ለሱዳን ሊሰጥ ነው ስለተባለው መሬት : ጆሮ ያለው ይስማ ልብ የአለው ልብ ይበል!

By historian   Fikre Tolossa

ለሱዳን ሊሰጥ ነው ስለተባለው መሬት
—————————————————-

eprdf berber

አሁን በጎንደር አና በቤንሻንጉል አካባቢ የሜገኙት የእነ ኦሜድላና ጋምቤላ መሬቶች በአውነት የማን ናቸው? ያለጥርጥር የኢትዮጵያ ናቸው። ለምን እንደዚህ እንዳልኩ ዝቅ ብዬ አስረዳለሁ። መሬቶቹ በታሪክ የሱዳን ነበሩና ለሱዳን ይሰጡ የሚሉት የኢትዮጵያ ባለስልጣናት መሬቶቹን ለሱዳን ለመስጠት የሚያቀርቡት ምክንያት “በ በሱዳን የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ጊዜ የእንግሊዝ መንግሥት ተወካይ የሆነ አንድ ሻለቃ የወሰን ምልክቱን የተከለው እዛ አካባቢ ነው፤ቀድሞ አፄ ምንይልክ በዚህ ተስማምተው፥ በሁዋላ ደግሞ አፄ ኅይለሥላሴ እና ደርግም ይህን አፅድቀውታል፤” የሚል ነው። በሌላ አነጋገር፥ በታሪካዊ ምክንያት ነው። እዚህ ላይ አንድ አስቂኝ ታሪክ ታወሰኝ። አንድ እንግሊዛዊ ከሱዳን የኢትዮጵያን ድንበር ተሻግሮ የዱር እንስሳና አውሬ ለማደን በሚል ፈሊጥ ሲዘዋወር ለስለላ ነው ብለው በጠረጠሩት የሃገሬው ተወላጆች ተገሎ እዛው ተቀበረ። ታዲያ ይህን ሰበብ አድርጎ አንድ እንግሊዛዊ መኮንን (ምናልባትም እላይ የተጠቀስው እብድ ሻለቃ) ያ አካባቢ በሞላ ለእንግሊዝ መንግሥት ሊሰጥ ይገባል፤አለ። በምን ሂሳብ ተብሎ በአባ መላ (ፊታውራሪሃብተጊዮርጊስ ዲነግዴ) ተጠየቀ። አንድ የእንግሊዝ ዜጋ ሞቶ እዚህ ስለተቀበረ፤ሲል መለሰ። አባ መላም ከትከት ብለው ስቀው፥እሺ ደግ ነው፤አንድ የእንግሊዝ ዜጋ ሞቶ እዚህ ስለተቀበረ ይሄን ሁሉ መሬት ለናንተ እንሰጣችሁአለን። የአፄ ቴዎድሮስ ልጅ ልዑል ዓለማየሁ ለንደን ውስጥ ሞቶ እዛው ለንደን (ዌስትሚኒስትር አቢ) ስለተቀበረ እኛ ደግሞ ለንደንን እንረከባችሁአለን። በዚህ ከተስማማህ ውል መፈራረም እንችላለን፤ብለው አሾፉበት። ከዛ ቦታ በቅፅበት ዳብዛው ጠፋ። ስለታሪክ ካወሳን ዘንድ፥ ይሄ ዛሬ ሱዳን የተባለው ምድር ሁሉ ቢያንስ ለ 4000 ዓመታት ያህል የኢትዮጵያ ግዛት ነበር።ጥንት የሚታወቀው ኑብያ ተብሎ ነበር። ኖባ በተሰኘው የኩሽ ዘር ስም።መናገሻውም መርዌ ነበር። የዛሬ 2900 ዓመት ግን ሱዳን ይባል ጀመር። ይህ ስም የወረደው ከአፄ አክሱማይት እናት ከንግሥት ሳዶንያ ነው። እሱ በህፃንነቱ የግብፅ ፈርኦን ሆኖ እስከሚያድግ ድረስ እስዋ በ 350,000 የአማራ ሰራዊት ታጅባ ዙፋኑን እየጠበቀች በሱ ስም ግብፅን፥ ሊብያን እና የዛሬውን ሱዳን ታስተዳድር ነበር። በዚህ ምክንያት፥ ከሳሃራ በርሃ በታች የአለው ምድር በሞላ ሳዶንያ ተባለ። ቀስ በቀስ ደግሞ ሱዳን። እንዳውም ኑብያ ውስጥ የነበረው መርዌ ለዛ አካባቢ እንደ ዋና ከተማ ሆኖ ያገለግል ነበር። ቢያንስ 14 የኢትዮጵያ ሴቶች ህንደኬ በሚል ማእረግ በንግሥትነት በተከታታይ ዛሬ ሱዳን፤ ግብፅና ሊብያ የሚባሉትን ሃገሮች ለ 1000 ዐመት ያህል ገዝተዋል። ለመጨረሻ ጊዜ የኑብያ ንጉሥ የነበሩት በ 16ኛው ክፍለ ዘመን የኖሩት አፄ ፋሲል ነበሩ። ከኑብያ ብቻ ሳይሆን ከስናር (ከካርቱምብዙያልራቀ ስፍራ) ድረስ የወርቅ ግብር ይመጣላቸው ስለነበር አዝማሪ አንዲህ ሲል የሱዳን ገዥነታቸውን አረጋግጦላቸው ነበር፤-

ጎንደር ቢያጉረመርም ፋሲል ፈረስህ ኑብያና ስናር ወርቁን ጫኑልህ፥ሳሩን ተጠየፈ የፋሲል ፈረሱ፥ ክምር የሱዳን ወርቅ ገፈራው ነው ለሱ።

“ገፈራ” ማለት የፈረስ ምግብ ነው። ዛሬ ፉርሽካ የምንለው ዐይነት። እንግዲህ ይህ ግጥም፥ ሱዳን አስከ የዛሬ 500 ዐመት የኢትዮጵያ ግዛት አንደነበረች ይመሰክራል። በሁዋላ በዘመነ መሳፍንት አና ከዛ ትንሽ ቀደም ብሎ ኢትዮጵያ አየተዳከመች ስትሄድ ቱርኮች ያዝዋት። ቱርኮች ተዳክመው ለእንግሊዝ ለቀቁላት። እንግዲህ ከእጅ የወጣ ሃገር በታሪክ ሰነድ ወይም ማረጋገጫ የሚመለስ ቢሆን ኖሮ፥ መላው ሱዳን ለኢትዮጵያ በተመለሰ ነበረ። ከላይ አንደ ተረዳነው ሱዳን የኢትዮጵያ እንጂ ኢትዮጵያ የሱዳን ሆና አታውቅም። ታዲያ በምን ምክንያት ነው አሁን የኢትዮጵያን መሬት የጠየቀችው? እስዋ አፍዋን ምን ቁርጥ አርጉዋት ጠየቀችና? እስዋ በራስዋ ተነሳስታ ደፍራ መሬት አለኝ አላለችም።

አሁን በአመራር ላይ የአሉት የኢትዮጵያ ባለስልጣናት ደርግን በሚዋጉበት ሰዐት ሱዳን ለዋለችላቸው ውለታ ወሮታውን ሊመልሱላትና አሁንም ተቀዋሚዎቻቸውን እንዳታስተናግድ የሚከፍሉዋት ዋጋ መሆኑ ነው። ወዲህም መሬቱ ያለው በአማራ፥በቤንሻንጉል፥ በጋምቤላና በአሮሞ ክልሎች ስለሆነ የእኛን ምድር ስለማይመለከት ችግር የለውም ዐይነት ነው። ብሄራዊ ስሜት የሚባል ነገር ስለሌለ። መሬት በነፃ እንካ ከተባለ ማን ይጠላል? ስለዚህ ሱዳኖቹ እየፈነጠዙ ሊወስዱ አኮብኩበዋል።አሁን ኢትዮጵያ ውስጥ ያለው መንግሥት 1600 ኪሎሜትር ለም መሬት ለሱዳን ይገባታል ብሎ ጠበቃ የቆመላት እላይ የተጠቀሰው ቅኝ-ገዢ መኮንን በቸከለው ድንበራዊ ችካል ክሆነና በእንግሊዝ ቅኝ ገዥነት አገር ቅርጫ አንዲሆን ከተፈቀደ፥ እንዲሁም እንግሊዝ ያቀናው መሬት ሁሉ ለሱዳን ይቸር ዘንድ ከተፈረደ፥ የቀድሞው የአንግሊዝ ቅኝ ግዛቶች የነበሩት እነ ዩጋንዳና ሱዳን፥ ካስፈለገም እነ ናይጀሪያ ሁሉ ለሱዳን መሰጠት ይገባቸዋል ማለት ነዋ!!! የሆነ ሆኖ፥ ያ ሆፈፌ ቅዥተኛ እንግሊዝ ምኞታዊ ህልም አልሞ የፈለገውን ያህል የወሰን ድንጋይ ቢተክልና አፄ ምኒልክም አልተስማሙም እንጂ ቢስማሙለትና መሬት ቆርሰው ቢሸልሙትም አንኩዋን ያ ውል የሞተ ነው። ለምን ቢባል፥ ሱዳንን ዐለምና የተባበሩት መንግሥታትም ያወቃትና በታሪኩዋ ለመጀመሪያ ጊዜ ራስዋን ችላ የራስዋን ባንዲራ ያውለበለብችበት ዳር ድንበር አሁን የአለው ነውና። እኤአ በ 1953 ዐመተ ምህረት እንግሊዝ ግዛቴ ይሄ ብቻ ነውና ያንቺም ግዛትሽ ይሄው ነው ብሎ በዐስር ጣቱ ፈርሞ የተወላት መሬት ነው። እሱውም ከመከፈልዋ በፊት የነበረው የቆዳ ስፋቱ 2,505,813 ስኩዌር ኪሎሜትር የሆነው ነው። ከመከፈልዋ በፊት ሱዳን በቆዳ ስፋት ከአፍሪካ አንደኛ ነበረች። አሁን ሶስተኛ ነች። አሁንም ከኢትዮጵያ ትልቃለች ማለት ነው። የያዘችው ይበቃት ነበር። የኢትዮጵያን መሬት ለግሰናት በደቡብ ሱዳን የተወሰደባትን መሬት እንተካላት ካልተባለ በቀር። ሰጭና ነሽው አንግሊዝ ከተደረገና የእንግሊዝ መንግሥት ለክቶ፥ “አበጥሮ”፤ “አንጥሮ” ሁሉን አጣርቶ ራሱ በመጨረሻ ያረጋገጠው የሱዳን ምድር እላይ የተጠቀሰው ስፋት ከሆነ በምን ሂሳብ ነው አንግሊዝም ሆነ የተባበሩት መንግሥታት የማያውቁትን የኢትዮጵያን መሬት በ ህቡዕ ለሱዳን የሚለገሳት? አይገባትም አንጂ በእርግጥ ሱዳን ይገባኛል የምትለው መሬት ከአላት ወደ ተባበሩት መንግሥታት ሄዳ ነው አንጂ አቤቱታዋን የምታቀርበው በስርቆሽ በር ነው እንዴ መሬት ቆርሳ የምትሮጠው? ወይንስ መሬቱን ከቦጨቀች በሁዋላ ወደ ተባበሩት መንግሥታት ቀርባ መርቁልኝ ልትል ይሆን? እስዋ ግን ወደ እዛ እስካሁን ያልሄደችው እኤአ በ 1953 እንግሊዝ ካስረከባት በቀር ሌላ መሬት ስለማይገባት “ወይጅ ወዲያ አትቀልጅ!” ይሉኛል፤ ብላ ፈርታ ነው። አለዛ ሱዳን ነፃ ከወጣች ጀምሮ መሪዎችዋ ከ ኢብራሂም አቡድ ጀምሮ እስከነ ኑሜሪ አና አሁን ያለውም አል በሺር የይገባኛሉን ጥያቄ ገና ድሮ ባቀረቡ ነበር። ሰብብ ፈጥረን ስለቀድሞ ውለታዋ እና ተቀዋሚዎቻችንን ስለምትገታልን እንዲሁ በነፃ እንቸራት ካልተባለ በቀር እንደ እውነቱ ከሆነስ ሱዳን፥ “ኢትዮጵያ ያዘችብኝ፥ ይገባኛል፤” የምትለው አንዲት ስንዝር መሬት የላትም። ከቅኝ ግዛት ነፃ ከወጡ በሁዋላ የአፍሪካ ሀገራት በሞላ የያዙት ድንበርና ወሰን የቅኝ ገዥዎችቸው አነዚህ ናቸው፤ ብለው ያረጋገጡላቸውን ብቻ ናቸው። ስለዚህ ሱዳን ከሌሎቹ የአፍሪካ ሃገራት በምንም አትለይም። በመሆኑም ከኢትዮጵያ ልቀበል ይገባኛል ልትል የሚያስችላት ኢትዮጵያ ውስጥ አንድ ጥሪኝ አፈር የላትም። ስለ ኦሜድላ ብቻ እንኩዋን ብንዘክር፥ አፄ ኅይለሥላሴ በሱዳን በኩል ከስደታቸው ሲመለሱ ከ 5 ዐመታት በሁዋላ ለመጀመሪይ ጊዜ የኢትዮጵያን ሰንደቅአላማ ሰቅለው የአውለበለቡት ኦሜድላ ላይ ነበር። ይህን በሚያደርጉበት ጊዜም የ እንግሊዝ የቅኝ ገዢ ትልቅ ባለስልጣናት ለ ሰንደቅአላማዋ አክብሮት በተጠንቀቅ ቆመው መሬቱ የኢትዮጵያ መሆኑን ተቀብለው ይመለከት ነበር እንጂ “የሱዳን መሬት ላይ እንዴት ባንዲራ ያውለበልባሉ!” ሲል በንጉሱ ላይ ቅዋሜ አላሰሙም።

ኦሜድላ የኢትዮጵያ ለመሆንዋ ከዚህ በላይ ምን ማረጋገጫ አለ? ታዲያ በምን ምክንያት ነው አሁን ይቺ ታሪካዊ ስፍራ ለሱዳን የምትሸለመው? ቀዳማዊ ኅይለሥላሤ ኦሜድላ ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅአላማ ሲያውለበልቡ ጦሩን እንዲያቀነባብር በእንግሊዝ መንግሥት ተሹሞ አብሮአቸው በሱዳን በኩል የገባው ሜጄር ዊንጌትም ታዛቢ ሆኖ እጎናቸው ነበረ። ንጉሡን ተሽቀዳድሞ አዲስ አበባ የገባው ሎርድ ካኒንግሃምም እሳቸው ኦሜድላ ላይ የኢትዮጵያን ሰንደቅአላማ እንዳውለበልቡ አሳምሮ ያውቅ ነበር። እነዚህም ሁለት ታላላቅ የእንግሊዝ መንግሥት ተወካዮች ኦሜድላ የኛ ናት አላሉም። የሆነ ሆኖ እውነት እንግሊዝ ከ አፄ ምንይልክ ጋር ተዋውሎ ከነበር እሱው እንግሊዝ የመሬት ይገባኛል ጥያቄውን ያቅርብልን እንጂ ያልተዋዋልናት ሱዳን ምን አገባት? ከሱዳን ሳንዋዋል እንዴት ሱዳን የተዋዋልነው ይከበርልኝ፥ ልትል ትደፍራለች? ይህን ጥያቄ ሊያነሳ የሚችል አንግሊዝ ብቻ ነው። ነበርም። ግን እንግሊዞች አላነሱም። ምክንያቱም ቀላል ነው። የዚህ ዐይነት ውል ከአፄ ምንይልክ ጋር ስላተፈራረሙ። ተፈራርመው ቢሆን ኖሮ መጠየቅ ብቻ አይደለም፥የተፈራረሙበት ቀለም ሳይደርቅ መሬቱን እጃቸው ያስገቡ ነበር። ስላልተፈራረሙ ይህን አላደረጉም። የሱዳንን ነፃነት እንግሊዞች ሲፈቅዱም የተባለውን መሬት የኔ ነበር ብለው ወደ ሱዳን አላዘዋወሩም። አሁን ያለውን መሬት ብቻ ነው ትተውላቸው የሄዱት።አሱም ለሁለት ተከፍሎባቸዋል። ከአንግሊዝ የተረከቡትን መሬት እንኩውዋን በቅጡ መያዝ አቅቶአቸው “የቆጡን አወርድ ብላ የብብትዋን ጣለች፤” የተባለው ተረት በነሱ ላይ ተፈፅሞባቸዋል። የራሳችውን አጥብቀው መያዝ ሳይችሉ የኛን መሬት መከጀላቸው ማስቆጣት ብቻ ሳይሆን ያስደንቃል። እንግዲህ እንግሊዝ ከአፄ ምንይልክ ጋራ መሬትን አስመልክቶ ላለመዋዋሉ ሶስት ማስረጃዎች አሉ ማለት ነው። አንደኛ፥ የተባሉትን መሬቶች ቀደም ሲል እጁ ባለመክተቱ፤ ሁለተኛ፥ ንጎሱ ኦሜድላ ላይ ሰንደቅአላማችንን ሲሰቅሉ አለመቃወሙ፥ ሶስተኛ፥ ሱዳንን ለቆ ሲሄድ ለሱዳን ከተወላት የተባበሩት መንግሥታይ ባፀደቀላት ዳር ድንበር ውስጥ እነዚህን ሁሉ የኢትዮጵያ መሬቶች በካርታም ሆነ በፅሁፍ ባለማካተቱ። በነዚህ ሶስት ማስረጃውች ምክንያት እሩቅ ሳንሄድ፥ ሰነድ ለማግኘት አፈር ሳንቆፍር እና ድንጋይ ሳንፈነቅል ምንይልክ እና እንግሊዝ አንዳችም የመሬት ውል እንዳልተፈራረሙ እናረጋግጣለን። ተፈራርመዋል የሚል እስቲ ሰነዱን ያቅርብልን!!! ደግሞም ቢፈራረሙም እንኩዋን ውሉ የቅኝ ገዥዎች ሰለሆነና ምንይልክም ሆነ ማንኛውም መሪ የአትዮጵያ መሬት የግል ንበረቱ ስላልሆነ መሬት ለባእዳን ሰጥቻለሁ ቢል አይፀናም።አፄ ምንይልክ ተስማምተውበት፥ አፄ ኅይለሥላሴ እና ደርግ ያፀደቀውን ነው እኛ በ ተግባር የምናውለው፤ ሲል ኢህአዲግ ደጋግሞ ተናግሮአል።

ይህን መሰረት በማድረግ እኔ ብዙ ምርምር አካሂጄ ሁለቱ አፄዎችና የደርግ ሊቀመንበር የነበሩት ኮረኔል መንግሥቱ ኅይለማርያም ለሱዳን መሬት ለመስጠት የተዋዋሉበት አንድም ሰነድ አላገኘሁም።ምክንያቱም ስላልነበረ። ስለ ሌለም። አሁን በህይወት የአሉት ኮሎኔል መንግሥቱም አንድም የዚህ ዐይነት ውል ከሱዳን ጋር እንዳልተፈራረሙ አበከረው መስክረዋል። ይልቁንም አኔ ያገኘሁት መረጃ፥ አውሮፓውያን መንግሥታት ለብቻቸው ተሰብስበው አፍሪካን ለመቀራመት ያደረጉትን ውል ለአፄ ምንይልክ ነግረው የኢትዮጵያን ነፃነት ግን አንደሚያስጠብቁ ቢገልፁላቸው፥ “እኔ በሌለሁበት እናንተ ተሰብስባችሁ ያደረጋችሁትን ውል በፍፁም አልቀበልም፤ የኢትዮጵያን ነፃነት አናስጠብቃለን ሰለአላችሁት ግን አመሰግናለሁ፤” በማለት ተንኮላቸውን ውድቅ ማድረጋቸውን የሚያሳይ ነው። በነገራችን ላይ፤ አፄ ምንይልክ እንኩዋን ለሱዳን መሬት ሊሰጡና በሰላም ኢትዮጵያ ውስጥ ይኖሩ የነበሩት የውጭ ሀገር ሰዎች መሬት አንዲገዙ አይፈቅዱላቸውም ነበር። አላደረጉትም እንጂ ሶስቱም መሪዎች አድርገውትም እንኩዋን ቢሆን፤የኢትዮጵያን ህዝብ መሬት አንስተው ለባእዳን ለመቸር ምንም መብት አልነበራቸው። ኢትዮጵያ፥ እንዲያስተዳድሩዋት አደራ የተሰጠቻቸው ምድር እንጂ እንዳሻቸው ለፈለጋቸው አገር ገፅበረከት አድርገው የሚለግስዋት የግል ንብረታችው አልነበረችምና። አሁን ያለውም መንግሥት አንዲሁ የኢትዮጵያን መሬት ገምሶ ለባእዳን ለመቸር ከቶም አንድም ህገመንግሥስታዊ ነፃነት ወይም ስልጣን የለውም። በጉልበቱ ካልሆነ በቀር። ረጅሙን ታሪካችንን ወደ ሁዋላ መለስ ብለን ብናስተውል፥ ባለፉት 5300 ዐመታት ኢትዮጵያን የመሩት መንግሥታት ድንበር ከማስፋት በቀር መሬታቸውን እንደ አንጀራ ቆርሰው ለባእዳን ሲቸሩ በፍፁም ተስተውሎ አያውቅም። አሁን ከአለው መንግሥት በስተቀር።እዚህ ላይ ባድመ ይታወሰናል። ባድመ ባድማው ደረቁ መሬት ከአትዮጵያና ኤርትራ በኩል ወደ 150000 ገደማ ወይም ከዛ በላይ ምስኪን ሰዎች በከንቱ አስጨረሰ። ከዚያ አልጀርስ ላይ ለኤርትራ ይገባታል ይሰጣት፤ ተብሎ ተፈረደላት።ባድመ እስካሁን በ ኤርትራ እጅ ውስጥ አልገባችም። ለምን? የትግራይ መሬት ውስጥ ስለሆነች የማትነካ፥ የማትገሰስና የተቀደስች ሆና ወይስ በሌላ ምክንያት? ሰፊ መሬት አለኝ ብሎ ከማውራት በቀር ለማንም የማይጠቅመውን ጠፍ መሬት አንሰጥም ብሎ ይዞ፥ ለመሬት ብላ ከኛ ላልተዋጋችው ሱዳን ለምለም ምድር ገምጦ ለመቸር መቸኮል ምን ይባላል? ይህ ለሰሚው ግራ ነው። ባድመም በኤርትራ ላትወስድ የቻለችው፥ “ትግራይ ሀገርህ ተወራለችና የኢትዮጵያ ህዝብ ሆይ! ተነሳ!” ተብሎ በተጠራው የሀገር ማዳን ጥሪ መሰረት፥ “ጉዳዩ እኔን አይመለከተኝም ይህ የትገራይ መሬት ነው፤” ሳይል በብሄራዊ ስሜት የነደደው ቆራጡ የኢትዮጵያ ህዝብ አጥንቱን ከስከሶ፤ ደሙን አፍሶ፤ንብረቱን አጉድሎ ባደረገው ተጋድሎ ነው። ትግራይ ስትወረር የኢትዮጵያ ህዝብ ፥ “ወይኔ ሃገሬ!” ብሎ ደሙን ሲያፈስ ባድመ የመጨረሻው እንጂ የመጀመሪያው አይደለም። ከዛ በፊት ጣልያን ከማንም አስቀድሞ ትግራይን በወረራት ጊዜ በመቀሌ፥ በአምባላጌ፥በአድዋ እና በማይጨው በ 40 ዐመታት ልዩነት ውስጥ ሁለቴ ከፍተኛ መስዋእትነት ከፍሎአል። ለዚህ ሁሉ ውለታው አፃፋው ይሄ ነውን? እባካችሁ ሰከን ብላችሁ ነገሩን አስቡበት። ይህ ድርጊት በትውልድ ያስወቅሳችሁአል። ጠንቁ ለልጆቻችሁና ለልጅ ልጆቻችሁ፤ እንዲሁም ለዘራችሁ ይተርፋል። ለስልጣን ያበቃችሁ የትግራይ ህዝብ ሳያቀር በአደራጎታችሁ ያፍርባችሁአል። የኢትዮጵያ ህዝብ ዛሬ አቅም ባይኖረው ነገ ሊጠነክር ይችላል። ሳይወድና ሳይፈቅድ መሬቱን ሱዳን አሁን ብትወስድበት እንኩዋን ነገ ሲጠነክር ተዋግቶ ያስመልሰዋል። በዚህ ሳቢያ አሁን ልትጠቅምዋት ያሰባችሁአት ሱዳንም ሰላም አታገኝም። የ እናንተም ስም በክፉ ተነስቶ አፅማችሁም ሲወቀስ ይኖራል። ስለዚህ ሱዳንን በሌላ በሌላ ነገር ካስዋት እንጂ የስንት ሰማአታት ወገኖቻችን ደም እና ላብ የአለማውን መሬታችንን አሳልፋችሁ በብላሽ አትስጡ። ለሱዳን ካሳ፥ አፍንጫዋ ስር የተገነባላት የአባይ ግድብ መች አነሳት? በዚህ የኢትዮጵያ ህዝብ ገንዘቡን በከሰከሰበት ግድብ ከማንም በላይ ተጠቃሚዋ ሱዳን አይደለችንምን? ግድቡ ይበቃታል፤ መሬቱ ይቅርባት። ብቻችሁን ይህን መወሰን ካስቸገራችሁ ደግሞ ፓርላማችሁና የኢትዮጵያ ህዝብ ይምከርበት። ለይስሙላስ ቢሆን ፓርላማ አለ አይደል? እንዲህ ዐይነቱ ትልቅ የሀገር ሉአላዊነት ጉዳይ ሀገር ሳይመክርበትና ህዝብ ሳይወስንበት አንዴት በዝግ ጉዋዳ ይካሄዳል? ባድመ አንዳትወሰድ የተረባረባችሁትን ያህል አና ለኤርትራ አንዳይሰጥ የምትተጉትን ያህል፥ እባካችሁ አሁን ሱዳንን የሚያዋስናትን ሁሉ የኢትዮጵያ ዳር ድንበር ለሱዳን ከመቸር ታቀቡ። በውኑ ከዚህ ከታቀባችሁ፥እናንተም፤ ልጆቻችሁም፥ ዘራችሁም፥ አንዲሁም በመቃብር ውስጥ የሚኖረው አፅማችሁም ከመወቀስና ከመረገም ይተርፋል። ጆሮ ያለው ይስማ። ልብ የአለው ልብ ይበል።l

%d bloggers like this: