዳይ ሀገር ሳይመክርበትና ህዝብ ሳይወስንበት አንዴት በዝግ ጉዋዳ ይካሄዳል? ባድመ አንዳትወሰድ የተረባረባችሁትን ያህል አና ለኤርትራ አንዳይሰጥ የምትተጉትን ያህል፥ እባካችሁ አሁን ሱዳንን የሚያዋስናትን ሁሉ የኢትዮጵያ ዳር ድንበር ለሱዳን ከመቸር ታቀቡ። በውኑ ከዚህ ከታቀባችሁ፥እናንተም፤ ልጆቻችሁም፥ ዘራችሁም፥ አንዲሁም በመቃብር ውስጥ የሚኖረው አፅማችሁም ከመወቀስና ከመረገም ይተርፋል። ጆሮ ያለው ይስማ። ልብ የአለው ልብ ይበል።l

ዳር ድንበራቸው ለሱዳን ሊሰጥ መዘጋጀቱን የተቃወሙ ኢትዮጵያውያን በዋሽንግተን ዲሲ ሰላማዊ ሰልፍ አደረጉ

(ዘ-ሐበሻ) 1200 ኪሎ ሜትር የሚገመትን የኢትዮጵያ መሬት ለሱዳን ለመስጠት ቅድመ ዝግጅት መጠናቀቁን የተቃወሙ ኢትዮጵያውያን ዛሬ ጠዋት በዋሽንግተን ዲሲ የሱዳን ኤምባሲ ፊት ለፊት የተቃውሞ ድምጻቸውን ሲያሰሙ ዋሉ።

DC-ethiopian-sudan

“የወያኔ መንግስት ሃገርን በመሸጥና በመክዳት የኢትዮጵያን መሬት ለሱዳን አሳልፎ በመስጠትና ነዋሪዎችንም በማባረር እየፈጸመ ያለው ወንጀል ዝም ሊባል” አይገባም የሚሉት እነዚሁ ሃገር ወዳድ ኢትዮጵያውያን የሱዳን መንግስት ከዚህ ወንጀል ጋር ተባባሪ እንዳይሆን በተቃውሞ ሰልፋቸው ጠይቀዋል። በሰልፉ ላይ ከተሰሙ መፈክሮች መካከል የሚከተለው ይገኝበታል።