ማዕተቤን አልበጥስም !!!

By Zemedkun Bekele

በአንድ ወቅት በጨካኝነቱ ተወዳዳሪ ያልነበረው የታላቋ ሩስያ መሪ የነበረው ስታሊን በአገዛዝ ዘመኑ የሩስያ ኦርቶዶቶዶክስን ለማጥፋት ያልወሰደው አረመኔአዊ ድርጊት አልነበረም ። ከእነዚህም አረመኔያዊ ድርጊቶች መካከል የቤተክርስቲያኒቱን አማኞች በጥይት መግደሉ ጥይት ማባከን ነው ብሎ በማሰቡ ከፓትርያርኩ ጀምሮ እስከ አራስ ህፃናት ድረስ ያሉትን ኦርቶዶክሳውያን በግዙፍ መርከቦች እየጫነ ውቅያኖስ ውስጥ በመጨመር ለአሳነባሪዎች ቀለብ እስከማድረግ መድረሱ ፣ ይህን የመሰለው ግፍ ግን ኦርቶዶክሳውያኑን ከማጥፋት ይልቅ ይበልጥ ሃይማኖታቸውን እንዲያጠብቁ አደረጋቸው ። እንዲያውም በሩሲያ ታሪክ እንደዚያን ዘመን የኦርቶዶክሳውያን አማኞች ቁጥር በዝቶ የታየበት ዘመን እንደሌለ የታሪክ ፀሐፊዎች ይናገራሉ ።

የሁኔታውን አደገኛነት የተገነዘበው ስታሊን ፓርላማውን ሰበሰበና እንዲህ አለ ።” ጓዶች ይሄ አካሄዳችን አላማረኝም ከሃይማኖቱ ሰባኪዎች ይልቅ የእኛ ግድያ የሩስያ ኦርቶዶክስን እያለመለመ እና እያጠነከረ ይገኛል። እናም ግድያው ይቁም ። ምክንያቱም ከዚህ አይነቱ አካሄዳችን የተማርኩት ነገር ቢኖር ክርስቲያን እና ምስማር በመቱት ቁጥር እየጠበቀ መሄዱን” ነው ብሎ ከቅዱሳን አበው አንዱ የተናገሩት እስኪመስል ድረስ የክርስቲያን እና የሚስማርን ጉዳይ አንስቶ ለእኛ ለክርስቲያኖች የሚገርም ጥቅስ ትቶልን ፣ የሩሲያን ኦርቶዶክስ ማጥፋትም ባለመቻሉም ድክም ብሎት አቆመ ይባላል ።

ትናንት ከግሸን እንደተመለስኩ ለ 10 ቀናት ያህል የተለየሁትን የማኅበራዊ ድረገፆችን ለማየት ብከፍተው አንድ ደስ የማይል ዜና ብዙዎች ሲቀባበሉት ተመለከትኩ ። ብዙዎች የሚያወሩት በስሜት እንዳይሆን ብዬ ወደ አንድ ወዳጄ ጋር ብደውል ወሬ አለመሆኑን አረጋገጠልኝ ። እኔም ምንም ከሌሎች የተለየ ነገር ማለት ባልችልም የአቅሜን ታህል ድምፄን ላሰማ አልኩና ይኸው ብቅ አልኩኝ።

ክቡር ሚንስትሩ በሲቪል ሰርቪስ ስልጠና ላይ ግልፅ በሆነ አማርኛ ” የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ይሄን የኦርቶዶክሳውያን ማዕተብ መበጠሳችን አይቀርም ” ብለው መናገራቸውን ሰማን ። አንድን ሰው ወንጀለኛ አድርጎ ከባድ ፍርድ እንዲፈረድበት የሚያደርገው ደግሞ ምቹ ጊዜ ሰዓትና በተገቢው ሁኔታ ቅድመ ዝግጅት አድርጎ ወንጀል መፈፀሙ ሲረጋገጥ መሆኑን የህግ ባለሙያዎች ይናገራሉ ። አንዳንድ ሰዎች የሰው ህይወት በእጃቸው ጠፍቶ 3 እና 4 ዓመት የሚፈረድባቸው እና ሌሎች ደግሞ በተመሳሳይ መንገድ የሰው ሕይወት አጥፍተው ከ ዕድሜ ልክ እስከ ሞት ፍርድ ድረስ የሚያደርስ ቅጣት የሚወሰንባቸው ከ3 እና የ4 ዓመት ፍርደኞቹ በተለየ መልኩ በስህተትና በአጋጣሚ ሳይሆን ሆን ብለው አቅደው ፣ቅድመ ዝግጅትም አድርገው ሆን ብለው የፈፀሙት ወንጀል በመሆኑ ነው ቅጣታቸውን ከባድ የሚያደርገው ።

እኝህ ክቡር ሚንስትር በዚህች ጥንታዊት ቤተክርስቲያን ላይ ደስ የማይሉ ንግግሮችን ቀን እየጠበቁ መናገራቸውን ከጀመሩ ቆየት ብለዋል ። እኝህ ሰው ዛሬም ሲናገሩ እግዚአብሔር በሰማያት ብዙዎቻችን በምድር እየሰማን ነው። ከሰመነው ሰዎች መካከልም፦

1. ቅዱስ ፓትርያርካችን ሰምተዋል ።
2. መላው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ሰምተዋል።
3. ካህናት እና ዲያቆናቱም ሰምተዋል።
4. መነኮሳቱና ባህታውያኑም ሰምተዋል።
5. የሊቃውንት ጉባኤ አባላትም ሰምተዋል።
6. የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት በሙሉ ሰምተወል።
7. ዘማሪዎቻችንም ለዚህ የሚሆን ዜማ ባይደርሱም ሰምተዋል።
8. ፀሐፍያን ነን ብለው በየአጋጣሚው መከራ የሚያሳዪን ፀሐፍትም ሰምተዋል።
9. ከሁሉም በላይ ከየመንፈሳዊ ኮሌጆቻችን ተመርቀው የወጡና የአውደምህረት ላይ የስቱዲዮና የሲዲ ላይ አንበሶቻችንም በደንብ ሰምተዋል ። ግን ሁሉም ይስሙ እንጂ ምንም ሊሉን አልፈቀዱም።

ቅዱስ ፓትርያርኩን ጨምሮ ክቡራን ሊቃነ ጳጳሳቱ ከጥቂቶች በቀር ብዙሃኑ በእርግና ማእረግ ላይ የሚገኙ ያውም መቃብራቸው የተማሰ ልጣቸው የተራሰ ቢሆንም ዝም ብለዋል ። አረ ተዉ ውኃ ሽቅብ አይፈስም ነው እኮ የሚባለው። እናንተ ዝም ስላላችሁ እኮ ነው ፓስተር ዳዊት ነኝ የሚል ፍንዳታ ወጠጤ ተነስቶ እንደፈለገ ቅድስት ቤተክርስቲያንን የሚሰድባትን ሰው ነው እኮ እንዲያው ሰው የላትም ተብሎ ከሚቀር በማለት እነ መምህር ምህረተአብ የአቅማቸውን ያህል የሚፍጨረጨሩት ። ሌሎችም እንዲሁ በየአቅጣጫው እየተነሱ የፈሪ በትራቸውን ሲያወርዱባት ምነው ዝምታችሁ በዛ ።

ሰባኪዎቻችንም እንደሁ ከጥቂቶች በቀር ብዙሃኑ እኛን ኢትዮጵያን አትልቀቁ ዲቪም አትሙሉ እያሉን እነሱ ግን በቦሌም በባሌም ፣ በሚስትም በሲስተምም እልም እያሉ መኖርያቸውን ከኢትዮጵያ ውጪ ከማድረግ በቀር ፣ ንግድ ሚንስቴር በማያውቀው ነፃው አውደምህረት ላይ በየ ስቱድዮው በመቀረፅ ያልበላንን በማከክ ከሚያራግፉብን ሸቀጦች ሌላ እና ለእርድ እንደተዘጋጀ የሐረር ሰንጋ ራሳቸውን ከማደለብ በቀር ምንም ሲፈይዱ አይታዪም ።

እስቲ ጥሩልኝ ኢትዮጵያ ውስጥ የቀረ ኑሮውን በምእራብ ሀገራት ያላደረገ ሰባኪ ። ከ ምህረተአብ በቀር እንደው በቤተክርስቲያን ላይ የሚወረወሩ ቀስቶችን ለመመከት የሚፍጨረጨር ማን አለ ? ንገሩኛ እከሌ በሉኝ ። ወይኔ ዛሬ እንኳን ሰው ይጥፋ ? እነ አትናትዮስን እነ ቅዱስ ጊዮርጊስን የወለደችው ቅድስት ቤተክርስቲያን የወላድ መካን ሆና ትታይ።

እኔ የምለው ክቡር ሚንስትር ይሄ አሁን ግዜ እየጠብቅንለት ነው ብለው የነገሩን ማዕተብ ከኦርቶዶክሳውያን አንገት ላይ የመበጠሱ ነገር የምእራብ ኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ባለፈው ዓመት ከምእራብ የሀገራችን ክፍል መጥተው ለቅዱስ
ሲኖዶሱ እንደተናገሩት …… ” ፖሊሶች በአንዳንድ ትምህርት ቤቶች በራፍ ላይ በመቆም ከኦርቶዶክሳውያን ተማሪዎች አንገት ላይ እየበጠሱ ነው ያሉትን አቤቱታ መነሻ በማድረግ በዚያ የታየው ማዕተብ የማስበጠስ ስራ ተሞክሮው አበረታች ሆኖ በመገኘቱ ነው ለዚህ አዋጅ መሰል ዛቻ ያበቃዎት ?

ሲቀጥል ደግሞ እርስዎ የሚከተሉት ሃይማኖት ምን ይሆን ?

እኔ ግን እላለሁ

1. ባለፈው ጊዜ ማኅበረ ቅዱሳንን የመጎነታተል ነገር ቢሞከር ከታሰበው በላይ ከማኅበሩ በተለያዪ ምክንያቶች የራቁትን ጨምሮ ሌሎች አዳዲስ አባላትን ወደ ማኅበሩ በማምጣት ማኅበሩን በሰው ኃይል እንዲጠናከር አድርጎታል።

2. በሻሻ የሚባል ቦታ በሀገራችን መኖሩን የሚያውቅ ከአካባቢው ሰው በቀር ስለ በሻሻ የሚያውቅ ብዙ ሰው አልነበረም ። ነገር ግን ጥቂት ብዙኃኑን የእስልምና እምነት ተከታዮች የማይወክሉ አሸባሪዎች ማዕተባችንን አንበጥስም ባሉ የተዋህዶ ልጆች ላይ በፈፀሙት ግድያ ምክንያት በሻሻ በዓለም ላይ ታወቀች። ዛሬ በሻሻ ልክ እንደ አክሱም ፅዮን ፣ ግሸን ማርያም ፣ ቅዱስ ላሊበላ ፣ ቁልቢ ገብርኤል ከመላው ዓለም በሚመጡ ምእመናን ይጨናነቃል ። በአክራሪዎቹ የወደመችዋ ደሳሳዋ የበሻሻ አቡነ ገብረመንፈስ ቅዱስ ቤተክርስትያንም ዛሬ በሚገርም ካቴድራል ተተክቷል ። ለዚህ እውቅና ደግሞ ሀገረ ስብከቱ ምንም ያደረገው አስተዋፅኦ የለም ። የሰማዕታቱ መሰየፍ እንጂ ።

ይገርምዎታል ክቡር ሚኒስትር የበሻሻ ጉዳይ መች በዚህ ብቻ ያበቃል መሰልዎ ። አሁን መላውን ዓለም እያስደመመ የሚገኘው የወጣቶች የጥምቀት በዓል አከባበርን የወለደው እኮ የበሻሻ ሰማእታት ደም ነው። በዚህ ጉዳይ የአንድም ሰባኪ እጅ የለበትም ። ከግሪሳዎቹ የተሃድሶ ርዝርራዦች መካከል አንዱ ግሪሳ ብቻ ነው የእኛ የአገልግሎት ነው ወጣቱን እንዲህ እንዲነሳሳ ያደረገው ሲል የተሰማው። ይህ ግን ሀሰት ነው ግሪሳዎቹ ኪሎና የባንክ አካውንታቸውን ከመጨመርና ከማብዛት በቀር አንድም ምእመን ወደ ቤተክርስቲያን ጉያ አልጨመሩም ።

አሁን ደግሞ ምን እየሆነ መሰልዎት እርስዎ የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ ማዕተብ ማስበጠሳችን እንደሁ አይቀር አሉ ከተባለ ወዲህ ይገርምዎታል የኦርቶዶክሳውያኑን አንገት ቢመለከቱ ቀድሞ የሀብት መግለጫ የነበሩትን የወርቅና የብር ሐብሎች በሚያምሩና በወፋፍራም የማዕተብ ክሮች ተተክተው እየታዩ ነው ። የብዙኀኑ የፌስ ቡክ ፕሮፋይል ፒክቸሮችም በማዕተብ ክሮች እየተለወጡ ነው ። የማዕተብ ክር ነጋዴዎችም ገበያ ድርት ብሏል። ምነው ደግሞ ቅዳሴ ማስቀደስ ፣ ንስሀ መግባት ፣ ስጋወደሙ መቀበል ፣ ፆም መፆም የሚከለክል በመጣና ተአምር ባየን ። ከዘመኑ ሰባክያን ይልቅ ምእመናን ወደ ቅድስት ቤተክርስትያን ለመመለስ እግዚአብሔር ባወቀ በአንድም በሌላም መንገድ የአህዛብና የመናፍቃን መነሳሳት ሳይሻል አይቀርም ። እንደውም የዘመኑን ግሪሳ ሰባክያን እና ዘማርያን ልብ ብላችሁ አንገታቸውን ብታዩት ማዕተብ የለውም።

በመጨረሻም ክቡር ሚንስትር እኔ ማዕተቤን በአንገቴ የማስረው ለጌጥ ሳይሆን ጌታ በማቴዎስ ወንጌል ምእራፍ 10 ፣ 32 – 33 ላይ የተናገረውን አምላካዊ መመርያ መሰረት በማድረግ ነው። ” ስለዚህ በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ፤ በሰው ፊትም የሚክደኝን ሁሉ እኔ ደግሞ በሰማያት ባለው በአባቴ ፊት እክደዋለሁ ይላል። ይህ ማለት በአፌ ማንነቴን መግለፅ የማልችል ብሆንም እንኳን ማዕተቤን በአንገቴ ላይ ማሰሬ ብቻውን የክርስቶስ መሆኔን እርርሪሪ እያለ በመጮህ ይመሰክርልኛል ።

ግን ቆይ የማዕተብ ክር በአንገታቸው ላይ ያለውን እናቆይ እና ሌሎቹን በትግራይ ፣ በአማራ ፣ በኦሮምያ ፣ በደቡብና በተለያዩ የሀገራችን ክፍሎች ያሉትን በግንባራቸዉ ፣ በአንገታቸው ፣ በክንዳቸው ላይ የተነቀሱ ኦርቶዶክሳውያን ዕጣ ፈንታስ እንዴት ሊሆን ነው ? ለዛሬ አበቃሁ ።

ዘመድኩን በቀለ ነኝ
ከግሸን ደብረ ከርቤ መልስ
መስከረም 26/ 1 /2007 ዓም
አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ

%d bloggers like this: