US Senators introduced a resolution condemning the lethal violence used by the government of Ethiopia

Press Releases Washington, D.C. – U.S. Senators Marco Rubio (R-FL) and Ben Cardin (D-MD) today introduced a resolution with 11 other senators condemning the lethal violence used by the government of Ethiopia against protestors, journalists and others in civil society Read More ...

The post US Senators introduced a resolution condemning the lethal violence used by the government of Ethiopia appeared first on 6KILO.com.

More than 140 Nure Ethiopians murdered by Murle of South Sudan

(ADDIS ABABA) – A massive and coordinated attack by combined military and armed Mulre civilians from South Sudan’s Buma state [Jonglei state] has left at least 221 people dead on both sides. The deadly attack occurred on Friday morning when Read More ...

The post More than 140 Nure Ethiopians murdered by Murle of South Sudan appeared first on 6KILO.com.

More than 140 Nure Ethiopians murdered by Murle of South Sudan

(ADDIS ABABA) – A massive and coordinated attack by combined military and armed Mulre civilians from South Sudan’s Buma state [Jonglei state] has left at least 221 people dead on both sides. The deadly attack occurred on Friday morning when Read More ...

The post More than 140 Nure Ethiopians murdered by Murle of South Sudan appeared first on 6KILO.com.

አርማጭሆ መልስ፤ ወደ ወገራ ጉዞ ክፍል ፬

አርማጭሆ መልስ፤ ወደ ወገራ ጉዞ

ክፍል ፬

ከአርማጭሆ ጎንደር ስገባ ድርገት ነበር፡፡ በጣም መሽቷል፡፡ ቀበሌ 12 ቢራ ለመጠጣትና ወሬ ለመቃረም ገባሁ፡፡ የገባሁባት ቤት አንድ ጊዜ ከአንድ ወዳጄ ጋር አውቃታለሁ፡፡ የቀበሌ ቤት ናት፡፡ ቤቷ ከዐሥር ሰዎች በላይ በአንድ ጊዜ ማስተናገድ አትችልም፡፡ ስለዚህ ደንበኞች በአንድ ሰዓት ከገቡ ሌላ የውጭ ሰው መግባት አይችልም፡፡ ከዚህች ቤት የማይዳሰስ ፖለቲካ አሊያም አገራዊ ጉዳይ የለም ማለት ይችላል፡፡ ቤቷን በወሬ ማድመቅ የሚችል ሰው መቼም ቢሆን ቢራ ከፍሎ ላይጠጣ ይችላል፡፡ ሞቅ ያለው የሰሊጥ ነጋዴ ‹‹አባቴ ይሙት!›› እያለ የሁሉንም ሰው የሳምንት ሒሳብ ሊዘጋ ይችላል፡፡ የቻልከውን ያክል እየጠጣህ መጫወት ነው፡፡

ከዚህች ቤት ብዙ ነገር ለመረዳት ችያለሁ፡፡ የተሸከምነው አምባገነን ሥርዓት በዜጎች መካከል አለመተማመን ፈጥሯል፡፡ የዚች ቤት ደንበኞች ሕወሓት በዐማራው ሕዝብ ላይ የሚያደርሰው ግፍ ከመጠን የዘለለ መሆኑን ያምናሉ፡፡ ከመጠጥ ደንበኞች መካከል የሰሜን ጎንደር ፖሊስ መምሪያ በኃላፊነት ቦታ ላይ እንዳሉ የተረደዋቸው ሰዎች ሁሉ ነበሩበት፡፡ የጎንደር ዐማሮች ሕወሓትንና የትግራይ ሕዝብን አንድ አድርገው ይመለከታሉ፤ እርግጥ ነው ይህ በብዙ የአገራችን አካባቢዎች እንዳለ አውቃለሁ፡፡ ጎንደር ግን በግልጽ ያለ ምንም ፍርሐት እከሌ አለ የለም ሳይባል በግልጽ የሚወራ አሊያም የሚነገር ነው፡፡ ከዚችው መሸታ ቤት የሰማሁት እውነታ (ቀልድ ሊሆን ይችላል) አስተሳሰቡ ምን ያክል የሰረጸ እንደሆነ ሊሳይ ይችላል፡፡

አንድ ከሽሬ የመጣ ሰው ቸቸላ ሆስፒታሉ ጋር ለመሔድ መስቀል አደባባይ ላይ ባጃጅ ኮንትራት ይጠይቃል፡፡

‹‹ዋይ! አንተ ቸቸላ ሆስፒታል ስንት ትወስደኛለህ ኮንትራት?›› ይላል ከትግራይ የመጣው ሰው፡፡

የባጃጅ ሾፌሩ ‹‹መቶ ብር!›› በማለት ይመልሳል፡፡ ከመስቀል አደባባይ እስከ ቸቸላ ሆስፒታል የኹለት ብር ታክሲ ትራንስፖርት ነው፡፡ ኮንትራት የሚይዝ ሰው ከዐሥር ብር የበለጠ አይከፍልም፡፡ ሆኖም እንግዳው ሰው ባልጠበቀው የዋጋ መናር ተገርሞ ‹‹ዋይ አቡነ አረጋይ! አንተ ለዚህ ቸቸላ ሙቶ ብር ያልከኝ አገሬን ሽረ አድርሰኝ ብልህ ስንት ልትወስደኝ ነው?›› በማለት የባጃጅ ሾፌሩን ጠየቀው፡፡

‹‹ተመልሰህ ካልመጣህ በነጻ እወስድሃለሁ!›› በማለት መለሰለት፡፡

ይህ እዚች መሸታ ቤት ሲነገር የሰማሁት ነው፡፡ መሸተኞች የራሳቸው ጓደኛ እንደተናገረው አድርገው ነው ያወሩት፡፡ ቁም ነገሩ እውነት ወይም ቀልድ መሆኑ ላይ አይደለም፡፡ የትኛውም ቢሆን አገዛዙ የትግራይ ተወላጆች እንደ ባዕድ እንዲቆጠሩ አድርጓቸዋል፤ ትግሬዎች በየትኛውም የአማራ አካባቢ በጥርጣሬ ይታያሉ፡፡ ይህ ከኹለት ነገር ሊፈጠር ችሏል፡፡ አንደኛ አገዛዙ ወደ ተለያዩ አካባቢዎች የሚልካቸው ደኅንነቶች የትግራይ ተወላጆች መሆናቸው ትግሬ የተባለ ፍጥረት ሁሉ የአገዛዙ አጋዥ እንደሆኑ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ ሌላኛው ምክንያት ደግሞ አገዛዙ የትግሬዎችን መጠላት የሚፈልገው ይመስላል፡፡ ምክንያቱም ትግሬዎች በሌሎች ኢትዮጵያውያን እንደጠላት ሲቆጠሩ አንድነታቸውን አጠናክረው ሕወሓትን ሊደግፉ ይችላሉ ከሚል ያረጀ ያፈጀ የፖለቲካ ፍልስፍና የመጣ ሊሆን ይችላል፡፡

በጣም ረጅም የበረሀ መንገዶችን ሳቆራርጥ ሰንብቼ በምሽትም መሸታ ለመሸታ ቤት መንከራተቴ ያለኝን ጊዜ ለመቆጠብ መሆኑን አንባቢ ይረደዋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ካደርኩበት የ‹ኤል ሸፕ› ሆቴል ሰማዩ ገና የአህያ ሆድ ሳይመስል ነቃው፡፡ በድካም የሰነበተ ሰውነቴን በቀዝቃዛ ውኃ ነክሬ በጠዋት ወደ ደባርቅ አቅጣጫ ወጣሁ፡፡ ትናንት ወደ አርማጭሆ የሔድኩበትን አቅጣጫ ትቼ ወደ ኮሶዬ አመራሁ፡፡ የዛሬው መንገዴ ትናንት የሔድኩበትን በርሀ ወደ ታች እየተመለከትኩ ደጋ ደጋውን ነው፡፡ ከጎንደር ከተማ ርቄ አሁን ወገራ ወረዳ እገኛለሁ፡፡ በደጋማው የወጋራ አፋፍ ላይ ሆኘ የአርማጭሆና የኹመራ ጫካ ታዬኝ፡፡ ‹‹ኧረ ጥራኝ ጫካው›› አልኩኝ በውስጤ፡፡

የወገራ እረኛ በቅርርቶ፤

‹‹ኧረ ጥራኝ ጫካው ኧረ ጥራኝ ዱሩ

ላንተም ይሻልሃል ብቻን ከማደሩ፡፡

ተንኮለኛው ገደል በሬ ያሳልፋል፤ ዝንጀሮን ይጠልፋል

ጂል ያመጣው ነገር ለሁሉም ይተርፋል›› ኮሶዬ አፋፉ ላይ ሆኖ ዋሽንቱን ከድምጹ ጋር እያቀናጀ ይሸልላል፡፡

ምን ታደርገዋልህ! እኔ ከጫካ ጋር የማደር ልምድ የለኝም፡፡ ከራማዬ ከአርማጭሆና ከቋራ ጫካዎች ጋር ስላልሆነ ቻው ብያቸው መጥቻለሁ፡፡ እተራራው ላይ ሆኜ እንደገና ሳያቸው ለምን እንደ እናቴ ልጅ እንደናፈቁኝ አላውቅም፡፡ የምር ግን በጭጋግ የተሸፈነውን ከአድማስ ማዶ ዓይኔ እስኪታክተኝ የማየው የሆነ የሚናፍቅ፣ የሚስብ ነገር አለው፡፡ ‹‹አልበር እንዳሞራ›› ነው ነገሩ፡፡ ወይ እንደ አእዋፋት አሊያም እንደ መላእክት ሆኜ ክንፍ ቢኖረኝ ኖሮ ምንኛ በታደልኩ፡፡ በ‹‹ኖሮ›› አይኖርም፤ ወደ ከምናቤ ልወጣ ግድ ነው፡፡

የኮሶዬ ነፋሻማ ሜዳ ከጎንደር በግምት 15 ኪሎ ሜትሮች አካባቢ ይርቃል፡፡ ኮሶዬ ለዓይን የሚስብ ገደል ጫፍ ያለ ሜዳማ ቦታ ነው፡፡ ነፋሻማና ብርዳማ ነው፡፡ በጠዋት ስለደርስኩ የብርዱ ነገር አይጣል ነው፡፡ የኮሶዬ ሜዳ ገደሉ ጫፍ ላይ ሎጅ አለ፡፡ የሎጂው አልቤርጎዎች በእሳር ክዳን (ትኩል) የተሠሩና በነገሥታቱ የተሠየሙ ናቸው፡፡ ሎጂውን እየዞርኩ ስመለከት በአጼ ኃይለ ሥላሴና በንግሥት ኤልሳቤጥ የተሰየሙ የጎጆ አልቤርጎዎች (ትኩል) ሳይ ጊዜ ለምን እንደሆነ ሰዎችን ጠየቅኩ፡፡

ንግሥት ኤልሳቤጥ ኢትዮጵያን በ1956/7 ዓ.ም. ከንጉሠ ነገሥት አጼ ኃይለ ሥላሴ ጋር ስትጎበኝ ካየቻቸው ቦታዎች መካከል የጢስ አባይ ፏፏቴና የሰሜን ተራሮች ይገኙበታል፡፡ የሰሜን ተራሮችን ከንጉሠ ነገሥቱ ጋር ጎብኝታ ስተመለስ መስንግዶ የሚደረግበትን ቦታ መምረጥ ያስፈልግ ነበር፡፡ ከዚህ አካባቢ ከኮሶየ የተሻለ መስህብነት ያለው ቦታ ጠፋ፡፡ ከእከሌ ሆቴል አሊያም ሎጅ የሚሉት ነገር አልነበረም፡፡ ኮሶዬ መስኩ ላይ የአካባቢው ነዋሪዎች የሰባውን ሰንጋ አርደው በብላክ ሌቨል ፋንታ የወገራን ጠላ ዘልለው፤ በእንግሊዝ ኬክ ፋንታ የጎንደርን እንጀራ አዋጥተው የታላቋን ኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥትና የታላቋን ብሪታኒያ ንግሥተ ነገሥት ለመቀበል ዳስ ሠሩ፡፡ በዚህ ቦታ የሁለት ታላላቅ ርዕሳነ ብሔራት ተስተናግደዋል፡፡ ያኔ አሁን ከተራራው አናት ላይ ያለው ሎጂ አልነበረም፡፡ ያኔ ሎጅ ሳይሆን የቆርቆሮ ክዳን የነበረው ቤት አልነበረም፡፡ የሰው ልጅ ከሠራው ይልቅ ተፈጥሮ ያበጀችው እይታ ይማርክ ነበርና ነገሥታቱ ይህን ቦታ በድንኳንና በዳስ አረፉበት፡፡ እንኳን እኔ ሐበሻው ንግሥት ኤልሳቤጥም በዚህ ቦታ ውበት ለመማረኳ አልጠራጠርም፡፡

አሁን ካለው ዘመናዊ ሎጅ የሚያስተናግድ ልጅ ‹‹የታላቋን ብሪታኒያ ንግሥትና የታላቋን ኢትዮጵያ ንጉሥ በጊዜው ያስተናገዱ አዛውንት እዚያ ጋ አሉ፤ ማገኘት ትችላለህ›› አለኝ፡፡ በደስታ እየሮጥኩ ወደ አመላከተኝ ቤት ሔድኩ፡፡ የባህር ዛፍ መከላከያ ለበቅ ባልይዝ ኖሮ ቤት የነበረው ውሻ ይበላኝ ነበር፡፡ ሆኖም ውሻው ሲታገለኝ እደጅ የነበሩ የቤተሰቡ አባለት ደረሱልኝና በውሻ ከመነከስ ተረፍኩ፡፡ የታላላቅ አገሮቹን ንጉሥና ንግሥት ያስተናገዷቸው ሰው ማግኘት እንደምፈልግ ነገርኳቸው፡፡ መደብ ላይ የተቀመጡ አዛውንት አመላከቱኝ፡፡ ጠየቅኳቸው፡፡ እድልለኛ አልነበርኩም፡፡ እኔ ያገኘዋቸው የእድሜ ባለጸጋ ንጉሡና ንግሥቲቱ ሲስተናገዱ የተመለከቱ እንጅ እራሳቸው አስተናጋጅ አልነበሩም፡፡ የሆነው ሆኖ የእድሜ ባለጸጋው ከቤታቸው ወጣ ብለው ወደ ሜዳው በብትራቸው እያመለከቱ ‹‹ድንኳን የተጣለው እዚያ ላይ ነበር፤ አይ ምን የመሠለ ሠንጋ አርደን ነበር መሠለህ! ግን ያዘጋጀነውን ሁሉ በደንብ ሳይበሉ ትተውን ሔዱ›› አሉኝ፡፡ በጊዜው ርዕሳነ ብሔሮቹን ለማስተናገድ የተመረጠ ሰው አልነበረም ወይ? የሚል ጥያቄ አቀረብኩ፡፡ አሁንም በድጋሚ ከቤታቸው በላይ ወደ ተራራማው ጫፍ እያመላከቱ ‹‹ወደ አቀበቱ መውጣት የምትችል ከሆነ መንገድ የሚመራህ ሰው ልስጥህ›› አሉኝ፡፡

የምችል አይደለሁም፡፡ ሩጫዬ ከጊዜም ከገንዘብም ጋር ነው፡፡ አንድ ቀን የጉዞዬን ጊዜ ባራዘምኩ ቁጥር የጋዜጣው መውጣት አለመውጣት ያሳስበኛል፡፡ ደግሞም በመንገድ ላይ የያዝኩት ስንቅ ቢያልቅ መመለሻ እንኳ አይኖረኝም፡፡ ስለዚህ በያዝኩት የጊዜ ገደብ መሠረት መጓዝ አለብኝ፡፡ የኮሶዬ ተራራ አናት ላይ ሆኜ ወደ በርሀው ስመለከት የተራራ ሰንሰለቶችን በጭጋግ ተሸፍነው አየሁ፡፡ ትናንት የነበርኩበት የአርማጭሆና የጠገዴ በርሃ በርቀት ይታየኛል፡፡ በእጄ የምነካት የምትመሥለው የጩጌ ማርያም ገዳምም ከሥሬ ናት፡፡ የጩጌ ማርያም ገዳም በድንጋያማ የተራራ ሰንሰለት ላይ ያለችና በ17ኛው ክፍለ ዘመን የተገደመች ናት፡፡ ከአንድ ዓመት በፊት ሒጄ አይቻታለሁ፡፡ አካባቢውን ለማያውቁ አንባቢያን የጩጌ ማርያም ገዳምን በትንሹም ቢሆን መናገር ያለብኝ ይመስለኛል፡፡ ገዳሙን ለማየት ስሔድ የያዝኩትን ማስታዎሻ ሳገላብጥ የሚከተለውን አገኘሁ፡፡

የአገሬዉ ሰዉ ለሰዉ ብርታት የሚሰጥበትን ዘዴ ሳስብ ይገርመኛል፡፡ የወገራ ሰዉ ‹በአገጩ በዚህ በኩል በጣም ቅርብ ነዉ!› ካለህ ቢያንስ ለሰዓታት ትጓዛለህ፡፡ በትሩን በረጅሙ እያጠቆመ ‹በዚያ በኩል ቅርብ ነዉ!› ካለህ ቢያንስ ለግማሽ ቀን ትሔዳለህ፡፡ ኮሶዬ ያገኘሁት ሰው ወደ ጩጊ በየት በኩል እንደምሔድ እንዲያሳየኝ አቅጣጫውን ስጠይቀው ሊነካት ያሰባት ይመስል እያንጋጠጠ ‹‹እዚች ተራራ ገደሉ ላይ የሆነ ቤት የሚመስል ነገር ይታይሃል?›› ሲል ጠየቀኝ፡፡ ከአለንበት አፋፍ ገደል ሥር እየተመለከትኩ ጫካና አምባ ተራራ እንጅ ቤት አለመኖሩን ነገርኩት፡፡ ‹‹ያችን አምባ እያት እንጅ! ከአምባዋ ጎን ካለዉ ገደሉ ላይ ተመልከት ቤት ታያለህ!›› አለኝ፡፡ እንደምንም ከርቀት ከጭጋግ ጋር ለመለየት የሚያስቸግር ቤት አየሁ፡፡ ‹‹አየሁት አየሁት!›› ስል አጻፋ መለስኩ፡፡

‹‹ያች ብዙ ተዐምራት የተሰራባት ጩጊ ማርያም ገዳም ናት›› አለኝ፡፡ ‹‹በየት በኩል ነዉ መንገዱ?›› ተጨማሪ ጥያቄ አስከተልኩ፡፡

‹‹በዚህ ነዋ›› በግንጭሉ እየጠቆመ ገደሉን አሳዬኝ፡፡

‹‹እንዴ! ይህ እኮ እንኳን ለሰዉ ለዝንጀሮም አይመችም!›› አልኩት፡፡

ሳቀብኝና ‹‹ቅርብ ነች፡፡ በአንድ ሰዓት ውስጥ ደርሰህ መመለስ ትችላለህ!›› አለኝ፡፡ በወኔ መንገዱን ጀመርኩት፡፡

ይህን ገደል በሽርታቴ ተያያዝኩት፡፡ ገደሉ ያን ያክል እንዳየሁት የሚያስፈራ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ በቀላሉ በስበት ኃይል እየተምዘገዘግኩ ወረድኩት፡፡ በጫካ ውስጥ ፈንዛ ጅራት ካላቸዉን ጉሬዛዎች እና ዝንጀሮዎች ጋር እየተላጋሁ ከራሴ ጋር እያወራሁ ሸመጠጥኩ፡፡ ዝንጀሮዎች እየጮሁ ገደል ለገደል ሲሮጡ መርግ ቢልኩብኝ እያልኩ በፍርሃት አስጨንቀውኝ ነበር፡፡ ደግነቱ በዛፎቹ ጥላ ሥር ስለምጓዝ ትንሽ ያስፈራል እንጅ ሙቀቱ አይታወቅም፡፡ በርቀት ገዳሙን እያየሁ የደረስኩ እየመሰለኝ እኔም በአገጬ ለመንካት እየሞከርኩ ለአንድ ሰዓት ያክል ለመጓዝ ተገደድኩ፡፡

ገዳሙ መግቢያ አካባቢ አፈሩ አንሸራቶ ጉድ ሰርቶኝ ነበር፡፡ ከዚያ ቦታ ላይ ብወድቅ ማንም ሳያየኝ መዳረሻዬ ተጨማሪ ኹለት ሰዓት የሚያስኬድ ገደልን እጨርስ ነበር፡፡ ሸርተት ካሉ መዳረሻው የማይታወቅ አገርና ዓለም ነው፡፡

ገዳሙ ያለበት እጅግ ገደል የበዛበት ሰንሰለታማ የድንጋይ አምባ ነዉ፡፡ መነኮሳቱና አርድዕቱ በገደሉ ላይ እንደዚያ ሲሮጡ በዝንጅሮቹ የገደል ላይ ጉዞ መደነቄ አናደደኝ፡፡ በዚያ ገደል ‹ሰዉ ዓለምን ንቆ በባዕት ለእድሜ ልካቸዉ የሚኖሩ መነኮሳት› እንዳሉ ማየት እጅግ ይገርማል፡፡ እኔ ላንድ ቀን እንቅልፍ ወስዶኝ የምተኛ አይመስለኝም፡፡

ይህ ገዳም የተገደመው በአባ ምዕመነ ድንግል በአስራ ሰባተኛዉ ክ/ዘመን ነዉ፡፡ በአጼ ሱስንዮስ ዘመነ መንግሥት (ከ1600- 1624 ዓ.ም.) አባ ምዕመነ ድንግል ብዙ መከራንና እንግልትን እንደተቀበሉ ገድላቸው ይመሰክራል፡፡ ገዳሙ ካለበት የቋጥኝ ተራራ ወገብ ላይ ዋሻ አለ፡፡ ዋሻዉ ውስጥ ደግሞ በክረምትም በበጋም የማይሞላ የማይጎድል ‹ማዬ ዮርዳኖስ› ወይም ‹የዮርዳኖስ ዉኃ› የሚሉት አለ፡፡ ጸበሉ በርካታ ምዕመናን ይጠመቁበታል፡፡ ግን አይጎድልም፡፡ የሚጠመቅ ሰዉ ከሌለም ሞልቶ አይፈስም፡፡ አፈር በሆነበት ቦታ ምንጮች እየደረቁ ባለበት ጊዜ ግጥም ካለ ቋጥኝ ተራራ ላይ ይህ መሆኑ ለእንደኔ ዓይነቱ ተጠራጣሪ አጃኢብ ያስብላል፡፡ ጸበሉን ጠጣሁት- አይሰለችም፡፡ እንዲያዉም እዉነት ለመናገር ከመጣሁ በኋላ ናፍቆኛል፡፡ መልኩ ሀጫ በረዶ ይመስላል፡፡ በመቆሙ ብዛት አረንጓዴ (አልጌ) አልጣለበትም፡፡ ይህን ጸበል ጠጣሁትም፤ ሲያጠምቁ ያገኘዋቸው አባም አጠመቁኝ፡፡

ብቻ ግሩም ነዉ እላችኋለሁ፡፡ ጸበሉን የሚጠጡ ፍጥረታት ገላቸው (አካላቸዉ) አይፈርስም፡፡ ጸበሉን የጠጡ 16 ፍየሎች ከነ ሙሉ አካላቸዉ ለ400 ዓመታት ለገባሬ ታእምር እስካሁን አሉ፡፡ ወልደዉ ለመሳም ያልታደሉ ሰዎች ከዚህ ቦታ መጥተዉ ተጠምቀዉ ጸበሉን ቢጠጡ የልጅ ጉጉታቸዉን እዉን ለማድረግ ዘጠኝ ወራት ብቻ እንደሚያስፈልጋቸው ከገዳሙ ያገኘዋቸው አርድእት ነግረውኛል፡፡

ቦታዉ የዋልድባዉ ሰቋር ኪዳነ ምህረት ዓይነት ነዳላ አምባ አለዉ፡፡ ወደ ነዳላዉ አምባ ለመሄድ ጸበሉን የጠመቁኝ አባት በዚህ በኩል ሒድ አሉኝ ወደ ምዕራብ አቅጣጫ እያመለከቱ፡፡ በተቀደሰዉ ቦታ ጫማህን አዉልቅ በሚለዉ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መርህ መሠረት ጫማ መልበስ ክልክል ነዉ፡፡ ጫማ የለመደ እግር በሚያቃጥል አለትና በሚቆረቁር አሸዋ ላይ መሔድ ይጠበቃል፡፡ በዚያ ድንጋያማ ተራራ እንደ ገበሎ አስተኔ በልብ አሊያም በአራት እግር መጓዝ ይጠይቃል፡፡ ከዋሻዉ ማዶ ‹ሰማያዊ ኬንዳ› የመሰለ ነገር ማዶ ካለዉ ገደል ላይ ተንጣሎ ይታያል፡፡ ያ ኬንዳ ምንድን ነዉ? ስል ጠየቅኩ፡፡ በተቀደደዉ የቋጥኝ ተራራ አልፎ የሚታየዉ ሰማይ ነዉ አሉን አባ፡፡ ከጸበሉ የነበረች አንዲት እናት ጋር አብረን እንድንሔድ አባ ነገሩን፡፡ ጉዞ ወደ ነዳላዉ አምባ፡፡ አብራኝ የምትጓዘዉ እናት እጅግ የበረታች ናት፡፡ እርሷ በዚያ ገደል ላይ ከዝንጀሮ እኩል ትፈጥናለች፡፡ ተከተልኳት፡፡ ድንጋይ በድንጋይ ላይ እየወጣን ወደ ነዳላዉ አምባ ተቃረብን፡፡ ወደ ገደሉ ስንወጣ በእጃችን እየቧጠጥን ነው፤ በእጃችን አጥብቀን ከመያዛችን በፊት ያገኘነውን ጎቶ ጥንካሬ መለካት ያሻል፤ አሊያ ዲካው ወደ ማይታወቀው ገደል መጓዝ ይመጣል፡፡ ከቦታዉ ስንደርስ አንድ ሽማግሌ አባት ከንቃቃት ድንጋይ ሥር እንደቤት አደርገዉ ሲጸልዩ ደረስን፡፡ አባ ከባዕታቸዉ ፈጽመዉ አይወጡም፡፡ የምጽዋት ገንዘብም ፈጽመዉ አይቀበሉም፡፡ ፎቶ ግራፍና ምስል እንድወስድ ብጠይቃቸዉ ‹‹ልጄ አወግዝሃለሁ›› አሉኝ ተቆጥተዉ፡፡ ይቅርታ ጠይቄ አቡነ ዘበሰማያት ደግመዉልኝ በበረከት ተለየዋቸዉ፡፡

በመጨረሻ እኔን ጠየቅኩት? ‹አባቶች ለነፍሳቸዉ እና ለአገር ደኅንነት ከዱር አራዊት፣ በልባቸዉ ከሚሳቡ ነፍሳት ጋር ሁሉ እንዲህ ይታገላሉ፡፡ እኔ ግን ከዚህ ድረስ መጥቼ በረከት እንኳ መውሰድ እንዴት ተሳነኝ?› እማሆይ ማዕድ አቀረቡልን፡፡ በላን፡፡

በልቤ የአባቶቼን ጽናት እያሰብኩ ወደ መጣሁበት ዓለም ለመመለስ ተነሳሁ፡፡ ከፊቴ አምዘግዝጎ ያረወደኝን ገደልና ጫካ ለመዉጣት፡፡ ዝንጀሮዎቹን ቢያዝሉኝ ስል ተመኘሁ፡፡ ዛፍ ለዛፍ የሚሯሯጡት ዝጉርጉር ጉሬዛዎች አስቀኑኝ፡፡ በ180 ዲግሪ ቀጥ ያለው የወገራ አቀበት ፊቴ ላይ ተደቀነ፡፡

……….

ወደ አያሌው ብሩ አገር ዳባት መንገድ ጀምርኩ፡፡ አምባ ጊዎርጊስ፣ ገደብዬ፣ ዳባት፣ ወቅን፣ ደባርቅ…፡፡ ዳባት ላይ የአያሌው ብሩ ቤተ መንግሥት አለ፡፡ አያሌው ብሩ የወገራ ገዥ የነበሩ ሲሆን በአጼ ኃይለ ሥላሴ ሀትሪክ ተሠርተዋል አሉ፡፡ አጼ ኃይለ ሥላሴ ወደ አዲስ አበባ እንዲሔዱ ጥሪ ሲልኩባቸው የወገራ ሰው እንዳይሔዱ መክሯቸው ነበር፡፡ ነገር ግን የወገራን ሰው ምክር ባለመሥማታቸው የአጼው ተንኮል ሰለባ ሆነዋል፡፡ በዚህም ምክንያት ድፍን በጌምደሬ ሲዘፍን ‹‹አያሌው ሞኙ ሰው አማኙ ሰው አማኙ፤ ኧረ አያሌው ተው በለው ተው በለው›› የሚለው የእርሳቸውን ሞኝነት ለማመለከት እንደሆነ ይናገራሉ፡፡ ቀሪውን ማጣራት የባህል ተመራማሪዎች ፋንታ ይሆናል፡፡

አምባ ጊወርጊስ ላይ ሆኖ ወደ ደባርቅ ሲመለከቱ አንዲት ኮረብታ በርቀት ትታያለች፡፡ ዳባት ላይ ሆኖም ይህችው ተራራ ከትክተት አትሰወርም፡፡ ዳባትን አልፈን ደባርቅ ሆነንም እናያታለን፡፡ የሰሜን ተራሮች አናት ላይ ብንወጣም ይህችን ተራራ ማንም አይጋርደንም፡፡ ይህች ተራራ ‹‹ወቅን›› ከተባለች አነስተኛ ከተማ ራስጌ ላይ የምትገኝ ስትራቴጂክ አምባ ናት፡፡ ስያሜዋም ‹‹ዞሮ ዞሮ ወቅን›› ትሰኛለች፡፡ ዞሮ ዞሮ ወቅን ከወገራ እስከ ኹመራ፣ ከአርማጭሆ እስከ ጃናሞራ፣ ከአዲአረቃይ እስከ ሽሬ ድረስ ቁልጭ ብላ በጉልህ ትታያለች፤ ዞሮ ዞሮ ወቅን፡፡

Ethiopia told to do extensive doping tests or face IAAF ban

By Elias Meseret ADDIS ABABA, Ethiopia (AP) — Ethiopia must carry out mass doping tests on up to 200 athletes by November or be the latest to face further action by the World Anti-Doping Agency and a possible ban by Read More ...

The post Ethiopia told to do extensive doping tests or face IAAF ban appeared first on 6KILO.com.

ከጎንደር እስከ አርማጭሆ፤ የቅማንት ጉዳይ፣ የግጨው ግጭትና የኢትዮ ሱዳን ድንበር ክፍል ፫

By Muluken Tesfaw

ከጎንደር እስከ አርማጭሆ፤ የቅማንት ጉዳይ፣ የግጨው ግጭትና የኢትዮ ሱዳን ድንበር

ክፍል ፫

ወደ አርማጭሆ መንገድ ጀምረናል፡፡ የተሳፈርኩባት ሚኒ ባስ የገነት ተራራንና ወለቃን በሌሊት አልፋ ወደ ትክል ድንጋይ እየተንደረደረች ነው፡፡ በነገራችን ላይ የገነት ተራራ ‹‹ትግሬ መጯኺያ›› በመባል ይታወቅ ነበር፡፡ በታሪክ ምሁራን ለዘመነ መሣፍንት መምጣትና ለጎንደር ነገሥታት ፍጻሜ ምክንያት ነው ተብሎ የሚታወቅ ራስ ሚካኤል ስሑል የሚባል ሰው ነበር፡፡ ራስ ሚካኤል ስሁል የትግራይ ተወላጅ ሲሆን ‹ንጉሥ ሠሪ› ወይም ደግሞ ‹አንጋሽ አፍላሽ› በመባል ይታወቃል፡፡ ይህም የሆነው እንዳይነግሥ የንግሥና ዘር የለውም፤ ስለዚህ የይስሙላ ንጉሥ ዙፋን ላይ አስቀምጦ ቤተ መንግሥቱን በቁጥጥር ሥር አደረገ፡፡ በዚህ ዘመን ነገሥታቱ ከጎንደር ራቅ ባሉ አካባቢዎች በግዛታቸው ሥር ያሉትን ሁሉ ማስተዳደርም ሕግን ማስፈንም ተሳናቸው፡፡ በዚህ የተነሳ ከርቀት ቦታዎች እየመጣ ፍትሕ የሚለምነው ሰው ቁጥር በረከተ፡፡

የተከዜ ወንዝንና በርሃን ተሻግረው ለቀናት ተጉዘው ጎንደር የሚደርሱት ትግሬዎች ጎንደር ከተማ ከደረሱ በኋላም ‹ብልኮ› እተባለው ሰፈር ላይ ኬላ ተጥሎ እንዳይገቡ ይከለከሉ ነበር፡፡ ይህም የነ ራስ ሚካኤል ፍትሕ ለማግኘት የትግሬ መጯኺያ የተባለው ተራራ ላይ በመውጣት የጎንደር ቤተ መንግሥትን ወደ ታች እየተመለከቱ ‹‹በሕግ አምላክ!›› እያሉ ይጮኹ ነበር፡፡ በዚህም ያ ተራራ ‹‹ትግሬ መጯኺያ›› እንደተባለ እንዲጠራ ምክንያት ሆነ፡፡ ዞሮ ዞሮ ተራራው አሁን ገነት ተራራ ተብሎ ስሙ ተቀይሯል፡፡ ጎሃ ሆቴል የሚባል መዝናኛም በደርግ መንግሥት ተሠርቶበት ትግሬ ይዝናናበታል እንጅ አሁን ላይ አይጮኽበትም፡፡

ወለቃ ከጎንደር ከተማ ወደ ደባርቅና ወደ ኹመራ መስመር ላይ ያለች ትንሽ መንደር ነች፡፡ ወለቃ የምትታወቀው ቤተ እስራኤሎች (ፈላሻዎች) መንደር በመሆኗ ነው፡፡ እስራኤል በዘመቻ ሰሎሞን የጀመረችውን ፈላሾችን ወደ አገሯ የመውስድ ሥራ በቅርቡ አጠናቃ ጎንደር ያለውን ቆንሲል ከመዝጋቷ በፊት የፈላሾች መንደር ወለቃ ነበረች፡፡ በወለቃ አሁን ላይ የዳዊት ኮከብ በሰማያዊ ቀለምና በነጭ መደብ የተሳለባት አንዲት የጀበና ቡና ቤት ውጭ አንድም አይሁድ ወይም የአይሁዳዊነት ምልክት አይታይም፡፡ የአይሁዳውያን መንደር ነበረች በሚል ብቻ ትታወሳለች፡፡

ላይ አርማጭሆ ትክል ድንጋይ እየደረስን ነው፡፡ ትክል ድንጋይ ከቅማንት ማንነት ጋር ችግር ከተፈጠረባቸው ቦታዎች አንዷ ናት፡፡ በነገራችን ላይ ከቅማንት የማንነት ጥያቄ ጋር በተያያዘ በዚህ አካባቢም እንደ ጭልጋው ሁሉ የከፋ ነገር ተከስቷል፡፡ ከ2006 ጀምሮ እስከ 2008 ዓ.ም. ግማሽ ዓመት ድረስ በሰሜን ጎንደር ብዙ ፍርድ ቤቶች የሚመጡ ክሶች የፍች ጥያቄዎች ያዘሉ ነበሩ፡፡ በጥብቅና እና በዳኝነት ሥራ ላይ የተሰማሩ አንዳንድ ግለሰቦች እንዳረጋገጡልኝ በርካታ ጥንዶች ‹ሰይጣን› በመካከላቸው ገብቶ ትዳራቸውን ንዶታል፡፡ በአማርኛ እያወሩ በግእዝ የሚያስቀድሱ በሥርዓተ ተክሊል ጸሎት ተጋብተው ‹አይ ትዳር እንደነሱ ነውጅ!› እየተባሉ ሲነገርላቸው የነበሩ ጥንዶች ቤት በድንገት የሚፈርሰው ‹ሉሲፈር› በመካከላቸው ካልተገኘ በስተቀር እንዴት ሊሆን ይችላል? አባ የንስሀ ልጆቻቸውን እሁድ እሁድ ሰብስበው ‹ስለ ፍቅረ ቢጽ› ሲያስተምሩ ‹ትዳርና ፍቅር እንደ እነ እንትና ነው!› እያሉ በአርኣያነት ሲጠቅሷቸው የነበሩ ጥንዶች ቤት በሰዓታት ውስጥ የቤታቸው ዋልታና ማገር ፈርሷል፡፡ ሕጻናት ትምህርት ቤት ደርሰው ሲመለሱ የወላጆቻቸውን ፍቅርና እንክብካቤ ሲናፍቁ እንዳልነበር ከአባት ወይም ከእናት ጋር ማን እንደሚቀር የልጆች ክፍፍል ተመልሶ ለልጆች ሰቀቀን ሆነ፡፡ ቤተሰብ ይሉት ተቋም ተናደ፤ ፈረሰ፡፡ ልጆችም ተበተኑ፡፡ የሃይማኖት አባቶች ትዳር ሲፈርስ እያዩ ምንም ማድረግ የማይችሉት ነገር ገጠማቸው፡፡ የአርባ አራቱ ታቦታት ጠበል ይህን የገባ ሰይጣን ፈውስ መስጠት ተሳነው፡፡ በቃ! ቅማንትና አማራ በሚል ሰበብ የስንት ሰው ሕይወት አደጋ ላይ ወደቀ? የቤተሰብ ፍቅር እንዲህ እንዳልነበር ሲሆን ማየት በጣም የሚያም ነገር ነው፡፡

ትዳር እንዴት ይፈርስ እንደነበር ለማስረጃ ይሆን ዘንድ የአንድ ሰው ታሪክ ከዚህ ላይ መናገር ፈለግኩ፡፡ ግለሰቡ ታሪኩን ያጫወተኝ በዚህ መልክ ነበር፡፡ ‹‹አስራ ሰባት ዓመታት ከሚስቴ ጋር አብረን ስንኖር ስለ እርሷ ማንነት የማዉቀው ነገር አልነበረኝም፡፡ ሰዉነቷ ብቻ በቂዬ ነበር፡፡ እዉነቴን ነዉ የምልህ የጎንደር ልጅ ከመሆኗ ዉጭ የማዉቀው አልነበረኝም፡፡ በጋብቻችን ለአቻዎቻችን አርኣያ የምንሆን ሰዎች ነበርን፡፡ በትዳራችን 3 ልጆችን አፍርተናል፡፡ የመጀመሪያዋ ልጄ 16 ዓመቷ ነዉ፡፡ ባለፈዉ ዓመት የጥቅምት መድኃኒዓለም ሊደርስ አንድ ሳምንት ሲቀረው እናቷ ደወሉልኝና ‹ለመድኃኒዓልም ዝክር ዝግጅት ታግዘኝ ላካት› አሉኝ (አማትን አንቱ በማለት ነው የሚጠራው)፡፡ እኔም እናቷን እንድታግዝ መሔዷን በደስታ ተቀበልኩ፡፡ የጥቅምት መድኃኒዓለም አልፎ ግን ከነገ ዛሬ ትመጣለች እያልኩ ከልጆቼ ጋር ብናያት የዉሃ ሽታ ሆነች፡፡ ስልክ ስንደዉል ስልኳን ዘግታለች፡፡ መጨረሻ ቤተሰቦቿ ካሉበት ቦታ ትክል ድንጋይ ሰዉ ተላከ፡፡ የተላኩት ሰዎች ‹ልጃችን ‹አማራ› አግብታ አትኖርም!› የሚል መልስ ተነገራቸው፡፡ አንድ ዓመት ያልሞላዉን ሕጻን ልጅ እና ሌሎቹንም ልጆቿን ትታ ለመቅረት እንደወሰነች ሰማሁ፡፡ በቄስ በሽማግሌ አስጠየቅኳት፡፡ ፈቃደኛ ልትሆን አልቻለችም፡፡ የሚገርምህ ልጆቼ ሲያድጉ ሠራተኛ አያውቁም፡፡ ሠራተኛ በዘመድ አፈላልጌ ቢያንስ ምግብ እንድታዘጋጅልን አደረግኩ፡፡ ልጆቼ ግን ሌላ ሰው የሠራውን ተመግበው ስለማያውቁ አስቸገሩኝ፡፡ ስለዚህ ምጣድ ሁሉ ሳይቀር እየጋገርኩ ልጆቼን ለማሳደግ ሞከርኩ፡፡ በዚያ ላይ ሕጻኑ ልጅ ሌሊት ላይ እማዬ እያለ ጡት ለመጥባት ፈልጎ ሲያጣት ያለቅስብኛል፡፡ ቤታችን ሁሉ ነገር ምሉእ ነበር፡፡ ግን በዚህ ምክንያት የምወዳትን ሚስቴን አጣሁ፤ ቤተሰቤም ፈረሰ›› አለኝ፡፡ ይህ ግለሰብ የነገረኝ ብዙ የሚያም ነገር አለው፡፡ ቢሆንም የጠቀስኩት ለግንዛቤ በቂ ነው፡፡

ይህ የአንድ ሰው ታሪክ ብቻ አይደለም፡፡ ሳይጠፋፉ በሰላም የተለያዩማ እድለኞች ነበሩ፡፡ በዚህ መካከል የሚያድጉ ሕጻናት በሕሊና ሊጎዱ የሚችሉትን ሳስብ አዝናለሁ፡፡ ሆኖም የደማውን ሕሊናየን የሚያክም ነገርም አገኘሁ፡፡ አሁን ላይ ‹በሁለቱም ወገን› ጎራ ከፍለው ሲናከሱ የነበሩ ሁሉ ትምህርት ወስደዋል፡፡ የችግሩ ምንጭ እነርሱ አለመሆናቸውን አምነዋል፡፡ ዛሬ ላይ የአድባር ዛፍ ሥር የተቀመጡ ነጭ ሸማ የለበሱ ሰዎችን ካያችሁ የፈረሰው ትዳር እንደገና ሲጠገን ነው፡፡ እንዳልነበር የሆነው ቤተሰብ ፍቅር በዛፉ አድባር ሲመለስ ነው፡፡ የገባው ሰይጣንም በአርባ አራቱ ታቦት ጸበል ተረጭቶ ሲወጣ ነው፡፡ አሁን ላይ ጎረቤታሞች ቡና እተጠራሩ ነው፡፡ ይህ ለእኔ ትልቅ እፎይታን ሰጥቶኛል፡፡ ከላይ የገለጽኩት ግለሰብም ከባለቤቱ ጋር ለመታረቅ ሙከራ ላይ እንዳለ ነግሮኛል፡፡ ትንሽ ቀናት ሰንብቼ ቢሆን ኖሮ የቤተሰቡን ፍቅር ሲታደስ አይቼ እንደምመጣ እርግጠኛ ነበርኩ፡፡

ከትክል ድንጋይ ወደ ታች አርማጭሆ ሳንጃ ጉዞ ቀጥያለሁ፡፡ በዚች ከተማ የማይረሳ ታሪክ አለኝ፡፡ ሳንጃ ከሁለት ዓመት በፊት አውቃታለሁ፡፡ አሁንም የተለወጠ ነገር የለም፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት ያየኋት ሳንጃ ምንም የተቀየረችው ነገር የለም፡፡ ሙቀቷ ብቻ ትንሽ ሳያይል አልቀረም፡፡ በአካባቢው የነበረው ደንም የተመናመነ መሠለኝ፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት ለተመሳሳይ ሥራ አሽሬ፣ ዳንሻና ሶሮቃ ደርሰን ከአንድ ወዳጄ ጋር ስንመለስ ሳንጃ ላይ መሸብን፡፡ ሳንጃ ቤርጎ ለመከራየት ስንዘዋወር አብሮኝ የነበረው ጓዴ ዩንቨርሲቲ አብሮት የተማረ የአርማጭሆ ጓደኛውን አገኘነው፡፡ ይህ የጓዴ ጓደኛ ‹‹እኛ ቤት ካልሔዳችሁ!›› ብሎ ገለገለን፡፡ ተከትለነው ሔድን፡፡ በእንግድነት ቤት እግራችን ታጥበን የሚበላውና የሚጠጣው በገፍ ቀረበልን፡፡ አልጋ ተለቆልን እንድንተኛ ቢነገረንም እንቅልፍ የማያስተኛ ነገር ገጠመን፡፡

በአርማጭሆ ደም የሚባል መጥፎ ነገር አለ፡፡ በእንግድነት የገባንበት ቤትም ደም የተቃቡ ሰዎች ነበሩ፡፡ እኛ ቤት ከመድረሳችን አንድ ሳምንት ያክል ቀደም ብሎ የጓደኛችን አያት (የአባቱን እናት) ሰው ገደላት፡፡ እንደነገሩን ከሆን በአርማጭሆ ሴት መግደል ነውር ነው፡፡ ሆኖም ግን አልፎ አልፎ እንዲህ ዓይነት ነገር መከሰቱ አይቀርም፡፡ በአርማጭሆ ሰው የተገደለበት ወገን የገዳዩን ተመሳሳይ ወገን ካልገደለ አስከሬኑ አይቀበርም፡፡ ስለዚህ በሰው የተገደለ ሰው ካለ ሌላም እንደሚጨመር መገመቱ ቀላል ነው፡፡ የገዳይ ዘመዶች በተቻላቸው መጠን ከአካባቢው ርቀው ቢሸሹም ከመገደል አይድኑም፡፡ ደም ያልመለሰ ሰው ሁልጊዜም መሰደቢያ ይሆናል፡፡ ደም መመላለስን በተመለከተ ብዙ ገራሚ ነገሮች አሉ፡፡ ሚስቱን አስረግዞ የተገደለ አባት የተወለደው ልጅ አድጎ የአባቱን ደም የመለሰበት አጋጠሚም አለ፡፡ ወንድ ልጅ ቢጠፋ በአርማጭሆ ሴት ደሟን ትመልሳለች፡፡ የአባቱን ወይም የወንድሙን አሊያም የጓደኛውን ደም የመለሰ ሰው ደመላሽ ይሰኛል፡፡ ኮረዳዎች ይገጥሙለታል፤ የዘፍን ቅኔን ይቀኙለታል፡፡ አሊያ ግን በድፍን አርማጭሆ አንገቱን ደፍቶ መኖሩ ነው፡፡ ወደ ቀደመው ነገር ስመለስ የጓደኛችን አባት የገደለበትን ሰው እናት ሳንጃ ከተማ መግቢያው አካባቢ ወንዝ ውኃ ስትቀዳ አገኛትና እዚያው ከእነተሸከመችው እንስራ አሰናበታት፡፡ ሁለቱም እናቶች ተቀበሩ፡፡ ነገር ግን ደም አይደርቅምና ቀጣዩን ሟች ከየትኛው ወገን እንደሚሆን ስለማይታወቅ ከሁለቱም ወገን መፈላለግ ጀመሩ፡፡ እኛ በእንግድነት ባህል እግራችን ታጥበን በልተንና ጠጥተን የሚመች አልጋ ላይ ተኝተን አባትና ልጅ በየተራ መሣሪያ በር ላይ ደቅነው ይጠብቁ ጀመር፡፡ መሣሪያ የያዘ ሰው ከበር ላይ ተቀምጦ እኛ እንዴት እንቅልፍ ይውሰደን? የመከራ ሌሊት ረጅም ነው እንዲሉ እኛም እንቅልፍ በዓይናችን ሳይዞር አድረን አርማጭሆን ለቀን ወጥተናል፡፡

አሁንም ድጋሚ ሳንጃ ተከስቻለሁ፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት ያስተናገደንን የጓደኛየን ጓደኛ ሳንጃ ላይ አገኘሁት፡፡ ይህ መልካም ወዳጄ የቅማንት ቤተሰብ ልጅ መሆኑን በዚህ ዓመት ነገረኝ፡፡ በፊት ስለነበረው የደም መቀባባት ጉዳይ ሳነሳለት እያዘነ ‹‹ባለፉት ጊዜያት ደም ስትቃባ ጠብህ ከግለሰቦች ጋር ብቻ ነበር፤ አሁን ግን አንድ ሰው ከተገደለ ‹የገደለው እኮ እሱ አማራ ወይም ቅማንት ስለሆነ ነው› እየተባለ ወደ ቡድን ጠብ ይቀየራል፡፡ ብዙዎቹ ዘመዶቼ ወደ ትክል ድንጋይ ናቸው፡፡ ላይ አርማጭሆ የተያዘው ነገር እንዲህ ያለ ነው፡፡ ምን እንደሚሻል አላውቅም›› አለኝ፡፡ ወዳጄ በተፈጠረው ነገር ካዘኑ ሰዎች መካከል ነው፡፡ እርግጥ ነው ያላዘነ ሰው የለም፡፡ ነገሮች አሁንም በዚህ መልኩ መቀጠል አለመቀጠላቸውን ላነሳሁለት ጥያቄ ‹‹እርግጥ ነው አሁን መሻሻሎች አሉ፤ ብዙ ዘመዶቼ ላይ አርማጭሆ ስለሆኑ እሔዳለሁ፡፡ በጉዳዩ ላይ እንወያያለን፡፡ ይህ በሕወሓት የተፈጠረ ሴራ መድረቅ እንዳለበት ዘመዶቼ ሁሉ ያምናሉ›› የሚል መልስ ሰጠኝ፡፡

ይህ ወዳጄ በአካባቢው ያደረግኩትን ጥናት ቀና እንዲሆን ብዙ አግዞኛል፡፡ አንዳንዶቹ ነገሮች በአንድ ኢትዮጵያ በምንላት አገር እየኖርን መሆን አለመሆኑን እንድንጠይቅ ሊያደርጉን ይችላሉ፡፡ ባለፈው ዓመት በምዕራብ አርማጭሆ ግጨው በተባለው አካባቢ የቀለጠ ጦርነት ነበር፡፡ ምክንያቱ ደግሞ የሚከተለው ነው፡፡

ችግሩ ከተጠነሰሰ ስድት ዓመታት አልፈዋል፡፡ የሕወሓትን የተስፋፊነት እቅድ በአርማጭሆና ጠገዴ ከሚኖረው ሕዝብ የበለጠ የሚያውቀው የለም፡፡ ይህን የተገነዘቡ የጠገዴና የአርማጭሆ ባላባቶች በአርማጭሆ የተለያዩ አካባቢዎች የዛሬ ስድት አመት ገደማ ቀለም ይዘዉ ዛፎቹን እያቀለሙ ደንበር አበጁ፡፡ ክረምት አልፎ ክረምት ሲተካ ዛፎቹ ላይ የተቀባው ቀለምም እየጠፋ ድንበሩም እየፈረሰ ሔደ፡፡ የተወሰኑ የሕወሓት አራሾች በየዓመቱ ትንሽ ትንሽ እያለፉ ማረስ ጀመሩ፡፡ ለምን? ብለዉ የሚጠይቁ ሰዎች ሲበርክቱ የሁለቱ ክልል መንግሥታት ጣልቃ ገብተዉ ካርታ ሠሩ፡፡ በዚህ ካርታ መሠረት ግጨው በሰሜን ጎንደር ሥር አረፈ፡፡ ከዳንሻ ጀምሮ እስከ ግጨው የተዘረጋ ትልቅ የወያኔ እርሻ አለ፡፡ የትግራይ ልማት ማኅበር እርጎየ ላይ ትምህርት ቤት ሠራ፡፡ የልማት ማኅበሩ የሠራው ትምህርት ቤት ለምን እንደሆነ የተገዘበ ሰው አልነበረም፡፡ በአርማጭሆነና በጠገዴ ያሉ የብአዴን አመራር ካቢኔዎች ሆን ተብሎ ይሁን አሊያም ባጋጣሚ በእናታቸው ወይም ባባታቸው አሊያም ሙሉ በሙሉ የትግራይ ተወላጅ የሆኑ ይበዛሉ፡፡

በሰኔ 2006 ዓ.ም. የክረምት መግቢያ ላይ የሕወሓት የጦር ተመላሽ የሰሊጥ አምራቾች ግጨዉ ከተባለዉ ተራራ አልፈዉ መመንጠር ጀመሩ፡፡ የአርማጭሆና የጠገዴ ሕዝብ አይሆንም ብለዉ በኃይል አባረሯቸዉ፡፡ ከጠገዴ ወረዳ ፖሊስ ሊያጣራ አንድ ኮንስታብል ማዕረግ ያለው ሰው ተላከ፡፡ ለእርሻ የመጡትን ሰዎች የእነርሱ ቦታ አለመሆኑን ነገሮ የአካባቢውን ገበሬዎችም አረጋግቶ ተመለሰ፡፡ ወደዚህ ቦታ የተላከዉ ፖሊስ ግዳጁን ፈጽሞ ከተመለሰ በኋላ በምን እና ማን እንደገደለዉ ሳይታወቅ በአገር አማን በጥይት ተገድሎ ተገኘ፡፡

ሰሊጥ አምራቾቹ እንደገና ተመልሰዉ መጥተዉ ሰሊጥ ለመዝራት ሞከሩ፡፡ ገበሬዎችም እንደገና ለመዝራት ከመጡት ሰዎች ጋር ተጣሉ፡፡ ችገሩ እየተባባሰ በመጣበት ወቅት የወረዳው ፖሊስ አዛዥ ለዞንም ሆነ ለክልል እርዳታ ሳይጠይቅ አፍኖ ያዘው፡፡ የፖሊስ አዛዡ ችግር ወደተፈጠረበት የሚሔዱ ጓዶቹን በግጭቱ መካከል ገብተው እነርሱ ላይ ለሚደርስ ጉዳት ሁሉ ኃላፊነት እንደማይወስድ አስጠንቅቆ ላካቸው፤ በርቀት ቆመዉ እንዲታዘቡ እንጅ ገብተዉ እንዲገላግሉ የፈለገ አይመስልም፡፡

ችገሩ እየጠነከረ ሲሔድ የሚገደሉ ሰዎችም ቁጥር ጨመረ፡፡ የፖሊስ አዛዡ ለአማራ ክልል ፖሊስ ኮሚሽን በስልክ አሳወቀ፡፡ ግን ይፋ ጦርነቱ ተጀመሮ ነበር፡፡ የትግራይና የአማራ ተወላጆች በየጎራቸዉ ተሰለፉ፡፡ የሰሜን ጎንደር ዞን የአማራ አድማ በታኝ ፖሊስ ላከ፡፡ የትግራይ ክልል ልዩ ኃይልና አድማ በታኝ ፖሊሶች የሲቪል ልብስ ለብሰው ግን ደግሞ እስከ አፍንጫቸዉ ታጥቀው ወደ ጦርነት ገቡ፡፡ በሲቪል ሰዎች መካከል የተደረገ ግጭት ለማስመሰል የታቀደ መሆኑ ነው፡፡ ግጨዉ ተራራ በአንድ ቀን ዉስጥ ወደ ጦር ሜዳነት ተቀየረች፡፡ ከሳንጃና ትክል ድንጋይ ብዙ ወጣቶች ወደ ግጭው ሲሔዱ መንገዱ ተዘጋ፡፡ ለቀናት ከጎንደር ኹመራ የመኪና መንገድ አገልግሎት መስጠት አቋረጠ፡፡ ምርኮ ሁሉ ነበረ፡፡ ይህ ሁሉ ነገር ከተፈጸመ በኋላ በሽምግልና ግጭቱ በረደ፡፡ ሕወሓት በወልቃይና በጠገዴ የተነሳውን እንቅስቃሴ ለማፈን እንዲያውም ግዛቴ ከዚህም የሰፋ ነው የሚል አስተሳሰብ ለመፍጠር ያደረገው ይመስላል፡፡

የፌደራል መንግሥት የሚያሠራው ከኹመራ ተነስቶ በማይካድራና አብደራፊ አልፎ መተማ የሚገባ መንገድ አለ፡፡ መንገዱን የያዘው ሱር የተባለ ኮንስትራክሽን ነው፡፡ በአቶ አባይ ወልዱ ትእዛዝ ከማይካድራ ቀጥታ ወደ ሱዳን ታጥፎ እንዲሠራ ይደረጋል፡፡ አቻቸው አቶ ገዱ ደግሞ የአቶ አባይን ትእዛዝ ጥሰው ወደ መተማ እንዲሠራ አደረጉት፡፡ አቶ ገዱ በምዕራብ አርማጭሆ የሚመረተውን ሰሊጥ ወደ ትግራይ ክልል እንዳይሔድ አብራጂራ ላይ ኬላ ተክለው የኢትዮጵያ የእህል ንግድ ድርጅትም እዚያው ቅርንጫፍ ጽ/ቤት እንዲከፍቱ በማስደረጋቸው በአካባቢው ስማቸውን ለመገንባት ጥረዋል፡፡ ብአዴን ለአማራው ሕዝብ የአህያ ባል እንደሆነ ማንም እያወቀ አካባቢው በአቶ ገዱ ላይ የጣለው እምነት ጉድ እንዳይሠራቸው እሰጋለሁ፡፡

ድንበር ጠባቂው ባሻ ጥጋቡ

በምዕራብ አርማጭሆ እጅግ ሰፊ የሆነና ለም መሬት በሱዳን መንግሥት ቁጥጥር ሥር መሆኑን በተለያየ የአርማጭሆ አካባቢዎች የሚኖሩ ብዙ ሰዎች ነግረውኛል፡፡ በዚህ አካባቢ የነበሩ ቦታዎች ሁሉ አረብኛ ትርጓሜም እየተሰጣቸው ነው፡፡ በእርግጥ ቀደም ባሉት ጊዜያትም ቢሆን ብዙ ቦታዎች የአረብኛ ትርጓሜ ያላቸው አሉ፡፡ ለምሳሌ አብደራፈፊ የሚባለው ከተማ ስያሜ ‹አብደላ ፊ› ከሚል ከአረብኛ ቃል የተገኘ ሲሆን ትርጓሜውም ‹አብደላ አለ› የሚል ነው፡፡ ያ ማለት ግን አካባቢው የሱዳን ነው ወይም ነበረ ማለት አይደለም፡፡ ሕዝቡ አረብኛን አቀላጥፎ ይናገራል፡፡ የሆነው ሆኖ በርካታ ኪሎ ሜትሮችን የሚሸፍን ከ2000 ዓ.ም. በፊት በእኛ ገበሬዎች እጅ የነበረ መሬት አሁን እዚህ የለም፡፡ ሕዝቡም በሥጋት ሌሎች የተረፉ ድንበር ላይ ያሉ አረብኛ ሥያሜ የነበራቸውን ቦታዎች ሁሉ ወደ አማርኛ እየቀየራቸው ነው፡፡ ለምሳሌ ያክል ቀድሞ ‹ኮር ኹመር› ትባል የነበረችው ትንሽ መንደር አሁን ‹ጠፈረ ወርቅ› ተብላለች፡፡

አሁን የባሻ ጥጋቡን ጉዳይ እናንሳ፡፡ ባሻ ጥጋቡ በሱዳን የገዳሪፍ ግዛት ስሙ የናኘ ነበር፡፡ ባሻ ጥጋቡ ለተበደለ ሰው የሚቆምና በኃይለኛነቱ የሚፈራ የራሱ ሚሊሻዎች የነበሩት አንድ ግለሰብ ነው፡፡ እንዲያውም ሱዳኖች ‹ባሻ ጥጋቡ ይቅር እንጅ መለስስ ይመጣ› ይሉ እንደነበር ይወራል፡፡ ድፍን አርማጭሆ ፍትሕ ሲጎድልበት የሚያመለክተው ለምዕራብ አርማጭሆ ፖሊስ አሊያም አስተዳደር ጽ/ቤት አልነበረም፤ ለባሻ ጥጋቡ እንጅ፡፡ ባሻ ጥጋቡ በደል ያደረሰውን ሰው ወዲያውኑ እንዲያስተካከል የፍትሕ ርትእትን ያስጠብቃል፡፡ የሱዳን መንግሥት ለም የሆነውን የአርማጭሆ መሬት በወሰደ ጊዜ የባሻ ጥጋቡን መሬት ማንም ሊደፍረው አልቻለም፡፡ እንደሚባለው የባሻን መሬት አልፈው ሱዳኖች ወደ መሐል ሲገቡ መካከል ላይ የባሻ መሬት ይገኛል፡፡ ሆኖም ሰው ሆኖ ከሞት የሚያመልጥ የለምና ይህ ጀግና በ2005 ዓ.ም. ታሞ ከዚህ ዓለም ተለየ (እርግጥ ነው ለሕክምና አዲስ አበባ በሔደበት ወቅት ሆን ተብሎ ተገድሏል የሚባል ሐሜትም አለ)፡፡

የባሻ ጥጋቡ ተዝካር እለት አንድም የአርማጭሆ ሰው አልተጠራም፤ ነገር ግን አንድም የአርማጭሆ ሰው የቀረ የለም፡፡ ሕዝቡ አዘነ፤ ተዝካሩን ተረባርቦ አወጣ፡፡ የባሻ ጥጋቡን መሞት የሰሙ ሱዳናውያን የባሻን የእርሻ መሬት ለመቀማት ካምፑን ወረሩት፡፡ በዚህ ጊዜ የሚገርም ነገር ተከሰተ፡፡ አንዲት መነኩሴ ቆቧን ጥላ ክለሽ አንግባ ‹‹ገና ለገና ባሻ ሞቷል ተብሎ ርስቱ ሊደፈር ነው?›› በማለት ለጦርነት ሔደች፡፡

አብራጂራ የነበረውን የመለስ ቢል ቦርድ የአርማጭሆ ሰው አውርዶ በምትኩ ‹‹ባሻ ጥጋቡ ሆይ ራዕይህን እናስቀጥላለን!› የሚል ጥቅስ ጽፎ ሰቀለበት፡፡ ይህ ተረት ተረት ሳይሆን ትናንት የተፈጸመ እውነታ ነው፡፡

ከአርማጭሆ ወደ ጎንደር እየተመለስኩ ነው፡፡

የሚቀጥል…

በቋራ ያሉ የናይጄሪያ ዘላኖችና ‹ሸውሽዌ› ክፍል ፪

By Muluken Tesfaw

በቋራ ያሉ የናይጄሪያ ዘላኖችና ‹ሸውሽዌ›

ክፍል ፪

በዚህ በርሃና ጫካ ብዙ ገራሚ ነገሮች አሉ፡፡ መንደሮች በድንገት በሚነሳ ቋያ ሙሉ በሙሉ ይድማሉ፡፡ በርሜልን ጨምሮ ብዙዎቹ የሰፈራ መንደሮች በበርሃ ቋያ በየጊዜው እየወደሙ እንደገና ይሰራሉ፡፡ የበርሃ ሰው ተስፋ አይቆርጥም፤ ነገ በቋያ ቤቱ እንደሚወድምበት እያወቀ እንደገና ይገነባል፤ ይቃጠልበታል፤ ይሰራል…

በየመንገዱ ጅራታቸው የውሻ ያክል የረዘመ በጎች በብዛት አሉ፡፡ እነዚህ በጎች ‹ፈላታ› በመባል ይታወቃሉ፡፡ ፈላታዎች የናይጀሪያ ዘላኖች በጎች ናቸው፡፡ በጎቹ በዘላኖቹ ስም ፈላታ እየተባሉ ይጠራሉ፡፡ የናይጀሪያ ዘላኖች የሱዳንና የቻድን መሬት አልፈው ለምን ቋራ እንደከተሙ ለኔ ብዙ እንቆቅልሽ ነው፡፡ ነገር ግን ቋረኞች እንደሚሉት በቋራ ጫካዎች ውስጥ ፈላታዎች ከብቶቻቸውንና በጎቻቸውን ያረባሉ፡፡ እርግጥ ነው አካባቢው የግጦሽ ሳርና ውኃ ችግር ስለሌለበት ለከበት አርቢዎች ምቹ ቦታ ነው፡፡ የፈላታ ከብቶች አውሬዎች ናቸው፡፡ አበሻ ካዩ አባርረው ይዋጋሉ፡፡ ብዙ ግዜ አበሻዎች ከዛፍ ካልወጡ በስተቀር አያመልጧቸውም፡፡ ነገር ግን አበሾች የፈለታዎችን ከብቶች በጥይት በመምታት እንደሚወስዱባቸው ሰምቻለሁ፡፡ የፈላታ በጎች ተራብተው በድፍን ቋራና መተማ በብዛት አሉ፡፡ መልካቸው ነጫጭ ሲሆን ጸጉር የላቸውም፡፡ ጅራታቸው ረጅም ነው፡፡ ሥጋቸው ቆንጆ ነው ሲሉ ሰምቻለሁ፡፡ እርግጥ ነው የሔድኩበት ቀን አርብ በመሆኑ የበግ ሥጋ አልበላሁም፡፡

ወደ ጫካ አንድ ሰው ጂፒኤስ ሳይዝ ከሔደ የመጥፋት እድሉ ከፍተኛ ነው፡፡ በተለይ ደግሞ አዲስ የመጣ የመንግሥት ተቀጣሪ ከሆነ መስክ ብቻውን መሔድ የለበትም ይላሉ፡፡ ወደ ጫካው ከሔደ በኋላ በርሃው ሕሊናውን ያነሆልለዋል፡፡ በበርሃ ሕሊናን የመሳት ሒደት ‹ሽውሽዌ› ይባላል፡፡ ሽውሽዌ የያዘው ሰው አቅሉን ስቶ ከመጓዝ ውጭ ወደየትና እንዴት እንደሚሔድ አያውቅም፡፡ በዚህ በርካታ ሰዎች ጠፍተው ቀርተዋል አሉ፡፡ ‹አሉ› የምለው ሰዎች በነገሩኝ መሠረት ስለምነግራችሁ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ይህች ሽሽዌ የምትባል ‹ነገር› አንዳች መለኮታዊ ነገር ይኑራት አይኑራት የሚታወቅ ነገር ያለ አይመስለኝም፡፡ እርግጥ ብዙ ሰዎች እንደ ሰይጣናዊ ሥራ የሚቆጥሩት አሉ፡፡ አንዳንዶች ደግሞ የአየር ንብረቱ ሞቃታማ መሆን የሰውነታችን ሥነ ሕይወታዊ (ፊዚዎሎጅካል) ሥራ ስለሚያወከው አእምሯችን በአግባቡ ሥራውን ማከናወን ያቅተዋል፡፡ በዚህም አቅጣጫ የመለየት ችግር ይገጥመናል የሚሉ አሉ፡፡ ነገር ግን የትኛው ትክክል እንደሆነ የተሰራ ጥናት አላየሁም፡፡ አቅጣጫ ሲጠፋ በአካባቢው የሚኖሩት ጉምዞች አቅጣጫን ለማወቅ የሚሆናቸው የለም፡፡ አንድ ጊዜ እንዲህ ሆነ አሉ፡፡ አንዲት ግብርና ተመድባ የመጣች ሴት ወደ ጫካው የገጠር አካባቢ ትሔዳለች፡፡ ብዙ እንደተጓዘችም ሽውሽዌ ትይዛታለች፡፡ ያኔ ወደየት እንደምትሔድ ሳታውቅ ብዙ ከገለጎ (የወረዳው ከተማ) ርቃ ሒዳለች፡፡ በዚህም ከፈላታዎች እጅ ትገባለች፡፡ እንደነገሩኝ ከሆነ ይህች ልጅ ፈላታዎችን አግብታ እርሷም ዘላን ሆና በመኖር ላይ ነች፡፡

ፈላታዎች ሴቶችን ጠልፈው ወይም ሽውሽዌ ከወሰደላቸው መቼም አይለቁም፡፡ በዚህ የተነሳ ይህች ሴት አንዳንዴ ለዘመዶቿ ደብዳቤ ከመጻፍ የዘለለ ከጫካ ውጭ ያለውን ዓለም በሽውሽዌ ከተጠለፈችበት ጊዜ ጀምሮ አይታው አታውቅም፡፡ ለማምለጥ ብትሞክር በፈላታዎች ጥቃት ስለሚደርስባት አስባም የምታውቅ አይመስልም፡፡ ፈላታዎች ብዙም ልብስ መልበስ የለመዱ አይደሉም፡፡ በሬዎቻቸውም ሆነ እነርሱ የማሽተት ኃይላቸው ከፍተኛ እንደሆነ ይነገራል፡፡ አደጋ ከመጣባቸው አሊያም አበሻ እየቀረባቸው መሆኑን ከብዙ ኪሎ ሜትሮች ርቀት አውቀው ይርቃሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች አእዋፍም የሚታዘዟቸው ይመስላል፡፡ ወደ እነርሱ እየቀረበ ያለው ሰው ይሁን ሌላ አንበሳ ሁሉንም አእዋፍ ሊነግሯቸው እንደሚችል የወሬ ምንጮቼ ያረጋግጣሉ፡፡

የአካባቢውን ማኅበረሰብ ወባ፣ እባብና ሽውሸዌ ያጠቁታል፡፡ መርዛማ የበርሃ እባብ አለ፡፡ በእጽ የሚከላከሉት ሰዎችም አሉ፡፡ እርግጥ እባብ የሚከላከሉበት እጽ ከሱዳን አስማተኞች የተገኘ ነው አሉ፡፡ አዲስ አበባ እባብ ስለሌለ ጥበቡን ማወቅ እንጅ እጹን አልፈለግኩትም፡፡ ስለዚህ ይዤ አልተመለስኩም፡፡ ጥበቡንም አልቀሰምኩም፡፡ ደሞስ መሥራት አለመሥራቱን ሳላረጋግጥ እንደኔ ዓይነት ቶማስ (ተጠራጣሪ) እንዴት ይዞ ይመጣል? ሽውሽዌ ብዙ ሰው ታጠቃለች፡፡ አንድ ጊዜም እንዲሁ ከቋራ ወረዳ ወደ ገጠር የተላኩ አምስት ያክል ባለሙያዎች በሽውሽዌ ይጠቃሉ፡፡ ሕሊናቸው ነሁልሎ የሚሔዱበትን አቅጣጫ ሳቱ፡፡ ሽውሽዌ የተጠቃ ሰው ያለ አቅጣጫው ኃይሉ እስከሚያልቅ ድረስ መጓዝ ነው፡፡ የእነዚህ ባለሙያዎች ኃይል አልቆ ኖሮ ወደቁ፡፡ ወዳጆቻቸው ለመፈለግ ሞከሩ፡፡ ሊገኙ አልቻሉም፡፡ ከረጅም ጊዜ በኋላ ለሌላ መስክ (ፊልድ) የተላኩ ሰዎች በርሃ ውስጥ ወዳድቀው በክረምት ዝናብ ሣር በቅሎባቸው ተገኘ አሉ፡፡ እንግዲህ ስለ ሸውሸዌና ፈላታ ናይጀሪያውያን ካላይ ያወጋሁት በሙሉ በቋረኞች በተነገረኝ መሠረት እንጅ ከፈለታ በግ ውጭ ያየሁት አንድም ነገር የለም፡፡ እርግጥ ነው ሁሉምን ለማየት አይቻለም፡፡ ደግሞም አደገኞች ናቸው፡፡ ሽውሽዌን ልይ ብል ተመልሦ ይህን ሪፖርት ማን ያስነብባችኋል? ዘላኖቹንም ማግኘት ሌላው ከባድ ነገር ነው፤ ደግሞም የሚመጡበት ወቅት አላቸው እንጅ ዓመቱን በሙሉ አይኖሩም፡፡ እባብ እንኳን በእውን በናሽናል ጂኦግራፊ ሳየውም ውቃቢየ አይወደው፡፡ በወባ ለመለከፍ አንድ ቀን ማደር ይጠበቅብኛል፡፡ ሁሉንም ግን አልሻም፡፡ የሔድኩባት ፒክ አፕ ወደ ሸኽዲ ትመለሳች፡፡

ጊዜ ቢኖረኝ ኖሮ ብዙ ነገር የሚታይ ነበር፡፡ ወደ ደጋማው የቋራ አካባቢ ቴዎድሮስ ከተማ የሚባል አለ፡፡ እዚያ የአጼ ቴዎድሮስ የልጅ ልጆችና ዘሮች እንዳሉ ሰምቻለሁ፡፡ እነርሱን የማግኘት እቅድ ነበረኝ፡፡ ጊዜም ገንዘብም ስለተመናመነ ብሎም ቀጣይ ጉዞ ስላለብኝ ያን በርሃ ትቼው መመለስ ግድ ይላል፡፡ ወጣሁም፡፡ ሸኽዲ ከተማ ባጃጅ ውስጥ ያነበብኩት ጥቅስ ለአካባቢ ምቹ (ኢንቫሮንመንት ፍሬንድሊ) ነው፡፡ እንደ አዲስ አበባ ‹የሰው ትርፍ የለውም› የሚል ጥቅስ እዚህ ቦታ አይታሰብም፡፡ ትርፍ አትጫን የሚል ሕግ የለምና፡፡ ባጃጅ ውስጥ ያለው ጥቅስ ‹ጊዜን አይቶ የማይከዳ ዕውነተኛ ጓደኛ የበርሃ ጥላ ነው› ይላል፡፡ ከዚህ የበለጠ ዕውነት በዚህ አካባቢ የለም፡፡ ቀን ላይ አይቸዋለሁና፡፡

አሁን እየመሸ ነው፡፡ ጀምበር መዘቅዘቅ ጀምራለች፡፡ ወደ ጎንደር የሚሔዱ መኪናዎችም ብዙ የሉም፡፡ ወደፊት 161 ኪሎ ሜትር መጓዝ ይጠበቅብኛል፡፡ ያገኘዋት ሚኒ ባስ በዚያ ሙቀት ሰው ጥቅጥቅ አድርጋ ሞላች፡፡ ጋቢና ነበርኩ፡፡ ጋቢና ሾፌሩን ሳይጨምር ሦስተኛ ሰው ታከለልን፡፡ አይሆንም ማለት አይቻልም፡፡ ዝም ብሎ መጓዝ ነው፡፡ ገንዳ ውኃን አለፈን፤ ደረቅ አባይ፤ ነጋዴ ባህር፤ አርሴማ፣ ሰራባ፣ ጭልጋ…. ጎንደር ምሽት ሦስት ሠዓት ሲሆን፡፡ ነገ ቀጣይ ጉዞ አለ፡፡ ወደ አርማጭሆ፡፡

በላንድ ማርክ ሆቴል የተደረገው የወልቃይት ጉዳይ ስብሰባ

የአርማጭሆን ጉዞ ከመጀመራችን በፊት ግን ትናንት በጎንደር ላንድ ማርክ ሆቴል ስለነበረው የወልቃይት ጠገዴ የአማራ ብሔርተኝነት የማንነት ጥያቄ ስብሰባ የታዘብኩት ማስቀመጥ እሻለሁ፡፡ ሐሙስ እለት ላንድ ማርክ ሆቴል ስደርስ የእቴጌ ምንትዋብ የስብሰባ አዳራሽ ሞልቶ መፈናፈኛ አልነበረውም፡፡ ውስጥ ገብቼ አንዳንድ ነገሮችን ሪከርድ ለማድረግ ብሞክርም መሹለኪያ መንገድ ጠፋ፡፡ ስለዚህ የነበረኝ አማራጭ ውጭ ላይ ሆኖ በሞንታርቦው የሚነገረውን ማዳመጥ ነበር፡፡ ስብሰባውን የአዘጋጁት የጎንደርና የዳባት አገር ሽማግሌዎች ናቸው፡፡ ወልቃይት ቀድም ባሉት ጊዜያት የቆላ ወገራ አካል ሆኖ አውራጃው ዳባት ነበር፡፡ በዚህም ይመስላል የዳባት የአገር ሽማግሌዎች ከጎንደር ከተማ ጋር በመቀናጀት ስብሰባውን የአዘጋጁት፡፡ ኮሚቴዎቹ የደረሱበትና እየገጠማቸው ያለውን ነገር ሲያስረዱ ሕዝቡ ላይ የቁጭት፣ የንዴትና የተስፋ ስሜቶች ተደባልቀው ይነበቡ ነበር፡፡ በዚሁ ሰሞን በወልቃይት፣ በጠገዴና በኹመራ አካባቢዎች ለሠፈራ ከመጡት የትግራይ ተወላጆች በተጨማሪ በመኪና እየተጫኑ እየመጡ ‹‹ያልተመለሰ የማንነት ጥያቄ የለንም፤ ጸረ ሰላም ኃይሎችን አንታገስም…›› ወዘተ የሚሉ የማወናበጃና የማስፈራሪያ መፈክሮች በሰፊው የመንግሥት መገናኛ ብዙሃን ሽፋን ሰጥተዋቸው ሲስተናገዱ ሰንብተው ነበር፡፡ ነገር ግን የአማራ ተወላጆች ነን ላሉት እንኳንስ ሰላማዊ ሰልፍ ሊፈቀድ ቀርቶ የቤት ውስጥ ስብሰባም ተከልክለዋል፤ አማርኛ ሙዚቃ እንዳያደምጡ ተደርገዋል፡፡ አልፎም ወደ አገራቸው ለመሔድ ኬላዎችን ተሸለክልከው ነው፡፡

የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ ከሆኑት መካከል ኮሎኔል ደመቀ የሚባሉት ይህን አስመልክተው ሲናገሩ ‹‹የእነርሱን ትግሬነት እኛ አልካድንም፤ እኛ የምንለው የእኛም አማራነት ይታወቅ ነው፡፡ አማራ የሆነ ሰው እንዴት በግዴታ ትግሬ ሊሆን ይችላል? በግዴታ እንዴት ማንነት ሊሰጠን ይችላል? እኛ እኮ በትግርኛ መርዶ ሰምተን በአማርኛ የምናለቅስ ነን፤ በትግርኛ የሰርግ ጥሪ ተላልፎልን በአማርኛ የምንዘፍን ሕዝብ ነን፡፡ ሕወሓት ጭቆና ወደ ጫካ አስወጣኝ ብሎ እኛ ላይ ያልፈጸመው በደል የለም፡፡ አማራ ነን ብሎ መናገር ምንድን ነው ጸረ ሰላም የሚያስብለው? ጠመንጃ መያዝ ለወልቃይት ሕዝብ ተራ በጣም ተራ ነገር ነው፡፡ ሆኖም ይህ የሚጠቅም ነገር ስላልሆነ በሕገ መንግሥቱና በሰላማዊ መንገድ ብቻ ጥያቄያችን እየቀርብን ነው፡፡ ይህ ጥያቄ የወልቃይት ብቻ ሳይሆን የመላው አማራ ነው፡፡ በእኛ ላይ የሚደርሰውን ግፍ ለማውገዝ የግድ አማራ መሆን አይጠበቅም፡፡ ትግሬዎች ራሳቸው ሕወሓትን በቃህ ሊሉት ይገባል›› በማለት በሰፊው አብራሩ፡፡ አቶ አታላይ ዛፌ የተባሉም በወልቃይት ሕዝብ በተለይ ደግሞ በሱዳን ወታደሮች እየተወሰዱ ስላለቁት የአማራ ወጣቶች፣ በሕወሓት ባለሥልጣናት ስለተደፈሩት ሴቶችና ተማሪዎች፣ ግሕንብ የምድር እስር ቤት ውስጥ ስላለቁት ወልቃይቴዎች በሰፊው ሲዘረዝሩ አንዳንዶች ያለቅሳሉ፤ ሌሎች ደግሞ ያጨበጭቡ ነበር፡፡ ፍጹም ድብልቅልቅ ያለ ስሜት፤ በቃ ደስታና ሀዘን፣ ተስፋና ተስፋ መቁረጥ፣ የዋህነትና በቀል፣ የአንድነትና የልዩነት…. ስሜቶች በአንድ ሰው ገላ ላይ ሳይታዩ አልቀረም፡፡

አንድ ስሙን ሳልሰመው ያለፈኝ የወልቃይት ተወላጅ ሁለቱን ወንድሞቹን የሕወሓት የጸጥታ ቡድኖች ወስደው እንዴት አሰቃይተው እንደገደሉበት ምስክርነቱን ሊሰጥ ማይክራፎኑን (የድምጽ ማጉያውን) ተቀበለ፡፡ ግን አልቻለም፡፡ ምንም እንኳ ግፉ የተፈጸመው ከዐሥር ዓመታት በፊት ቢሆንም አሁንም ድረስ በሐዘኑ ልቦናው እንደተሰበረ ነው፡፡ ሊናገር ሲል ትናገው መከፈት አልቻለም፡፡ በዐይኑ እንባ ፈሰሰ፡፡ ድምጹ ተቆራረጠ፡፡ ብዙ በጣም ብዙ በስብሰባው የነበሩ ሰዎች ዝም ብለው ማዳመጥ አልቻሉም፡፡ የሰዎች ኪስ ሲንኮሻኮሽ ይሰማል፡፡ ሶፍት ወይም ማኅረም ፍለጋ ነበር፡፡ የዛሬ ዐሥር ዓመት የተገደሉ ሰዎች ዛሬ መርዶአቸው የተረዳ መሠለኝ፡፡ ወንድ ልጅ ሲያለቅስ ማየት አልወድም፡፡ ቀረጻ ላይ ነበርኩ፡፡ እንባየ ተናነቀኝ፤ ታገልኩት፤ አልቻልኩም ፈሠሠ፡፡

ግለሰቡ ወንድሞቹን ከእናታቸው ነጥለው ወስደው አሰቃይተው ገድለውበታል፡፡ እርሱም አገር አለኝ ብሎ ተመልሶ አያውቅም፡፡ እንኳን ወልቃይት ሊሔድ ቀርቶ ጎንደር ኹመራ መውጫን ወለቃን አልፎ አያውቅም፡፡ በሐዘን የተሰበረ ልብ ይገርማል፡፡ በወልቃይት ሕዝብ ላይ ሕወሓት የፈጸመው ግፍ በቀላሉ ተነግሮ እንደማያልቅ ለመረዳት ችያለሁ፡፡ ሰዎች ተገድለው በአዲ ረመጥ ከተማ በመኪና ላይ ተጭነው ለሕዝብ መቀጣጫ እንዲሆኑ እንደ ደርግ የቀይ ሽብር ሰለባዎች በዚህ ዘመን የተፈጸመው ከወልቃይት ሕዝብ ውጭ የትም አይኖርም፡፡ አማራ በግዴታ ወደ ትግሬነት የተቀየረው ከወልቃይት ሕዝብ ውጭ በአገራችንም በዓለማችንም አይኖርም፡፡ እውነታው ይሔ ነው፡፡ ከሌሎች የአማራ ክልል አካባቢዎች እኛም ጋ መጥታችሁ ጉዳዩን አስረዱን የሚሉ ጥያቄዎች ብዙ ነበሩ፡፡

ጎንደር ስሔድ ምሽት ላይ ብዙ ጊዜ ወደ አጼ በካፋ የባህል ምሽት ማዝገሜን አልተውም፡፡ ጥሎብኝ የዚህ የባህል ምሽት እወደዋለሁ፡፡ የዛሬው አካሔዴ ግን ለመዝናናት እንዳልሆነ ብናገር ተአማኒነት ስለማይኖረው ብዙም ምክንያት ማቅረብ አልሻም፡፡ ብዙ ዜጎቻችን በርሃብ ጠኔ የሚበሉትን አጥተው እየተቸገሩ እንደሆነ አውቃለሁ፡፡ ይህንንም አይቻለሁ፡፡ በሰፊው ወደፊት ስለምሔድበት አሁን አልቀላቅልም፡፡ ቀን ላይ በወልቃይቶች ላይ የደረሰውን ስሰማ በእውነቱ እድሜ ልኬን በሐዘን የምኖርም መስሎኝ ነበር፡፡ ነገር ግን የሰው ልጅ ጠንካራ ፍጥረት ነውና የሐዘን ብዛት አጥንቱን አይሰብረውም፤ የመደሰቻ ሕዋሳቱን አያደነዝዝም እንጅ ትንሽ ብቻ በቂ ነበር፡፡ የሆነው ሆኖ አዝማሪ ምን አለ ለማለት ነበር የገባሁት፡፡

ተንኮለኛው ጋዜጠኛ ተስፋየ ገብረ አብ አንድ ጊዜ ጎንደር ሒጄ ሰማሁት ያላቸውን የአዝማሪ ግጥሞች አስታወስኩ፡፡

ጎንደር አገር ጠፍቶ ሲፈለግ ሌሊት

ቀን ታዲሱ ጋራ ሲሔድ አየሁት፤

በረከት አገሩ ስለናፈቀው

ዳሸን አናት ሆኖ አስመራን አየሁ፡፡

እነዚህን ግጥሞች ጎንደር በሔድኩ ቁጥር አዝማሪ ለአዝማሪ ቤት እየዞርኩ ልሰማቸው ፈልጌ አልተሳካልኝም፡፡ ግን የጎንደር አዝማሪ ከእነዚህ በላይ የግጥም ቅኔዎች ማሽሞንሞን ይችላል፡፡ ለምሳሌ ይህን ግጥም በሕሊናችሁ በማሲንቆ አጃቢነትና በመረዋ የቡርቧክስ አዝማሪ ድምጽ ስሙት (ቡርቧክስ ከጎንደር ከተማ 40 ኪሎ ሜትር ያክል የሚርቅ ማክሰኝት የምትሰኝ ከተማ ወደ በለሳ መውጫ በኩል ያለ የገጠር ቀበሌ ሲሆን የበርካታ አዝማሪዎች ቀዬ ነው)፡፡

ኧረ አገሬ ጎንደር ሸንበቆው ማማሩ፣

አገሬ ወስከንቢት ሸንበቆው ማማሩ፤

ኧረ አገሬ ቋራ፣ መተማ አርማጭሆ ሸንበቆው ማማሩ

አገሬ ወልቃይት፣ ቃፍታና ኹመራ ሸንበቆው ማማሩ፣

ቆርጠው ቆርጠው ጣሉት ለም-አገር እያሉ!

አዝማሪው አገሩን በሸንበቆ መስሎ ለም ለም የሆነው ሁሉ ተቆርጦ አንድም ለሱዳን አሊያም ለታላቋ የትግራይ ሪፐብሊክ ምስረታ መወሰዱን በቁጭት ነው በቅኔ የሚገልጸው፡፡ የሆነው ሆኖ በዚያ ቀን አብዛኛው በበካፋ የባህል ቤት ሲዘፈን ያመሸው ስለወልቃይት ነው፡፡ አንድ ራሰ በራ ድምጸ መረዋ አዝማሪ አለ፡፡ የድምጹ ነገር ወፍ ከሰማይ ያወርዳል፤ ወይንም በአገራችን አባባል ነብር ይጠራል፡፡ የፋሲል ደመወዝን ‹‹አረሱት መተማ፣ አረሱት ኹመራን የውም የእኛን እጣ፣ እነርሱ ምን ያርጉ ከእኛ ሰው ሲታጣ›› ያለ ጊዜ የምድር ቤት ውስጥ ያለው አዳራሽ በጩኸት ተናወጠ፡፡ መቼም በጩኸት ከኢያሪኮ ከተማ ውጭ የፈረሰ ግንብ አልሰማሁም እንጅ ያን እለት የነበረው ጩኸት ከዚህ ላይ ለመግለጽ ቃላት መፈለግ ግድ ይለኛል፡፡

አዝማሪው ያዘምራል፡፡ እንዲህ በማለት

ኧረ አገሬ ጎንደር ሰሜን ጃናሞራ ወልቃይት ጠገዴ፣

ለራበው እንጀራ ለጠገበው ጓንዴ!

ወደ መድረክ ሰው ሁሉ መቶ ብር መወርወር ጀመረ፡፡ በዚያ ምሽት ቤቱን አይቶ የማያውቅ እንግዳ ሰው ቢገባ የቤቱ ሕግ መስሎት መቶ ብር እንደሚወረውር በእርግጠኛነት መናገር እችላለሁ፡፡ መድረክ አካበቢ ወደ አዝማሪው ስመለከት ውር ውር የሚሉ አረንጓዴ ቢራቢሮዎች ባለማሲንቆውን ሸፍነውታል፡፡ አዎ ቢራቢሮዎች አይደሉም፤ የባለ መቶ ብር ኖቶች እንጅ፡፡ ከዚህ ቤት ውስጥ የታመቀ ብሶት ፈንድቷል፡፡ የተጠራቀመ ቁጭት ፈሷል፡፡ ወጣቱ ደሙ ፈልቷል፡፡ ባርነትን በቃህ የሚል ይመስላል፡፡ ማንም ይህን የተናገረ የለም፤ እኔ ግን እያንዳንዱ ሰው ፊት ላይ ያለውን ስሜት አንብቤዋለሁ፡፡ ሊመርጅ የገባው የደህነንቱም ሰው ስሜት ቢሆንም!!

እስኪ አንድ ሰው እስክስታ እየመታ ሲያነባ፣ ግማሽ ፊቱ የብርሃን ጸዳል ወርሶት ግማሹ ግን የዳመነ ሲሆን፣ ውስጡን በነገር ሞልቶ መተንፈስ አልችል ሲል፣ ሁለት ፍጹም ተቃራኒ ስሜቶች በአካላቱ ላይ ሲነበቡበት ያያችሁት ሰው አለ? ወይስ ይህ ስሜት ገጥሟችሁ ያውቃል? እኔ በዚያ ቤት ውስጥና በዚያ ሰዓት ያየሁት ግን ይህ ነው፡፡ ቤቱን ሁለት ፍጹም ተቃራኒ መናፍስት ወርሰውት አምሽተዋል፡፡

የሚቀጥል